ጆን ማጉፉሊ፦ ታንዛኒያ "አስገዳጅነት የሌለበትን" የቻይናን እርዳታ ትመርጣለች

የፎቶው ባለመብት, AFP
የታንዛኒያው ፕሬዝዳንት ጆን ማጉፉሊ ከምዕራባውያን ከሚገኘው እርዳታ ይልቅ አነስተኛ ግዴታ ያለበትን የቻይና እርዳታን እንደሚመርጡ ተናገሩ።
ማጋፉሊ በአጨቃጫቂ ፖሊሲዎቻቸው ምክንያት ምዕራባዊያን ከፍተኛ ጫና እያሳደሩባቸው ነው።
በህዳር ወር ዴንማርክ "በተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ላይ ተቀባይነት የሌለው አስተያየት" ሰጥተዋል በሚል የ9.8 ሚሊየን ዶላር እርዳታን አቋርጣለች።
በአሁኑ ወቅት በአፍሪካ ፈታኝ ከሆነው የምዕራባውያን ተፅዕኖ በተፃራሪው ቻይና ከፍተኛዋ የልማት አጋር ሆናለች።
በቀጣዮቹ ሶስት አመታትም 60 ቢሊየን ዶላር የሚያወጣ ብድርና እርዳታ በአፍሪካ ላይ ለማፍሰስ ቃል ገብታለች። የዚህ እርዳታና ብድር አብዛኛው ገንዘብ የሚውለው መሰረተ ልማትን ለመገንባት ይሆናል ተብሏል።የሐሙስ ምሽት አጫጭር ዜናዎች
"እርዳታቸው የሚያስደስተው ነገር በምንም አይነት ግዴታዎች የታጠረ አይደለም። ሊሰጡ ሲወስኑ ይሰጡናል" ብለዋል ፕሬዝዳንት ማጉፉሊ።
ይህንን የተናገሩት ከቻይና መንግስት በተገኘ የ40.6 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ በዳሬ ሰላም በሚገኝ ዩኒቨርስቲ የተገነባውን ቤተ መፃህፍት በመረቁበት ወቅት ነው።
በአሁኑ ወቅት የአውሮጳ ህብረት ለምስራቅ አፍሪካ በየአመቱ የ88 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ በማድረግ ትልቁ የልማት አጋር ነው።













