ቀጥታ, ኢራን 'እውነተኛውን ስምምነት' ሙሉ በሙሉ እስክታከብር ድረስ የአሜሪካ ኃይሎች በቀጣናው እንደሚቆዩ ትራምፕ ተናገሩ

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በግል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን “ትክክለኛውን ስምምነት ሙሉ በሙሉ የማታከበር ከሆነ “ማንም ካየው በላይ ጠንካራ የሆነ ጥቃት” እንደሚፈጸም በመግለጽ አስጠነቀቁ። ፕሬዚዳንቱ በትሩዝ ሶሻል ላይ ባጋሩት ጽሑፍ “ተኩስ ከሚጀመረው ግዙፍ እና የተሻለ እንዲሁም ማንም ካየው በላይ ጠንካራ ሆኖ ነው” በማለት አስጠንቅቀዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የኢራን ፕሬዝዳንት እጆቻችን “አሁንም ቃታው ላይ ናቸው” ሲሉ አስጠነቀቁ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን እስራኤል ሊባኖስ ላይ የምትፈጽመው ጥቃት "ግልጽ የተኩስ አቁም ጥሰት” ነው አሉ።

    የእስራኤል ጥቃቶች መቀጠላቸው ሊደረስ ለሚችል ስምምነት ቁርጠኝነት እንደሚጎድል የሚሳይ “አደገኛ ምልክት” ነው ሲሉም ወቅሰዋል።

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ይህንን አስተያየት በኤክስ ገጻቸው ያሰፈሩት የእስራኤል ጦር የሄዝቦላህ ዒላማዎች እንደሆኑ በገለጻቸው የሊባኖስ ስፍራዎች ላይ ከ100 በላይ የአየር ጥቃቶችን በፈጸመ ማግሥት ነው።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያናሁ “አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ” ሄዝቦላህ ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በዛሬው ዕለት ተናግረዋል።

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን በኤክስ ልጥፋቸው የጥቃቶች መቀጠል ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን ድርድር ወደ “ትርጉም የለሽነት” እንደሚያወርደው ገልጸዋል። የኢራን እጆች “ቃታው ላይ ሆነው እንደሚቀጥሉም” ጽፈዋል።

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ በበኩላቸው “የተኩስ አቁም ጥሰቶች ግልጽ ዋጋ” እንደሚያስከፍሉ እና “ጠንካራ ምላሽ” እንደሚያስከትሉ ተናግረዋል።

    ሊባኖስ “የማትነጠል የተኩስ አቁሙ አካል” መሆኗን ገለጹት አፈ ጉባኤው ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ፤ “ለክህደት እና ማፈግፈግ የሚሆን ቦታ እንደሌለ” አሳስበዋል።

    “በአስቸኳይ እሳቱን አጥፉ” ሲሉም አክለዋል።

  2. ዩናይትድ ኪንግደም፤ እስራኤል በሊባኖስ የምትፈጽመውን ጥቃት አወገዘች

    የዩናይትድ ኪንግደም መከላከያ ሚኒስትር ጆን ሄሊ አገራቸው የኢራን ጦርነትን ለማስቆም የተደረገውን የተኩስ አቁም እንደምትደግፍ እና እንዲዘልቅ እንደምትፈልግ ገልጸው፤ በሊባኖስ የሚታየውን የጥቃት መባባስ አወገዙ።

    የሩሲያ ሰርጓጅ መርከቦች እንቅስቃሴን ተመለከተ ዛሬ መግለጫ የሰጡት ሚኒስትሩ፤ የተኩስ አቁሙ ይዘልቃል ብለው ያስቡ እንደሆነ ከቢቢሲ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።

    “የተኩስ አቁሙን በበጎን እንቀበለዋለን። እንዲዘልቅ እንፈልጋለን። እንዲጠናከር ለማድረግ የራሳችንን ድርሻ እንወጣለን” ብለዋል።

    መከላከያ ሚኒስትሩ አክለውም፤ “ሊባኖስ ውስጥ የሚታየውን [የጥቃት] መባባስ እናወግዛለን። የእስራኤል ሊባኖስ ግጭት በተኩስ አቁሙ ማዕቀፍ ውስጥ እንዲካተት እንፈልጋለን፤ ምክንያቱም መላው የመካከለኛው ምሥራቅ ቀጣና ወደ ትልቅ መረጋጋት ተመልሶ መመልከት እንፈልጋለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    ሄሊ በመግለጫው ዩናይትድ ኪንግደም የኢራን ጦርነትን በተመለከተ የያዘችው አቋም እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የዩናይትድ ኪንግደም ጦርን ወደ መካለኛው ምሥራቅ ማሰማራት “የብሪታኒያን ብሔራዊ ጥቅም” እንዳልሆነ አስረድተዋል።

    “በመካከለኛው ምሥራቅ እንደሆነው፤ ቀውስ በከፍተኛ ሁከት እና አደገኛ በሆነ ሁኔታ በሚፈነዳበት ወቅት፤ ሰዎች ለምን የዩኬ ወታደራዊ ይዞታዎች ችግሩን ለመፍታት አልተሰማሩም የሚል ጥያቄ ማንሳታቸውን እረዳለሁ” ብለዋል።

    “ነገር ግን ይሄ የብሪታኒያ ብሔራዊ ጥቅም አይደለም” ሲሉ ተናግረዋል።

    “ግዙፎቹ ስጋቶች ብዙውን ጊዜ የማይታዩ እና ድምጽ አልባ መሆናቸውን” የጠቀሱት መከላከያ ሚኒስትሩ፤ የመከላከያ ፍላጎቶች እየጨመሩ በመምጣታቸው የዩናይትድ ኪንግደም "ሀብቶቻችንን የተሻለ ውጤት ባላቸው [ጉዳዮች ላይ] ማሰማራት” አለብን ብለዋል።

