በምሥራቅ ወለጋ በተፈፀመ ጥቃት ሁለት ሰዎች ተገደሉ

የፎቶው ባለመብት, Google Map
በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ወለጋ ወሊጋልቴ ገጠር ቀበሌ ውስጥ ሁለት ግለሰቦች በወጣቶች በተፈፀመባቸው ጥቃት መገደላቸውን የዓይን እማኞች ገለጹ።
ቅዳሜ አመሻሽ ላይ የተደራጁ ወጣቶች መኪና በማስቆም ሁለቱን ግለሰቦች በኃይል ከመኪና ላይ በማውረድ በድንጋይ ደብድበው መግደላቸውን የዓይን እማኞች የገለጹ ሲሆን፤ የሲቡሴ ወረዳ የፖሊስ አዛዥ የሆኑት ምክትል ኮማንድር ጫላ ኦቦሶ ደግሞ ሁለቱ ሰዎች በድንጋይ መገደላቸውን አረጋግጠው የግድያው ምክንያት በግለሰቦች መካከል በነበረ ግጭት ነው ብለዋል።
ምክትል ኮማንደር ጫላ ኦቦሶ ሟቾቹ ፍፁም መሃሪና ሃፍቱ ሃገዞም ይባላሉ ብለዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ሁለቱ ግለሰቦች 1977 ዓ.ም በህጻንነት ዕድሜያቸው በሰፈራ ከትግራይ ወደዚህ ወደ አካባቢው መምጣታቸውን ይናገራሉ።
አቶ ፍጹም የተባለው ሟች መቀሌ ከተማ ቤት ሰርቶ ወደዚያው ለመመለስ እቃ ጭነው በመሄድ ላይ ሳሉ እንደተገደሉ የዓይን እማኞች የገለጹ ሲሆን የፖሊስ አዛዡ ግን ይህ መረጃ የለኝም ብለዋል።
የሟች ቤተሰቦች እንደሚሉት ከሆነ አስክሬን ከፖሊስ ተቀብለው ለመውሰድ ሙከራ ቢያደርጉም እዚሁ ቅበሯቸው የሚል ማስፈራሪያ ደርሶናል ብለዋል።
ምክትል ኮማንድር ጫላ ኦቦሶ የሟቾች አስክሬን ለምረመራ ወደ ሆስፒታል ተልኮ ከተመለሰ በኋላ እዛው ወሊገልቴ በተባለው ቀበሌ ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት ዛሬ ስርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል ብለዋል።
ምክትል ኮማንደር ጫላ የቤተሰብ አባላቱ አስክሬን ይዘው እንዳይሄዱ ስለመከልከላቸው እንደማያውቁ ተናግረው፤ ሟቾቹ በምሥራቅ ወለጋ ከ30 ዓመታት በላይ መኖራቸውን እና ሌሎች የቤተሰብ አባላሎቻቸውም በቀበሌዋ እንደሚኖሩ ጨምረው ተናግረዋል።
ከተፈጸመው ወንጀል ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ሥር የዋለ ሰው ስለመኖሩ የተጠየቁት የፖሊስ አዛዥ ''በምረመራ ላይ ያለ ጉዳይ ስለመሆኑ በጉዳዩ ላይ መረጃ መስጠት አልችልም'' ብለዋል።















