በአለም ላይ በየቀኑ 137 ሴቶች በህይወት አጋሮቻቸውና በቤተሰቦቻቸው ይገደላሉ

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መረጃ እንደሚያሳየው በዓለም ላይ በአማካኙ 137 ሴቶች በህይወት አጋራቸው፣ በፍቅረኞቻቸውና በቤተሰቦቻቸው በየቀኑ እንደሚገደሉ ነው።
ፅሁፉ እንደሚያሳው በከፍተኛ ሁኔታ ሴት የምትገደልበት ቦታ ቤቷ እንደሆነ ነው።
በባለፈው ዓመት ከተገደሉት 87 ሺ ሴቶች መካከል ግማሹ ህይወታቸው የጠፋው የቅርብ በሆኑ ቤተሰቦቻቸው ሲሆን 30 ሺዎቹ በህይወት አጋራቸው እንዲሁም 20 ሺዎቹ በዘመዶቻቸው እንደሆነ መረጃው ያሳያል።

የወንዶች ግድያ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ ላይ ነው
የተባበሩት መንግሥታት መረጃ ጨምሮ እንደሚያሳየው ከሴቶች በላይ በአራት እጥፍ ወንዶች በግድያ ህይወታቸውን ያጣሉ
ይኼው መረጃ እንደሚያሳየው ከአስሩ ግድያዎች ስምንቱን የሚፈፅሙት ወንዶች መሆናቸውን ነው።
ነገር ግን ሪፖርቱ እንደሚያሳየው ግድያ ከሚፈፀማባቸው አስሩ ስምንቱ ሴቶች ሲሆኑ ጥቃቱም የሚደርሰው በፍቅረኞቻቸውና በህይወት አጋሮቻቸው ነው።
"በህይወት አጋሮቻቸውና በፍቅረኞቻቸው የሚገደሉ ሴቶች ቁጥር እየጨመረ ሲሆን በሴቶችም ላይ ከፍተኛ ጫና እያደረሰ እንደሆነ" ሪፖርቱ ያትታል።
አርባ ሴቶች፣ 21 ሃገራት፣ አንድ ቀን
ከአውሮፓያኑ ጥቅምት 1 ጀምሮ የተለያዩ የሚዲያ ሽፋኖችን በመዳሰስ ከፆታቸው ጋር በተያያዘ በ21 ሃገራት ላይ የተገደሉ ሴቶች ቁጥር 47ነው።
እነዚህ ግድያዎች አሁንም ምርመራ ላይ ናቸው።
በሀገሪቱ ሚዲያ ከተዘገቡና የሀገሪቱ ባለስልጣናትም ካረጋገጧቸው አምስት ግድያዎች እነሆ

የፎቶው ባለመብት, Family handout
ጁዲት ቼሳንግ፣ 22፣ ኬንያ
ጥቅምት ወር ላይ ጁዲት ቼሳንግና እህቷ ናንሲ የማሽላ እህላቸውን በማረስ ላይ ነበሩ። የሶስት ልጆች እናት የሆነችው ጁዲት ከባለቤቷ ላባን ካሙረን ጋር የተለያየች ሲሆን ወደ ቤተሰቦቿ መንደር ለመመለስም ወሰነች።
እህትማማቾቹ የተለመደ ተግባራቸውን ማከናወን በጀመሩበት ወቅት የፈታችው ባለቤቷ ደርሶ ጁዲትን ገደላት።
የአካባቢው ፖሊስ እንደገለፀው ግለሰቡ በአካባቢው ማህበረሰብ ተገድሏል።
ይኸው ሪፖርት ጨምሮ እንደጠቀሰው አፍሪካም ውስጥ በትዳር አጋሮቻቸው ወይም በቤተሰቦቻቸው የሚገደሉ ሴቶች ቁጥር ከፍተኛ ሲሆን፤ ከ100 ሺ ሰዎች 3.1 እንደሆነም ተጠቅሷል።
የባለፈው አመት መረጃ እንደሚያሳየው እስያ በሴቶች ግድያ ከፍተኛ ቁጥር መያዟን ነው። በባለፈው አመት 20 ሺ ሴቶች ተገድለዋል።

የፎቶው ባለመብት, Manohar Shewale
ኔሃ ሻራድ ቻውዱሪ፣ 18፣ ህንድ
ኔሃ ሻራድ ቻውዱሪ በ18 አመቷ የክብር ግድያ ተብሎ በሚጠራው ሳትገደል እንዳልቀረች ተገምቷል።
በተገደለችበት ወቅት ከወንድ ጓደኛዋ ጋር የተገናኙበትን ዕለት እያከበረች የነበረ ሲሆን፤ ግንኙነታቸውንም ቤተሰቦቿ ይቃወሙ ነበር ተብሏል።
በዛችው ዕለትም ወላጆቿና አንድ የወንድ ዘመድም ቤት እንደገባች በመግደል ተወንጅለዋል።
ምርመራው የቀጠለ ሲሆን፤ ቢቢሲ ከቤተሰቦቿ ጠበቃ እንደተረዳው የቀረበባቸውን ክስ ሊክዱ እንደተዘጋጁ ነው።
በመቶዎች የሚቆጠሩ ሴቶች ቤተሰብ ከማይፈቅደው ወንድ ጋር የፍቅር ግንኙነትና ትዳር በመመስረትና ይገደላሉ።
ይህ የክብር (ኦነር ኪሊንግ) ተብሎ የሚጠራው ግድያ ሪፖርት ስለማይደረግም መረጃ ማግኘት አስቸጋሪ ነው።