  3. ሆርሙዝ ተከፍቶ የሚቆየው አሜሪካ ጥቃቶችን እስካቆመች ድረስ መሆኑን ኢራን አስታወቀች

    አሜሪካ ስታካሂድ የቆየውን “የወረራ ጥቃት” እስካቆመች ድረስ ለሳምንታት ተዘግቶ የቆየው የሆርሙዝ ወሽመጥ መልሶ እንደሚከፈት ኢራን አስታወቀች።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳኢድ ኻቲብዛዴህ እንደተናገሩት አገራቸው መርከቦች በወሳኙን የባሕር መተላለፊያ በኩል እንዲተላፉ “ደኅንነታቸው የተጠበቀ እንዲሆን” እንደምታደርግ ገልጸዋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ጦርነት እስከከፈተችበት ጊዜ ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥ ለሺዎች ዓመታት ከፍት ሆኖ መቆየቱን ጠቅሰው፤ አሁንም መተላለፊያው ክፍት የሚሆነው እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመውን ጦርነት በመጥቀስ “አሜሪካ በተግባር ወረራው እንዲሆም” ስታደርግ ብቻ ነው ብለዋል።

    ባለሥልጣኑ ጨምረውም አገራቸው “ለዓለም አቀፍ ሕጎች እና ደንቦች እንድምትገዛ” ነገር ግን ሆርሙዝ የዓለም አቀፍ ውሃ አካል ባለመሆኑ፣ በወሽመጡ በኩል ያለ ችግር ለማለፍ “የኢራን እና የኦማን መልካም ፈቃድ ያስፋልጋል” ብለዋል።

    በሰላም በሆርሙዝ በኩል ማለፍ ማለትን በተመለከተ ኢራን የውሃ አካሉ “ሰላማዊ” እንዲሆን እንደምትፈልግ ነገር ግን ይህ የሚሆነው ሌላውም አካል ተመሳሳዩን ሲያደርግ እንደሆነ እና አገራቸው ባሕረ ሰላጤውን “የጦር መርከቦች”ያላግባብ እንዲጠቀሙበት አትፍቅድም ብለዋል።

  4. ስታርመር ለባሕረ ሰላጤው አገራት ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደ መደራደሪያ መያዝ የለባትም አሉ

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የገቡት የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ኢራን “የሆርሙዝ ወሽመጥን መደራደሪያ” ማድረግ የለባትም አሉ።

    ስተርመር ከባሕረ ሰላጤው አገራት የመከላከያ ተወካዮች ጋር ባደረጉት ንግግር አገራቸው በጦርነቱ ላይ ቋሚ አቋም ማንፀባረቋን ያነሱ ሲሆን፤ ግጭቱ እንዲረግብ እና ዘላቂ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ ጥሪ አቅርበዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሆርሙዝ ወሽመጥ ጉዳይ አገራት በአንድ ላይ በመስራት መፍትሔ መፈለግ ይገባቸዋል ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ተኩስ የማቆም ስምምነት ላይ ከደረሱ በኋላ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ያለፈቃድ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማለፍ የሚፈልግ መርከብ ዒላማ እንደሚደረግ እና ጉዞው እንደሚዘገይ አስታውቋል።

    የዋይት ሐውስ ፕሬስ ኃላፊ ካሮሊን ሌቬት ግን የሆርሙዝ ወሽመጥ ተዘግቷል የሚሉ ሪፖርቶች ሐሰተኛ ናቸው ብለዋል።

  5. ኔታንያሁ እስራኤል “አስፈላጊ በሆነ ጊዜ” ሄዝቦላህ ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም ተናገሩ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እስራኤል “አስፈላጊ በሆነ ጊዜ” ሄዝቦላህ ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም ተናገሩ።

    እስራኤል ከዚህ ቀደም አሜሪካ እና ኢራን የደረሱት የተኩስ አቁም ስምመምነት ሊባኖስን እንደማያካትት ተናግረው ነው።

    ኢራን ግን እስራኤል ሊባኖስ ላይ የፈጸመችው ጥቃት የስምምነቱ “ከባድ ጥሰት” ነው ብላለች።

    ኔታንያሁ “መልዕክታችን ግልጽ ነው። ማንም ከእስራኤል ሰላማዊ ዜጎቻችን በተቃራኒ የቆመ ዒላማ ይሆናል” ብለዋል።

    “በሰሜን የሚገኙ ነዋሪዎችን ሙሉ ደኅንነት እስክናረጋግጥ ድረስ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ ሄዝቦላህን እንደበድባለን።”

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት የእስራኤል መከላከያ የሄዝቦላህ ዋና ፀሐፊ ናይም ቃሰም የወንድም ልጅ የሆነውን አሊ ዩሱፍ ሃርሺን መገደሉን ካስታወቀ በኋላ ነው።

  6. በሊባኖስ እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት በ24 ሰዓታት ውስጥ ከ200 በላይ ሰዎች ተገደሉ

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር ባለፉት 24 ሰዓታት በመላ አገሪቱ የተፈጸመ የእስራኤል ጥቃትን ተከትሎ 203 ሰዎች መገደላቸውን እና ከ1000 በላይ ሰዎች መቁሰላቸውን ገለጸ።

