ልጇን አግታ ሸጣለች የተባለችው ደቡብ አፍሪካዊት እናት ተፈረደባት

የፎቶው ባለመብት, Executive Mayor Andrè Truter/ Facebook
የስድስት ዓመት ልጇን አግታ በሕገወጥ መንገድ አዘዋውራለች የተባለችው ደቡብ አፍሪካዊት እናት ላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ አሳለፈ።
ፍርድ ቤት ኬሊ ስሚዝ የተባለችው እናት እንዲሁ የወንድ ጓደኛዋ ዩአኪን አፖሊስ እና ጓደኛቸው ስቴቨኖ ቫን ራየን ጥፋተኛ ናቸው ሲል በይኗል።
ጆሽሊን የተባለችው የስድስት ዓመት ልጅ ከጠፋች አንድ ዓመት አልፏታል። በደቡብ አፍሪካዋ ኬፕ ታውን ከተማ ከሚገኘው ሳላዳና ቤይ አካባቢ ነበር ጆሽሊን የጠፋችው።
ሦስቱ ተጠርጣሪዎች ከዚህ ቀደም ጥፋተኛ አይደለንም ሲሉ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተው ነበር።
የጆሽሊን መጥፋት ደቡብ አፍሪካውያንን አስደንግጧል። እስካሁን ድረስም አልተገኘችም።
ዐቃቤ ሕግ የልጅቷ እናት "ሸጣታለች ወይም አዘዋውራታለች። አልያም ደግሞ ለውጣታለች" ሲል ክሱን አቅርቧል።
እናትየዋ ልጅቷ ጠፍታለች ብላ መዋሸቷንም ዐቃቤ ሕግ ገልጿል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የፍርድ ቤቱ ውሳኔ በተላለፈበት ቀን በርካታ ደቡብ አፍሪካውያን በአካባቢው ተሰባስበው ዜናውን ለመስማት ሲጠባበቁ ነበር።
በአካባቢው መጨናነቅ እንዳይፈጠር መንገዶች ተዘግተው ፖሊስም ተሰማርቷል።
የእናትየዋ ጎረቤት የነበረችው እና ዐቃቤ ሕግ ምስክር አድርጎ ያቀረባት ሎውሪንታ ሎምባርድ እንዳለችው፣ እናትየዋ "የሞኝ ሥራ ሠርቻለሁ" ብላ ልጇን ለባህላዊ ሐኪም መሸጧን ነግራታለች።
በደቡብ አፍሪካ ሳንጎማ ለሚባሉት ባህላዊ ሐኪሞች ልጇን መሸጧን ለፍርድ ቤት ገልጻለች።
"ጆሽሊንን ባህላዊው ሐኪም የወሰዳት ለዓይኗ እና ለቆዳዋ ሲል ነው" ብላለች።
በአካባቢው የሚያገለግሉ ፓስተርም ለፍርድ ቤት ቃላቸውን የሰጡ ሲሆን፣ የሦስት ልጆች እናት የሆነችው ኬሊ ልጆቿን በ1,100 ዶላር እንደምትሸጥ ስትናገር መስማታቸውን ገልጸዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ጆሽሊን መጥፋቷን ተከትሎ ደቡብ አፍሪካውያን አደባባይ ወጥተው ፍትህ እንዲገኝ ሲጠይቁ መቆየታቸው ይታወሳል።
በተፈጥሮዋ ሰማያዊ እና አረንጓዴ ዓይን የነበራት ጆሽሊን ለዓይኗ እንዲሁም ነጣ ለሚለው ቆዳዋ በሚል ለባህላዊ ሐኪም መሸጧ በፍርድ ቤት ተገልጿል።
ፍለጋው በስፋት ቢቀጥልም እስካሁን ድረስ የደረሰችበት ሊታወቅ አልቻለም።












