እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማን እንዲወደድ ያደረጉ ምክንያቶች

የእረኛዬ ድረማ ተዋንያን ከሆኑት መካከል ድርብ ወርቅ ሠይፉ (እማ ቸርነት) እና ሳያት ደምሴ (እናና)

የፎቶው ባለመብት, Arts TV

እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ በአርትስ ቴሌቭዥን በአራት ምዕራፎች በ48 ክፍሎች ሲተላለፍ ቆይቶ አርብ ነሐሴ 13/2014 ዓ.ም. ተጠናቋል።

ይህ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ በአዜብ ወርቁ፣ በቤዛ ኃይሉ እንዲሁም በቅድስት ይልማ የተጻፈ ሲሆን፣ ያዘጋጀችው ደግሞ ከደራሲዎቹ መካከል አንዷ የሆነችው ቅድስት ይልማ ነች።

እነዚህ ሦሰት ደራሲያን ለፊልም ጽሁፍ እንዲሁም ዝግጅት እንግዳ አይደሉም። በስማቸው በርከት ያሉ ሥራዎች ሰፍረው ይገኛሉ።

በጥምረት ግን ሲሰሩ ይህ የመጀመሪያቸው ነው።

እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቭዥን ድራማ መቼቱን ያደረገው ከከተማ ግርግር ርቆ፣ ሕይወት ስክን ብላ በምትፈስበት ገጠር ውስጥ ነው።

ይህ አብነት የተሰኘ የገጠር መንደር በምናብ የተፈጠረ ነው።

ይህች የገጠር መንደር ኢትዮጵያን እንድትመስል ተደርጋ ነው የተሳለችው።

በዚህ መንደር በፍቅር ተሳስበው የሚኖሩ ዘመዳሞች እና ጎረቤታሞች ፍቅራቸውን የሚነቀንቅ ተቀናቃኝ መጥቶባቸዋል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ይህ ተቀናቃኝ ባለሀብት ነው።

በሀብቱ ብዛት መሬታቸውን ሊነጥቅ የቋመጠ፣ ለዚህም በቀኝ በግራው፣ በፊት በኋላው ግለሰቦችን ያሰለፈ ነው።

ይህ ባለሀብት የሚነጥቃቸው መሬት ይምሰል እንጂ ከመሬቱ ጋር የተሰፋ ማንነት፣ ባሕል እና ትውፊት አብሮ አለ።

የአብነት መንደር ነዋሪዎች ይህንን የኖረ ባሕላቸውን፣ ማንነታቸውን ለመከላከል በገበሬ አቅማቸው ይውተረትራሉ።

በድራማው የመጀመሪያ ክፍል ላይ የምናያቸው እና በኋላም በታሪኩ ውስጥ በተደጋጋሚ በአርዓያ ሰብነት የሚጠቀሱት አብዬ በቃሉ ከአካባቢው ሁሉ የተለዩ ግለሰብ ነበሩ።

መለየታቸው ለመልካም ነው። ሕብረት ይወዳሉ፤ ድንበር አይፈልጉም። አገራዊ እውቀቶች ከአንዱ ሰው ወደ ሌለው እንዲተላለፉ አጥብቀው ይሻሉ። ለእርሱም ትምህርት ቤት ከፍተው የአብነትን ነዋሪዎች ያስተምሩ ነበር።

ነገር ግን ልጃቸው ከጋብቻ ውጪ አርግዛ የሠርጓ ዕለት በመውለዷ በድንጋጤ ሕይወታቸው አለፈ።

አገሬው ጉድ አለ፤ የአቶ በቃሉ ሕልም ተዳፈነ። ቤተሰቡ አንገቱን ደፋ። ልጃቸው ወጋየሁም ጨርቄን ማቄን ሳትል ሌሊቱን ማንም ወደማያውቃት አገር ተሰደደች።

የአብነት መንደር ወግ ባሕል ልማድ የተጣሰው ዋነኛ ተቆርቋሪ በሆኑት አብዬ በቃሉ ልጅ፣ ወጋየሁ ነው።

በኋላ ግን የጠፋው ወግ ባሕል ልማድ በእርሳቸው የልጅ ልጅ እንደ አዲስ ሲያንሰራራ እንመለከታለን።

በአንድ ማህጸን ያደሩት ዳዊት እና መንግሥቱ በተለያዩ ወላጆቻቸው እጅ ማደጋቸው፣ የተለያየ ባሕርይ እና ማንነት ሰጥቷቸው የማይግባቡ ዥንጉርጉሮች አድርጓቸዋል።