    ኢራን በበኩሏ በሊባኖስ ላይ እየተፈጸመ የሚገኘው ድብደባ ከአሜሪካ የተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ የተፈጸመ “ከባድ ጥሰት” ነው ስትል ተናግራለች።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር በሊባኖስ ላይ የሚፈጸመውን ጥቃት በተመለከተ ከአሜሪካ ጋር ረቡዕ ምሽት በአደራዳሪዋ ፓኪስታን በኩል ንግግሮች እንደነበሩ ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት የሚቆይ ጊዜየዊ የተኩስ አቁም ስምምነት ማድረጋቸወን ተከትሎ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ "ሊባኖስን አያካትትም" በማለት መጠነ ሰፊ ጥቃት ከፍተዋል።

    ይህንንም ተከትሎ የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ "በተቻለ መጠን ጥቃቱን እንዲየስቆምላቸው" ተማጽኖ አቅርበዋል።

    ናዋፍ ሳላም የእስራኤል ጦር ጥቃቶች ለዓለም አቀፍ ሕግ "ፍፁም ቸልተኝነት" አሳይተዋል በማለት "ሁሉም የሊባኖስ ወዳጆች እነዚህን ጥቃቶች በሁሉም መንገዶች ለማስቆም እንዲረዱን ጥሪ እናቀርባለን" ብለዋል።

  7. እስራኤል በሊባኖስ ላይ የፈጸመችውን ጥቃት እነማን አወገዙ?

    የዩኬ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዬቬት ኩፐር እስራኤል በሊባኖስ ላይ የፈጸመቸውን ጥቃት “ሙሉ በሙሉ ስህተት” ሲሉ ገልጸውታል። ሌሎች የአውሮፓ አገራትም የአየር ድብደባውን አውግዘዋል።

    የፈረንሳይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዢን ኖኤል ባሮት “ተቀባይነት የሌለው” ሲሉ ያወገዙት ሲሆን፣ ኢራንም የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ለመታጠቅ የምታደርገውን ጥረት እንዲሁም ለሄዝቦላህ እና ለሐማስ የምትሰጠውን ድጋፍ መተው አለባት ብለዋል። የእስራኤል ጥቃት “በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰውን ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ዝቅ የሚያደርግ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም” ሲሉ አክለዋል።

    የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ በበኩላቸው “መመለሻ የሌለው ነጥብ ላይ ደርሰናል፤ አሁን ግን በቁርጠኝነት ሊተገበር የሚገባው የሰላም ተስፋ እየጠበበ ነው” ብለዋል።

    ስፔን በቴህራን የሚገኘው ኤምባሲዋን ዳግም ልትከፍት መሆኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ተናግረዋል። ሆዜ ማኑኤል አልባሬሰ “የተኩስ አቁሙን በግልጽ ጥሳለች” ሲሉ እስራኤልን ወንጅለዋል። አክለውም “የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው” ሲሉ ኮንነውታል።

  8. የኢራን ሚኒስትር እስራኤል በሊባኖስ የፈጸመችው ድብደባ የተኩስ አቁሙ “ከባድ ጥሰት ነው” ሲሉ ለቢቢሲ ተናገሩ

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳይድ ኻቲብዛድ ከቢቢሲ ቱደይ ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቆይታ እስራኤል ረቡዕ ዕለት በሊባኖስ የፈጸመችው ድብደባ የተኩስ አቁሙ “ከባድ ጥሰት ነው” አሉ።

    ሚኒስትሩ አሜሪካ ኢራን ላይ ጦርነት ከመክፈቷ በፊት ለዘመናት ክፍት ሆኖ ለዘለቀው የሆርሙዝ ወሽመጥ ቴህራን “ደኅንነቱ የጠበቀ እንቅስቃሴ” እንደምትሰጥ ገልጸዋል።

    ሆኖም ወሽመጡ ዳግም የሚከፈተው “አሜሪካ በትክክል ከጥቃቷ ስትታቀብ” እንደሆነ እስራኤል ሊባኖስ ላይ የፈፀመችውን ጥቃት በማመልከት ገልፀዋል።

    ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ኢራን “ለዓለም አቀፍ መርኅ እና ሕግ ተገዢ” እንደምትሆን ጠቅሰው፤ ሆኖም ግን የሆርሙዝ ወሽመጥ ዓለም አቀፍ ውሃ እንዳልሆነ እና ደኅንነቱ የተጠበቀ መተላለፊያ “በኢራን እና ኦማን መልካም ፈቃድ” ላይ የተመሠረተ ነው ብለዋል።

    ሚኒስትሩ ደኅንነቱ የተጠበቀ መተላለፊያ ማለት ኢራን በእያንዳንዱ መርከብ ክፍያ መጣል ወይም ለመደብደብ ማስፈራራት ማለት ነው ተብለው ተጠይቀዋል።

    ሚኒስትሩ በምላሻቸው ኢራን ወሽመጡ “ሰላማዊ” እንዲሆን እንደምትሻ ጠቁመው፤ ሆኖም ደኅንነቱ የተጠበቀ መተላለፊያ ሁለት ወገን እንደሆነ እና ሰርጡ “ለጦር መርከቦች ያለአግባብ ጥቅም ላይ እንዲውል” አንፈቅድም ብለዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ አቁም ላይ መድረሳቸው ይፋ ቢደረግም እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት መፈጸም በመቀጠሏ ትናንት ለዋይት ሐውስ ጠቅለል ያለ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    “በአንድ ግዜ ኬክ ሊኖርህም ልትበላው አትችልም” በማለት የተኩስ አቁም ላይ ተደርሶ ሊባኖስን መደብደብ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ተናግረዋል።

