ኢትዮጵያዊያን፣ ጃፓናዊትና ህንዳዊ በታጣቂዎች ተገደሉ

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ነጆ ወረዳ ሁምነ ዋቀዮ በተባለ ቀበሌ ውስጥ ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት የአምስት ሰዎች መገደላቸውን የኦሮሚያ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ አስታወቀ።
ታጠቂዎቹ ጥቃቱን የፈጸሙት ዛሬ (ማክሰኞ) ጠዋት አንድ ሰዓት ተኩል ገደማ ሲሆን፤ በጥቃቱም ሁለት የውጪ ሀገራት ዜጎች እና ሦስት ኢትዮጵያዊያን በአጠቃላይ አምስት ሰዎች መገደላቸውን የክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ገልጿል።
በአካባቢው የተሰማራው ኮማንድ ፖስት አባል የሆኑት አቶ አደም ኢስማኤል ለቢቢሲ እንዳረጋገጡት የውጪ ሃገር ዜጋ የተባሉት ሟቾች አንዲት ጃፓናዊትና አንድ ህንዳዊ ናቸው።
በታጣቂዎቹ የተገደሉት ሰዎች ሰንራይዝ የሚባል ኩባንያ ሰራተኞች እንደነበሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ጥቃቱ የተፈጸመባቸው ሰዎች በአንድ መኪና ሲጓዙ በተጠቀሰው አካባቢ በተከፈተባቸው ተኩስ መገደላቸውን የጠቀሱት አቶ አደም፤ አጥቂዎቹ ኋላም መኪናውን በእሳት እንዳቃጠሉትም ተናግረዋል።
በእሳት የተያያዘውን መኪና ማጥፋት በአካባቢው ከነበሩት ሰዎች አቅም በላይ ሆኖ በመቆየቱ የተገደሉት ሰዎች አስከሬን ለቃጠሎ መዳረጉንና ለመለየት አስቸጋሪ እንደነበር ተገልጿል።
ከጥቃቱ በኋላ የጸጥታ አካላት ባደረጉት አሰሳ በግድያው የሚጠረጠሩ ሰዎችን በቁጥጥር ስር ማዋላቸው ተገልጿል።
ግድያውን የፈጸሙት ታጠቂዎች ማንነታቸው ያልታወቀ ሲሆን እንደሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ለጸጥታ ኃይሎች ጥቆማ ሰጥተዋል።












