ዋትስአፕ ከአምስት ጊዜ በላይ መልዕክት ማጋራት አገደ

በዋትስአፕ አንድን መልዕክት ከአምስት ጊዜ በላይ መላክ አይቻልም

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, በዋትስአፕ አንድን መልዕክት ከአምስት ጊዜ በላይ መላክ አይቻልም

ዋትስአፕ ተጠቃሚዎች አንድን መልዕክት ከአምስት ጊዜ በላይ እንዳያጋሩ አገደ። ከዚህ ቀደም ተጠቃሚዎች የጽሁፍ መልዕክት ወይም ምስል በአንድ ጊዜ ለ20 ሰዎች ማጋራት ይችሉ ነበር።

ዋትስአፕ ከዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው የሀሰተኛ ዜና ስርጭትን ለመግታት እንደሆነ ተገልጿል።

የዋትስአፕ ተጠቃሚዎች ከአምስት ጊዜ በላይ መልዕክት እንዳያጋሩ የሚያግውን አሰራር ከስድስት ወር በፊት በሕንድ መተግበር ጀምሯል።

ከዚህ ቀደም ሕንድ ውስጥ በዋትስአፕ በተሰራጨ ሀሰተኛ ዜና ምክንያት የመንጋ ጥቃት መከሰቱና ብዙዎች መጎዳታቸውም ይታወሳል።

አንድ ሰው የሚደርሰውን መልዕክት አምስት ጊዜ ካጋራ በኋላ እያንዳንዶቹ ተቀባዮቹም አምስት ጊዜ መልዕክቱን ሊያጋራቱ ይችላሉ። ሆኖም ስርጭቱ ከቀደመው ጊዜ የተሻለ እንደሚገደብ የዋትስአፕ ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

አደገኛ ይዘት ያላቸው መልዕክቶች ስርጭትን ለመግታት ለወደፊት ሌሎች ተጨማሪ እርምጃዎች እንደሚወሰዱም ቃል አቀባዩ አክለዋል።

በአንድ የዋትስአፕ ቡድን ውስጥ 265 ተጠቃሚዎች መግባት ይችላሉ። ስለዚህ አንድ ተጠቃሚ የሚልከው መልዕክት ቢበዛ ለ1,280 ሰዎች ይደርሳል። ቀድሞ ግን 5,120 ሰዎች ይደርስ ነበር።

ዋትስአፕና ፌስቡክ ሀሰተኛ ዜናና ፕሮፖጋንዳ በመንዛት ስማቸው እየተብጠለጠለ ነው። ባለፈው ሳምንት ፌስቡክ 500 ሀሰተኛ ዜና የሚያሰራጩ ገጾችን ማገዱ ይታወሳል።