    አክለውም በስምምነቱ ላይ ሊባኖስ መጠቀሷን በማንሳት የአሜሪካ አጋር የሆችው እስራኤል ግን “ጭፍጨፋ” መፈጸሟን በመጥቀስ ወንጅለዋል።

    አሜሪካ ጦርነት ወይም ሰላም እንደምትፈልግ “መምረጥ አለባት” ያሉት ሚኒስትሩ ሁለቱም በተመሳሳይ ወቅት ሊኖራት አይችልም ብለዋል።

    እስራኤል በሊባኖስ የምታካሄደውን ድብደባ ከቀጠለች ከስምምነቱ ይወጡ እንደሆን የተጠየቁት ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ “በአጠቃላይ መካከለኛው ምሥራቅ ደህንት ላይ ነው ትኩረታችን” ሲሉ መልሰዋል።

    ኢራን ሄዝቦላህ ሮኬት መተኮሱን እንዲያቆም ታደርግ እንደሆን ሲጠየቁ ስምምነቱ ሊባኖስን ያካተተ ነው ኢራን እና አጋሮቿ “የተኩስ አቁሙን ለመቀበል” ፈቃደኞች ናቸው ብለዋል።

  9. የአሜሪካ-ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት ‘አጠራጣሪ’ ቢሆንም የኢራን ተደራዳሪዎች ወደ ፓኪስታን አቀኑ

    የኢራን ተደራዳሪዎች ልዑክ ከአሜሪካ ጋር ጦርነቱን ለማቆም ወደ ፓኪስታን ማምራቱን በፓኪስታን የኢራን አምባሳደር አረጋግጠዋል።

    ልዑኩ ቅዳሜ ከአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዴ ቫንስ ጋር ይገናኛል።

    በፓኪስታን የኢራን አምባሳደር ሬዛ አሚሪ ሞግሃደም በኤክስ ገፃቸው ድርድሩ “ኢራን ባቀረበችው ባለ 10 ነጥብ ምክረ ሐሳብ” ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

    ድርድሩ በየትኛው አገር ባቀረበው ነጥብ ላይ ነው የሚለው አወዛጋቢ ጉዳይ ሆኗል።

    አምባሳደሩ ንግግሩ የእስራኤል አገዛዝ የዲፕሎማቲክ ጥረቶችን ለማሰናከል በተደጋጋሚ የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ ኢራናውያን ጥርጣሬ ባደረባቸው ሰዓት እንደሚካሄድም ጠቅሰዋል።

  10. ትራምፕ ኢራን “ትክክለኛውን ስምምነት” እስክታከብር ድረስ ሲሉ ምን ማለታቸው ነው?

    አሜሪካ እና ኢራን ያወጁት ለሁለት ሳምንት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት እርስ በእርሱ የሚጣረስ ነው።

    አለመግባባቱ የመጣው ባለ አስር ነጥብ ዕቅድ በሚል እየተዘዋወረ ካለው ሰነድ ጋር ተያይዞ ነው።

    ትራምፕ “በዩናይትድ ስቴትስ ተቀባይነት ያለው እና አንድ ትርጉም ያለው” ስምምነት ብቻ መኖሩን ተናግረዋል።

    ይህንንም ትክክለኛ ስምምነት በሚል በመጥራት “የኒውክሌር ጦር መሣሪያዎች እንደማይኖር እንዲሁም የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል፤ ደህንነቱም የይጠባቃል” የሚል መሆኑን ጠቅሰዋል።

    በኢራን ወገን ግን የተለያዩ የስምምነት ሰነዶች ይገኛሉ።

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን በኢራን፣ ኢራቅ፣ የመን እና ሊባኖስ የሚካሄደውንው ውግያ የሚያስቆም እንዲሁም የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መክፈት እና አሜሪካ ማዕቀቦችን ለማንሳት ሙሉ ቁርጠኝነት እንዳላት የሚግለጽ ሰነድን አቅርቧል።

    በኋላ ላይ ደግሞ የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ይፋ ያደረገው ባለ አስር ነጥብ ዕቅድ ዩራኒየም ማበልጸግ እና ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደምትቆጣጠር የሚሉ ሃሳቦችን ይዞ መጥቷል።

    በደህንነት ምክር ቤቱ መግለጫ ውስጥ በእንግሊዘኛ የቀረበው መግለጫ ላይ ዩራኒየም ማበልጸግ የሚለው ሃሳብ በኋለ ላይ እነዲወጣ ተደርጓል።

    ትራምፕ የማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፋቸው ላይ በተኩስ አቁሙ ሊባኖስ ስለመካተቷ ያሉት ነገር የለም። ነገር ገን በተኩስ አቁሙ ዙሪያ ላለመግባባት ምክንያት ከሆኑት ጉዳዮች መካከል አንዱ ግን የሊባኖስ አለመካተት ነው።

  11. የአሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት ጥርጣሬ ማሳደሩን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    አሜሪካ ኢራንን ለሁለት ሳምንት ላለማጥቃት ከተስማማች በኋላ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳይቶ የነበረ ቢሆንም ሐሙስ ጠዋት ግን ዳግም ጨምሯል።

    በዓለም አቀፍ ገበያ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በበርሚል 2.2 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 96.70 ዶላር ገብቷል። በአሜሪካ ገበያ ደግሞ ከዚህም ከፍ በማለት በ2.8 በመቶ በመጨመር 96.90 ዶላር ገብቷል።

