የጋራ መኖርያ ቤቶቹ በዕጣ መተላለፋቸውን የኦሮሚያ ክልል ተቃወመ

በአዲስ አበባ የተገነቡ ኮንዶሚንየም ቤቶች

የፎቶው ባለመብት, Mayor Office of Addis Ababa

የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ዛሬ በክልሉ አንዳንድ ከተሞች የተደረገውን የተቃውሞ ሰልፍ ተከተትሎ ማምሻውን መግለጫ አውጥቷል። በመግለጫው እንደተመለከተውም ትናንት ለባለእድለኞች በዕጣ የተላለፉ የጋራ መኖርያ ቤቶችን በተመለከተ የጸና አቋም ወስጃለሁ ብሏል።

የአዲስ አበባም ሆነ ተያያዥ ጉዳዮች በቅደም ተከተል ምላሽ እንደሚያገኙ የተስማማንባቸው ጉዳዮች ነበሩ ያለው መግለጫው ነገር ግን በአዲስ አበባና ኦሮሚያ መካከል ያለው የወሰን ጉዳይ እልባት እስከሚያገኝ ድረስ የኦሮሚያን ወሰን ተሻግረው የተሠሩ መኖርያ ቤቶች በዕጣ መተላለፋቸው ተቀባይነት የለውም ሲል አስታውቋል።

በመሆኑም ይላል መግለጫው፣ በመሆኑም ይህ በዕጣ የማስተላለፉ ውሳኔ ሥራ ላይ እንዳይውል 'የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የጸና አቋም አለው'።

መግለጫው ጨምሮ እንዳለው ይህ አቋም የተወሰደው በቀናነትና የሕዝባችን ተጠቃሚነት ለማስከበር እንጂ የሕዝቦችን በጋራ የመኖር እሴት ከመጥላት አይደለም፤ ይህንንም ሕዝቡ ሊገነዝብ ይገባል ብሏል።

የክልሉ መንግሥት ከአዲስ አበባ ጋር በተገናኘ የሚነሱ ማናቸውንም አጀንዳዎች ከኦሮሚያ ሕዝብ ፍላጎትና ተጠቃሚነት አንጻር ብቻ እንደሚመለከተውም አስምሮበታል።

በመሆኑም በአዲስ አበባ ዙርያ የሚሠራው ሥራ ከኦሮሚያ መንግሥትና ሕዝብ ዕውቅና ውጭ በመሆኑ ሕገ ወጥ ነው ብለን እናምናለን ይላል።

አዲስ አበባ ላይ ከድንበርና ከቤቶች ጉዳይ ባለፈ የአዲስ አበባን የኦሮሞ ባለቤትነት ጥያቄ ለማረጋገጥ የጀመርነውን ሥራ አጠናክረን እንቀጥላለን ሲል መግለጫው ይደመድማል።