ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
የቻይና ምጣኔ ሃብት እድገት በአስርት አመታት ውስጥ ዝቅተኛ ቁጥር አስመዘገበ
የቻይና ምጣኔ ሃብት በባለፈው ሩብ አመት ማሽቆልቆሉ የዓለምን የኢኮኖሚ ስርአት ያዛባዋል የሚል ፍራቻን አሳድሯል።
እስከ ታህሳስ ባሉት ሶስት ወራት ውስጥ የምጣኔ ሃብት እድገቷ 6.4% ያስመዘገበ ሲሆን ይህም በባለፈው አመት ከነበረው 6.5% ያነሰ ሆኖ ተገኝቷል።
በአጠቃላይ በአመቱ ውስጥ 6.6% እድገትን ያስመዘገበች ሲሆን ይህም እንደ ጎርጎሳውያኑ አቆጣጠር ከ1990 በኋላ ዝቅተኛው ነው ተብሏል።
ምንም እንኳን የተመዘገበው የኢኮኖሚ እድገት ተገምቶ ከነበረው ቁጥር ጋር የሚጣጣም ቢሆንም የአለም ትልቋ ኢኮኖሚ እድገት መቀዛቀዝ ሊፈጥረው የሚችለው ተፅእኖ አሳሳቢ ሆኗል።
ቻይና በአለም ላይ ያላትን ከፍተኛ መስፋፋት ተከትሎም ነው በአለም አቀፉ ኢኮኖሚ ላይ ፍራቻን ያስከተለው።
ሰኞ እለት የወጣው ይህ ቁጥር ከአለም አቀፉ የኢኮኖሚ ቀውስ በኋላ የተመዘገበ ዝቅተኛ የሩብ አመት እድገት መሆኑም ተገልጿል። የቻይና እድገት ከአመት አመት የተወሰነ መቀነስን ቢያሳይም በቅርብ ወራት ግን የተከሰተው ማሽቆልቆል ኩባንያዎችን አሳስቧቸዋል።
በዚህ ወር መጨረሻ የአፕል ኩባንያ የቻይና ኢኮኖሚ መቀዝቀዝ ሽያጩን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንሰው ገልፆ ነበር።
የመኪና አምራቾችና ሌሎች ኩባንያዎችም ከአሜሪካ ጋር ያለው የንግድ ጦርነት በቻይና እንዲሁም በአለም አቀፉ ምጣኔ ሃብት ላይ እያስከተለ ያለውን ጫና በመናገር ላይ ናቸው።
የቻይና መንግሥት ምርቶችን ወደ ውጪ ሃገር ከመላክ ይልቅ የተመረቱትን ምርቶች ሃገሬው እንዲጠቀምባቸው የማድረግ የኢኮኖሚ ዘዴን ለመቀየስ እየሰሩ ነው።
የፖሊሲ አማካሪዎችም ኢኮኖሚውን ለመደገፍ ጥረት እያደረጉ ነው።
እየተደረጉ ካሉ ርብርቦች መካከል የተለያዩ የግንባታ ስራዎችን ስራ ማጣደፍ፣ ግብርን መቀነስና እንዲሁም ባንኮች የሚይዙትን መጠባበቂያ ክምችት መቀነስ መሆኑ ተገልጿል።
ኢቫንስ ፕሪቻርድ የተሰኘው የቻይና ምጣኔ ሃብት ባለሙያ እንደገለፀው ምንም እንኳን ቁጥሩ ዝቅ ያለ ቢሆንም እንደተፈራው እንዳልሆነ ነው።