    እስራኤል በሊባኖስ ላይ ተከታታይ ጥቃት መክፈቷን ተከትሎ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ላይ ቀዳዳዎች እንዲታዩ አድርጓል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስምምነቱን ካበሰሩ በኋላ ረቡዕ ዕለት ብሬንት ነዳጅ በ15 በመቶ በመቀነስ አንድ በርሜል 92 ዶላር ገብቶ ነበር። በኋላ ላይ ግን የነዳጅ ዋጋ ከዚህ ትንሽ ከፍ ብሏል።

    የነዳጅ ዋጋ ጦርነቱ የካቲት 21/ 2018 ዓ.ም. ከመጀመሩ በፊት ከነበረበት ዋጋ በጣም ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

  12. የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር የአሜሪካ-ኢራንን የተኩስ አቁም ስምምነት ለማፅናት በርካታ ሥራዎች ገና ይቀራሉ አሉ

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር ለሁለት ሳምንታት የታወጀውን የአሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት ለማፅናት እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት “በርካታ ሥራዎች መሰራት” አለባቸው ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ረቡዕ ዕለት ስምምነቱን ለመደገፍ እና ለማፅናት የዲፕሎማሲያዊ ጥረት ለማድረግ የባሕረ ሰላጤው አገራት ጉብኝት አካል በሆነው ጉዟቸው ሳዑዲ አረቢያ ገብተዋል።

    ሰር ኪር ስታርመር ስምምነቱን ተከትሎ “እፎይታ” ስሜት እንዳለ ጠቅሰው ጊዜው ገና መሆኑን ግን ተናግረዋል።

    የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስተያየት የተሰማው የኢራን መገናኛ ብዙኃን እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት መፈፀሟን ተከትሎ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በሆርሙዝ ማለፍ ማቆማቸውን ከዘገቡ በኋላ ነው።

    በተኩስ አቁም ድርድሩ አሸማጋይ ሆና ያገለገለችው ፓኪስታን እና ኢራን ስምምነቱ ሊባኖስንም እንደሚያካትት ቢናገሩም፤ እስራኤል ግን ስምምነቱ ሊባኖስን አይጨምርም ብላለች።

    ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በሆርሙዝ ሰርጥ ማሳለፍ የአሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት ቁልፍ አካል ነው።

    የዩናይትድ ኪንገደም እና የሳዑዲ ወታደሮችን ያነጋገሩት ስታርመር “እንደምታውቁት በርካታ መሰራት ያለባቸው ሥታዎች አሉ፤ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ቋሚ እንዲሆን እና ሁላችንም ማየት የምንፈልገውን ሰላም ለማምጣት በርካታ ሥራዎች መሰራት አለባቸው” ብለዋል።

    ስታርመር ወደ ጂዳ ተጉዘው የሳዑዲውን አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሳልማንን አግኝተዋል።

    ይህን ንግግር ተከትሎ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ ሁለቱ መሪዎች የሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች ያለስጋት እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ የዩኬ በአጋሮች ዘንድ ስምምነት እንዲኖር በምታደርገው ጥረት ላይ እንደተነጋገሩ ገልፀዋል።

  13. ኢራን የተኩስ አቁሙ ሦስት አንቀጾች “በግልጽ እና በይፋ ተጥሰዋል” አለች

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ ትናንት ምሽት በኤክስ ገጻቸው ላይ በጻፉት ጽሑፍ ኢራን ካቀረበችው ባለ 10 ነጥብ ምክረ ሀሳብ መካከል ሦስት አንቀጾች “በግልጽ እና በይፋ ተጥሰዋል” አሉ።

    አፈ ጉባዔው በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ የሁለትዮሽ የተኩስ አቁም ስምምነት ወይም ድርድር “ምክንያታዊ አይሆንም” ብለዋል።

    ጋሊባፍ ሊባኖስ በዚህ ምክረ ሀሳብ ውስጥ ተካትታ እንደነበር የጠቀሱ ሲሆን ዋይት ሐውስ ግን ይህንን አስቀድሞ ውድቅ አድርጓል።

    በተጨማሪም አንድ ሰው አልባ አውሮፕላን ወደ ኢራን ደቡባዊ ፋርስ ግዛት መግባቱን አፈ ጉባዔው ጠቅሰዋል።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት እንዲህ አይነት ክስተት ስለመፈጠሩ "እንደማያውቅ" ለቢቢሲ ተናግሯል።

    አፈ ጉባዔው በሦስተኛው አንቀጽ ላይ ኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብት የሚል ተካትቷል ያሉ ሲሆን ይህም የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የጸጥታ ምክር ቤት በፋርስ ቋንቋ በሰጠው እና በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን በተነበበው መግለጫ ውስጥ ተካትቷል።

    የአሜሪካ እና የእስራኤል በኢራን ጦርነት የተጀመረው የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ሲሆን ይህም በኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ የተደረገው ድርድር ያለውጤት ከተጠናቀቀ ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

    አንዳንድ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች የትራምፕ አስተዳደር አፈ ጉባኤ ጋሊባፍን የወደፊቷ ኢራን መሪ ለማድረግ እያጤነ መሆኑን ጠቁመዋል።

  14. ትራምፕ ኢራን “ለትክክለኛው ስምምነት” ሙሉ በሙሉ እስክትገዛ ድረስ ጦሩ በተጠንቀቅ እንዲቆይ አዘዙ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በግል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን “ትክክለኛውን ስምምነት ሙሉ በሙሉ የማታከበር ከሆነ ማንም ካየው በላይ ጠንካራ የሆነ ጥቃት” እንደሚፈጸም በመግለጽ አስጠነቀቁ።

