ሩሲያዊው የኦርቶዶክስ ቄስ በባለቤታቸው "ሀጥያት" ለቅጣት ራቅ ወዳለ ገጠር ተመድበዋል

ኦስካና ዞቶፋ

የፎቶው ባለመብት, Yana Terekhova

በሩሲያ ኡራል በምትባል ግዛት የሚኖሩ አንድ የኦርቶዶክስ ቄስ ባለቤታቸው በፆም ወቅት በአካባቢው ቁንጅና ውድድር በመሳተፏ ለቅጣት ሲባል ራቅ ወዳለ ገጠር ተመድበዋል።

ኦክሳና ዞቶፋ የተባለችው ግለሰብ የቁንጅና ሳሎን ያላት ሲሆን ቁንጅና ውድድር ማሸነፏን ተከትሎ ባለቤቱ ያልታወቀው ፒካቡ የተባለ ድረ ገፅ አሸናፊዋ የቄስ ሚስት መሆኗን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ከፍተኛ ትችትን አስተናግዳለች።

የእምነቱ ኃላፊዎች ድርጊቷን ከሰሙ በኋላም ቄሱን ሰርጂ ዞቶፍን በማግኒቶጎርስክ ከተማ ውስጥ ከሚገኘው የኢየሱስ እርገት ተብሎ ከሚጠራው ካቴድራል ከኃላፊነታቸው እንዲነሱ አድርገዋቸዋል።

ከማግኒቶጎርስክ 65 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኝ አንዲት መንደር የተመደቡ ሲሆን የህዝብ ቁጥሯም አራት ሺ ብቻ እንደሆነ ተገልጿል።

የቤተክርስቲያን አስተዳደርና ጉዳዮችን የሚመለከተው ፍርድ ቤት ኃላፊ የሆኑት ኤጲስ ቆጶስ ፌዮዶር ሳፕሪይክን እንደተናገሩት " የቄስ ሚስት ራሷን እንዲህ መገላለጧ ከፍተኛ ኃጥያት ነው" ብለዋል።

ባለቤታቸው ንስሀ እስከምትገባም ድረስ ወደ ኃላፊነት እንደማይመለሱም ውሳኔ አስተላልፈዋል።

"ቤተሰቡን መቆጣጠር የማይችል ምን አይነት ቄስ ነው? እንዴትስ አድርጎ ነው ጉባኤውን የሚቆጣጠረው" የሚል ጥያቄም አንስተዋል።

አዲሱ የተመደቡበት ቤተክርስቲያን

የፎቶው ባለመብት, PoChel.ru

ፒካቡ የተባለው ይሄው ድረገፅም ያወጣው ፅሁፍ እንደሚያትተው ይህ የሚያስቆጣ ስራዋ የመጀመሪያዋ እንዳልሆነ ነው።

ሌቭ ባክሊትስኪ የተባሉት ሌላኛው ቄስ በበኩላቸው በአንድ ወቅት በባህር ዳርቻ አጠገብ የዋና ልብስ ለብሳ ፎቶ ተነስታ በማህበራዊ ሚዲያ የለጠፈች ሲሆን ፎቶውንም ያጠፋችው ከተነገራት በኋላ መሆኑን ገልፀዋል።

"ባህሪዋ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው" ነው ያሉት ቄስ ሌቭ ቄሱ ከስራቸው ተነስተው ወደ ሌላ አካባቢ መመደባቸው ጊዜያዊ እርምጃ እንደሆነና "ወደ ቀልባቸው እንዲመለሱ መልዕክት እንዲሆናቸው ነው" ብለዋል።

ከስራቸው የተነሱት ቄስ በበኩላቸው ጥፋት እንደሰሩ ቢያምኑም ቅጣቱን ግን ምህረት አልባ ብለውታል።

ከዚህም በተጨማሪም ባለቤታቸው በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ አፀያፊ አስተያየቶች እንደደረሰባት በመንገርም ምሬታቸውን አቅርበዋል።

ዜናው የብዙ ሩሲያውንን ቀልብ የሳበ ሲሆን አንዳንዶችም ቄሱን ከመተቸት አልቦዘኑም " ስለ ቄሶች ባለቤቶችም ሆነ ቄሶችም ማወቅ የሚገባችሁ ይህንኑ ነው። የሚሰብኩትን በተግባር የማያውሉ ናቸው" በማለት አንድ አስተያየት ሰጭ ዘልፏቸዋል።

ሌሎች በበኩላቸው የቤተ ክርስቲያኗን ውሳኔ በማፌዝ ለባለትዳሮቹ ድጋፋቸውን ገልጸዋል።

"ህይወቷን ተደስታ የማትኖረው ለምንድን ነው? ቄሶች ከሀጥያት ነፃ ናቸው ብለው የሚያምኑ አሁንም አሉ ማለት ነው። እነሱ እኮ ጥሩ ስራ ያላቸው ተራ ሰዎች ናቸው" የሚል አስተያየት በፒካቡ ድረገፅ ላይ ተነቧል

"ችግሩ ምንድን ነው? የሳትኩት ነገር ይሆን? በመፅሀፍ ቅዱስ ውስጥ የትኛው ቦታ ላይ ነው ቄሶች ቆንጆ ሚስት እንዳይኖራቸው የሚከለክለው" በማለት አስተያየቱን የሰነዘረም አለ።

ከዚህም በተጨማሪ ቤተ ክርስቲያኗን በነገር ሸንቆጥ ያደረጉ አስተያየቶች አልታጡም "ከሁሉም የተቀደሱት እኒህ ሰዎች በፆም ወቅት የሌሎች አይን በሜካፕ ቢሸፈንም ጉድፍን ማየት ችለዋል" በማለት ነው።