የፎቶው ባለመብት, Private via Amnesty International
ዘይናብ፣ ሴካንቫን፣ 24፣ ኢራን
ዘይናብ ሴካንቫን ባሏን ገድላለች በሚል በኢራን ባለስልጣኖች ተገድላለች።
ዘይናብ በሰሜናዊ ምዕራብ ኢራን ወግ አጥባቂ ከሆኑ ቤተሰቦች ሲሆን የተወለደችው፤ ዝርያዋም ከኩርዲሽ ወገን ነው።
ገና በህፃንነቷ ከቤተሰቦቿ ጠፍታ የሄደችው ዘይናብ፤ የተሻለ ህይወትንም ፍለጋ አገባች።
አምነስቲ እንደገለፀው ባለቤቷ አካላዊ ጥቃትና ድብደባ ያደርስባት የነበረ ሲሆን ፍችም በተደጋጋሚ ብትጠይቅ ምላሽ አላገኘችም፤ ፖሊስ ጥያቄዋን ችላ ብሎታል።
በ17 ዓመቷም ባሏን በመግደል ወንጀል ተከሰሰች።
አምነስቲን ጨምሮ ደጋፊዎቿ እንደሚሉት ባለቤቷን መግደሏን እንድታምን ፖሊሶች ድብደባና እንግልት ያደረሱባት ሲሆን፤ ትክክለኛ ፍርድም አላገኘችም።
ሪፖርቱ ጨምሮ እንደገለፀው የህይወት አጋሮቻቸውን የገደሉ ሴቶች ከፍተኛ የሆነ አካላዊ ጥቃት እንደሚደርስባቸው ነው።
ወንድ ጥቃት አድራሾች በበኩላቸው "መቆጣጠር መፈለግ፣ ቅናትና መተው" ሴቶችን ለመግደል የተነሳሱባቸው ምክንያቶች እንደሆኑም ተጠቅሷል።

የፎቶው ባለመብት, Reproduction / Facebook
ሳንድራ ሉሲያ ሐመር ሞራ፣ 39፣ ብራዚል
ሳንድራ ሉሲያ ሐመር ሞራ ከአጉያር ሪቤይሮ በ16 ዓመቷ ተጋባች።
ባሏም የገደላት ከተፋቱ ከአምስት ወራት በኋላ ነው።
ፖሊስ ለቢቢሲ ብራዚል እንዳሳወቀው አንገቷ ላይ በጩቤ ተወግታ ነው የተገደለችው።
ገዳዩነ ባለቤቱን መግደሉን በስልኩ ቪዲዮ በመቅረፅ ተናዟል።
በቪዲዮውም ላይ እንደሚታየው ሳንድራ ሌላ ፍቅረኛ እንደያዘችና እንደካደችውም ተናግሯል።
መታሰር እንደማይፈልግና " የአምላክን መንግሥት አብረው እንደሚወርሱ ጠቅሶ መኝታ ክፍላቸው ውስጥ ራሱን ገድሎ ተገኝቷል።
የሳንድራ ጉዳይ "ገድሎ ራስን ማጥፋት" የሚባል ሲሆን፤ይህም አንድ ሰው ሰዎችን ገድሎ ራሱን የሚያጠፋበት ማለት ነው።

የፎቶው ባለመብት, PHOTOPQR/LE PROGRES/Photo Jean-Pierre BALFIN
ሜሪ አሚል፣ 36፣ ፈረንሳይ
ሜሪ አሚ በቀድሞ ባለቤቷ ሴባስቲየን ቫይላት በጩቤ ተወግታ ተገደለች።
ባልና ሚስቱ የተፋቱት ከአራት የጋብቻ አመታት በኋላ ነው።
ለፖሊስ ከመናዘዙ በፊት በጩቤ የገደላት ሲሆን፤ ከጥቂት ቀናት በኋላም በእስር ቤት ራሱን ገድሎ ተገኘ።
ሜሪ አሚል በምትነግድበት የልብስ ሱቅም አካባቢ የተለያዩ ግለሰቦች የማስታወሻ አበባ አስቀምጠዋል።

የፎቶው ባለመብት, PHOTOPQR/LE PROGRES/Photo Jean-Pierre BALFIN

ምንም እንኳን እነዚህ የግድያ ዜናዎች በሚዲያ ቢሰሙም ቁጥራቸው በውል የማይታቅ ሴቶች ግድያ ሪፓርትና ምርመራ ሳይደረግበት እንደዋዛ ያልፋል። ይህንንም በማየት የሴቶች ግድያ ምን ቢሆን ነው ሪፖርት ለመደረግ የሚበቃው የሚል ጥያቄ ያስነሳል።

ሪፖረተር፦ ክሩፓ ፓዲ
ፕሮዲውሰር፦ ጆርጊና ፔርስ
ምርምር፦ ቢቢሲ ሞኒተሪንግ