    ፕሬዚዳንቱ በትሩዝ ሶሻል ላይ ባጋሩት ጽሑፍ “ተኩስ የሚጀመረው ግዙፍ እና የተሻለ እንዲሁም ማንም ካየው በላይ ጠንካራ ሆኖ ነው” በማለት አስጠንቅቀዋል።

    አክለውም ሁሉም የአሜሪካ ጦር መርከቦች፣ አውሮፕላኖች እና ወታደሮች እንዲሁም ተጨማሪ ጦር መሣሪያዎች ዝግጁ እንዲሆኑ አዝዘዋል።

    ረቡዕ ዕለት አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ላይ መድረሳቸውን ተከትሎ የሚፈጸሙ ጥቃቶች ቢቆሙም እስራኤል ግን በሊባኖስ ላይ ጠንካራ እና ገዙፍ ድብደባዎችን መፈጸሟን አስታውቃለች።

    በዚህም የተነሳ የሄዝቦላህ አዛዠን ጨምሮ ከ180 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰምቷል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመው ጥቃት በአስቸኳይ ካልቆመ “ጸጸት የሚያስከትል ምላሽ” እንደሚሰጥ ዝቷለ።

    የትራምፕ ማስጠንቀቂያ የተሰማው የአብዮታዊ ዘቡ ማስጠንቀቂያን ተከትሎ ነው።

    “ከዚህ ቀደም በከፍተኛ ደረጃ አቅሙ የተዳከመውን ጠላት ለመምታት እና ለማጥፋት ተገቢ እና አስፈላጊ የሆነ ማንኛውም ነገር ትክክለኛው ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እስኪሆን ድረስ በኢራን እና በዙሪያው አካባቢ ይቆያል” ብለዋል ፕሬዝዳንት ትራምፕ።

    ትራምፕ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰው “ትክክለኛ ስምምነት” የማይከበር ከሆነ ግን “ሊሆን የሚችል አይመስለኝም” በማለት “ተኩስ የሚጀመረው ግዙፍ እና የተሻለ ሆኖ እንዲሁም ማንም አይቶት ከሚያውቀው በላይ ጠንካራ ሆኖ ነው” ብለዋል።

    ቀደም ብሎ “ምንም እንኳ ሐሰተኛ መረጃዎች ስለ አገሪቱ ቢኖሩም” ምንም ዓይነት የኒውከክሌር ጦር መሣሪያ እንደማይኖር እና የሆርሙዝ ወሽመጥ ደህንነቱ ተጠብቆ እንደሚከፈት ከስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር” ብለዋል።

    ይህ በእንዲህ አንዳለ “ታላቁ ጦራችን መሣሪያውን እየጫነ እና እያረፈ ቀጣዩን ድል ይጠብቃል፤ አሜሪካ ተመልሳለች” ብለዋል።

  15. የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሊባኖስ ላይ የሚፈጸመው ጥቃት ከቀጠለ “ጸጸት የሚያስከትል ምላሽ” እሰጣለሁ ሲል አስጠነቀቀ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመው ጥቃት በአስቸኳይ ካልቆመ “ጸጸት የሚያስከትል ምላሽ” እንደሚሰጥ መዛቱን የኢራን መንግሥት የዜና ወኪል ዘገበ።

    አብዮታዊ ዘቡ በቴሌግራም ገጹ ላይ ባስተላለፈው መልዕክት “ቃሏን ላጠፈችው ዩናይትድ ስቴትስ እና ጽዮናዊት አጋሯ ከባድ ማስጠንቀቂያ አለን” ብሏል።

    “በውዷ ሊባኖስ ላይ የሚፈጸመው ጥቃት አሁኑኑ ካልቆመ የገባነውን ቃል በመፈጸም ጸጸት የሚያስከትል ጥቃት በቀጣናው ረባሽ ላይ እንሰነዝራለን” ሲል ዝቷል።

    የአገሪቱ ብሔራዊ የዜና ወኪል ኢርና የአብዮታዊ ዘቡ ባለሥልጣናትን በመጥቀስ “በኩሩው ሄዝቦላህ ላይ የሚፈጸም ጥቃት ኢራን ላይ እንደተፈጸመ ነው። ጦሩ ከባድ ምላሽ በጨካኙ ወንጀለኛ አገዛዝ [እስራኤል] ላይ ለመውሰድ እየተዘጋጀ ነው” ማለታቸውን ዘግቧል።

  16. እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው የአየር ድብደባ 89 ሰዎችን ሲገደሉ ከ700 በላይ ቆሰሉ

    እስራኤል በመላው ሊባኖስ ዛሬ ረቡዕ በፈጸመችው ጥቃት 89 ሰዎች ሲገደሉ ከ700 በላይ መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ለሮይተርስ ተናገሩ።

    ቃል አቀባዩ ጨምረው አንደተናገሩት በደቡባዊ ሊባኖስ ከሞቱት መካከል 12 የሕክምና ባለሙያዎች ይገኙበታል።

    የእስራኤል ሠራዊት በዛሬው ዕለት ባለፈው ወር በሊባኖስ የእግረኛ ወታደሮችን ካሰማራ ወዲህ “ግዙፍ የአየር ድብደባ” መፈጸሙን አስታውቋል።

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል በቴሌግራም ገጹ ላይ “ከጥቂት ሰዓታት በፊት” በቤይሩት የሄዝቦላህ አዛዥን መግደሉን አስታውቋል።

    ጦሩ ዝርዝር መረጃ እንደሚሰጥ አስታውቋል።

    የሊባኖስ ብሔራዊ የዜና ወኪል በቤይሩት እና ደቡባዊ ሊባኖስ ጥቃቶች መቀጠላቸውን ዘግቧል።

  17. ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ማለፍ ማቆማቸው ተዘገበ

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን እስራኤል የእግረኛ ጦሯ ወደ ሊባኖስ ከገባ ወዲህ ግዙፍ ያለችወን ድብደባ መፈጸሟን ተከትሎ በሆርሙዝ ወሽመጥ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ማለፍ ማቆማቸውን ዘገቡ።

    ኢራን እና አሜሪካ በደረሱት የተኩስ አቁም ላይ በባሕር ወሽመጡ በኩል ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እንዲያልፉ ማድረግ ቁልፍ የስምምነቱ አካል ነው።

    ነገር ግን ከኢራን እስላማዊ አብዮት ዘብ ጋር ግንኙነት ያለው ፋርስ ዜና ወኪል ዛሬ ማለዳ ከቴህራን ፈቃድ አግኝተው ሁለት ነዳጅ የጫኑ መርከቦች ማለፍ ችለው የነበረ ቢሆንም ከዚያ በኋላ ግን መርከቦች እንዳያልፉ ተደርገዋል።

    ዘ እስላሚክ ሪፐብሊክ የዜና ወኪል በበኩሉ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመውን የአየር ድብደባ በመቀጠሏ የመርከቦች ጉዞ መቋረጡን ዘግቧል።

  18. ምዕራባውያን ሁሉም ወገኖች በሊባኖስ ጭምር የተኩስ አቁሙን እንዲያከብሩ ጥሪ አቀረቡ

    የምዕራባውያን አገራት በኢራን "ፈጣን እና ዘላቂ ሰላም" እንዲመጣ እንዲሁም "ሁሉም ወገኖች" በሊባኖስ ጭምር የሁለት ሳምንቱን የተኩስ አቁም እንዲያከብሩ ጥሪ አቀረቡ።

    መግለጫው በዩናይትድ ኪንግደም፣ በፈረንሳይ፣ በጣሊያን፣ በጀርመን፣ በካናዳ፣ በዴንማርክ፣ በኔዘርላንድስ፣ በስፔን፣ በአውሮፓ ኮሚሽን እና በአውሮፓ ምክር ቤት መሪዎች ተፈርሟል።

    ፓኪስታንን እና ሌሎች አደራዳሪዎችን “ስምምነቱን ስላመቻቹ” በማመስገን ለሁለት ሳምንት የሚቆየው የተኩስ አቁም “መልካም” መሆኑን ገልጸዋል።

    መግለጫው "ቀጣዩ ግብ በመጪዎቹ ቀናት ጦርነቱ በፍጥነት እና በዘላቂነት በሚያበቃበት ሁኔታ ላይ ድርድር የሚደረግበት መሆን አለበት። ይህ ሊገኝ የሚችለው በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ብቻ ነው። በፍጥነት በድርድር ላይ ወደ ተደረሰ ተጨባጭ ስምምነት እንዲመጣ አጥብቀን እናበረታታለን" ይላል።

    የምዕራቡ አገራት መሪዎች በመግለጫቸው ስምምነቱ "የኢራንን ሕዝብ ለመጠበቅ በጣም አስፈላጊ ነው" ብለዋል።

    “ሁሉም ወገኖች የተኩስ አቁሙን በሊባኖስ ጭምር ተግባራዊ እንዲያደርጉ ጥሪ እናቀርባለን።”

  19. የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የእስራኤል ድብደባን እንዲያስቆም ጠየቁ

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም ከፍተኛ የአየር ድብደባ ከተፈጸመ በኋላ "የሊባኖስ ወዳጆች በሙሉ" የእስራኤልን ወታደራዊ እርምጃ "በሚችሉት መንገድ ሁሉ" እንዲያስቆሙ ተማጸኑ።

    ናዋፍ ሳላም በኤክስ ገጻቸው ላይ "እስራኤል በሊባኖስ በተለይም በዋና ከተማዋ ቤይሩት ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎች ያልታጠቁ ሰላማዊ ሰዎችን ሕይወት የቀጠፈ በሕዝብ በተጨናነቁ የመኖሪያ ሰፈሮች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች" ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጥሪ ያቀረቡት የእስራኤል ሠራዊት በሄዝቦላህ ላይ ዘመቻ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በተለየ በመላው ሊባኖስ ዛሬ “መጠነ ሰፊ ድብደባ” መፈጸሙን ካስታወቀ በኋላ ነው።

    ሳላም እንደሚሉት የእስራኤል ጦር ጥቃቶች ለዓለም አቀፍ ሕግ "ፍፁም ቸልተኝነት" አሳይተዋል።

    አክለውም "ሁሉም የሊባኖስ ወዳጆች እነዚህን ጥቃቶች በሁሉም መንገዶች ለማስቆም እንዲረዱን ጥሪ እናቀርባለን" ብለዋል።

    ሊባኖን 24 የተባለ የአረብኛ ዜና ወኪል በበኩሉ በኤክስ ገጹ ላይ በሊባኖስ የሚገኙ ሆስፒታሎች በተጎጂዎች መጨናነቃቸውን አጋርቷል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስትር በበኩሉ ዜጎች አውራ መንገዶችን ለአምቡላንሶች እንዲለቅቁ ጠይቋል።

    የሄዝቦላህ ደጋፊ የሆነው አል ማናር ቴሌቪዥን ጣቢያ ደግሞ እስራኤል በደቡባዊ ቤይሩት በፈጸመችው ጥቃት በርካቶች መሞታቸውን እና መጎዳታቸውን በቴሌግራም ገጹ ላይ ጽፏል።

    ኤልቢሲአይ የተባለ የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን በኤክስ ገጹ ላይ የአገሪቱን ጤና ሚኒስቴር ጠቅሶ በእስራኤል ጥቃት መቶዎች መሞታቸውን እና መጎዳታቸውን አጋርቷል።

    በመንግሥት የሚመራው የአገሪቱ የዜና ወኪል በበኩሉ በደቡባዊ ሊባኖስ አድሉን ከተማ በአንድ ቤት ላይ በተፈጸመ ጥቃት ሦስት ሴቶች መገደላቸውን ዘግቧል።

    አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ሲደርሱ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ይህ “ሊባኖስን አያካትትም” ብለዋል።

  20. የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ኢራን ከአሁን በኋላ ስጋት አትሆንም አሉ

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ኢራን ላለፉት 47 ዓመታት ስጋት ሆና ቆይታ የነበረ ቢሆንም “ከአሁን በኋላ ግን አትሆንም” አሉ።

    ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ለሁለት ሳምንት የሚቆይ የተኩስ አቁም ከተደረሰ በኋላ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።

    ፒት ሄግሴት ጋዜጣዊ መግለጫውን የሰጡት ከፔንታጎን የጋራ ወታደራዊ አዛዦች ሊቀ መንበር የሆኑት ጄነራል ዳን ኬን ጋር በመሆን ነው።

    ፒት ሄግሴት "ፕሬዚዳንት ትራምፕ ይህንን ቅጽበት ፈጥረዋል፤ ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ ለምናለች፤ ይህንንም ሁላችንም እናውቀዋለን" ሲሉ ተናግረዋል።

    ሄግሰት ኦፕሬሽን ኤፒክ ፉሪ “ታሪካዊ እና እጅግ አስደናቂ ነበር” ያሉ ሲሆን የአሜሪካ ጦር “የኢራንን ጦር አውድሟል” ብለዋል።

    ሄግሴት ጊዜያዊ የተኩስ አቁም የተደረሰበትን ዕለት “ለዓለም ሰላም ትልቅ ቀን” ሲሉ አሞካሽተዋል።

    አክለውም “በዓለም ግንባር ቀደም አሸባሪነትን የሚደግፍ መንግሥት ራሱን፣ ሕዝቡን ወይም ግዛቱን መከላከል ሙሉ በሙሉ አቅሙ የለውም” ሲሉ ተናግረዋል።

    ሄግሴት ዩኤስ የኢራንን ባሕር ኃይል እና አየር ኃይል ጠራርጎ ለማጥፋት የያዘችውን ወታደራዊ ዓላማ አሳክታለች - አሜሪካ "ሰማያቸውን” ትቆጣጠራለች ብለዋል።

    ኢራን የተኩስ አቁሙን የተቀበለችው “በከፍተኛ ጫና” መሆኑን ሚኒስትሩ ጠቅሰው ቴህራን የዋሺንግተንን ቅድመ ሁኔታዎች ባለትቀበል ኖሮ “ቀጥሎ ዒላማ የሚሆኑት ድልድዮቿ፣ የኃይል ማመንጫዎቿ፣ የነዳጅ እና ኢነርጂ መሠረተ ልማቶቿ ነበሩ” ሲሉ የፕሬዚዳንት ዛቻ ጠቅሰዋል።

    ኢራን መልሶ ለመገንባት አስርታት ዓመታትን ይወስድባት ነበር በማለት የግዛቲቱ መሪዎች ይህንን በመገንዘባቸው ከስምምነት ላይ መድረስን መርጠዋል ብለዋል።

    “ፕሬዚዳንት ትራምፕ የኢራንን ምጣኔ ኃብት በደቂቃዎች ውስጥ ማሽመድመድ አቅም ነበራቸው ነገር ግን ርህራሄን መርጠዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ሚኒስትሩ የተኩስ አቁሙ “ለእውነተኛ ሰላም እና ለእውነተኛ ስምምነትን” ዕድል እንደሚፈጥር ጠቁመው መስሪያቤታቸው “ለአሁኑ” የበኩሉን አድርጓል ፣ ግን ኢራን እያንዳንዱን ስምምነት ማክበሯን ለማረጋገጥ ዝግጁ ይሆናል” ብለዋል ።

    ሄግሴት እስራኤልን “ደፋር፣ ፈቃደኛ እና አቅም ያላትአጋር” በማለት ጠርተዋታል። የተቀረው ዓለም እና ሌሎች "የአሜሪካ አጋሮች ነን የሚሉ" አንዳንድ ማስታወሻዎችን መውሰድ አለባቸው ብለዋል።

    የፔንታጎን የጋራ ወታደራዊ አዛዦች ሊቀ መንበር የሆኑት ጄነራል ዳን ኬን በበኩላቸው የአሜሪካ ጦር “ከታዘዘ ወይም ጥቃት ዘመቻውን እንዲቀጥል ጥሪ ከቀረበለት ዝግጁ ሆኖ ይጠብቃል ብለዋል።

    “የአሜሪካ ወታደሮች ባለፉት 38 ቀናት እንዳሳየነው ፍጥነት እና ቆራጥነት የጥቃት ዘመቻውን እንድንቀጥል ከታዘዝን ወይም ከተጠራን ዝግጁ ሆነን እንጠብቃለን እና ያ እንደማይሆን ተስፋ እናደርጋለን።”