ያደሩበት ማህፀን፣ ተካፍለው የጠቡት ጡት ያቆየላቸው እንጥፍጣፊ ፍቅር ያለ አይመስልም።

እረኛዬ በእነዚህ ገፀ ባሕሪያት በኩል የአገርኛ እውቀቶች እንዲያብቡ፣ ባሕል ወግ ልማድ እንዳይጣስ፣ ፍቅር ይቅርታ የኑሮ አምድ እንዲሆኑ ደጋግሞ ይወተውታል።

በበርካቶች ዘንድ ትኩረትን ያገኘው ለዚህ ይሆን? ድራማውን የተከታተሉ ሁለት ግለሰቦች አነጋግረናል።

የእረኛዬ ተከታታይ ድራማ ተዋንያን

የፎቶው ባለመብት, Arts TV

ገሸሽ ያደረግነውን ማንነት ፍለጋ

በእረኛዬ ድራማ ላይ የምናያቸው የማምረቻ መሳሪያዎቹ፣ አልባሳቱና ጌጣጌጦቹ፣ ወዘተ የራሳቸው የሆነ ቱባ ሥነ ውበታዊ ገጽታ አላቸው።

በአሰራራቸው የአገርኛ ጥበብ አሻራ ታትሞባቸው ይገኛል።

በድራማው ላይ የሚታዩት የሰላምታ ልውውጦች፣ የግብይት ልማዶች፣ የጋብቻ ሥርዓቶች፣ የአምልኮ ትውፊቶች፣ የለቅሶ ልማድ ሁሉ የየራሳቸው ውበትና መስህብ እንዲኖራቸው ተመልካችን እንዲያማልሉ ሆነው ተቀርፀዋል።

በድራማው ላይ በእረኞች እና በኮማሪቷ ማስረሻ፣ የሚገጠሙ ግጥሞች የማኅበረሰቡን ማንነትና ስሜት ከማንጸባረቅ ትይዩ የቆሙ፣ ሥነ ጽሑፋዊ ቴክኒክ ተላብሰው የቀርቡ ናቸው።

ይህም የማዝናናት ለዛቸውን አጉልቶ፣ አይረሴና ተጨባጭ አድርጓቸዋል።

ድራማው አካብቶ ያቀርብልን የማኅበረሰቡ ጠቅላላ የተሞክሮ ዕውነታ ባሕላዊ ማንነትን የሚያጎሉ ቅርሶች የተዝናኖት ፋይዳ ጨምረውለታል።

የደራሲዎቹ የተጠባቢነት አቅም ልኩ የሚመዘነው ደግሞ እነዚህን አጣጥሞ በማቅረብ ብቃቱ ላይ የተመሰረተ መሆኑን የባላገሩ ቴሌቪዥን የፕሮግራም ዳይሬክተር የሆነው ሲራክ ተመስገን ይናገራል።

የትያትር እና የፊልም መምህር የሆነው አንተነህ ሠይፉ በበኩሉ እረኛዬን የወደድንበትን ምክንያት ሲያነሳ አስቀድሞ የሚጠቅሰው መቼቱን ነው።

በኢትዮጵያ የፊልም እና የተከታታይ ድራማ ታሪክ መቼታቸውን በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ያደረጉ ሥራዎች በቀላሉ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት እና ተወዳጅነት ማግኘታቸውን በማንሳት እረኛዬም ይህ እንደረዳው ይገልጻል።

የዚህ ተከታታይ ድራማ ደራሲና አዘጋጅ የሆነችው ቅድስት ይልማ ቀዳሚ ሥራ የሆነው ‘ረቡኒ’ን በምሳሌነት ያነሳው አንተነህ፣ በተመሳሳይ መልኩ መቼቱን ገጠር በማድረጉ ተወዳጅነትን አትርፎ እንደነበር ያስታውሳል።

አንተነህም ሆነ ሲራክ፣ እረኛዬ ተከታታይ ድራማ፣ ያነሳው ታሪክ ወደ ጥንታዊ ማንነት፣ ገሸሽ ወዳደረግናቸው ባሕላዊ እሴቶቻችን መመልከቱ በተመልካች ዘንድ ተወዳጅነት ለማግኘቱ አስተዋጽኦ ማድረጉ ላይ ይስማማሉ።

አክለውም ታሪኩ የተዋቀረበት እና ገጸ ባህሪያቱ የመጡበት ዓለም፣ ከማኅበራዊ ከሌሎች እሴቶቻችን ጋር መሳ ለመሳ መሆኑ ተቀባይነት ለማግኘት አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ይናገራሉ።

ዳይሬክተሯም ገጸ ባህሪያቱ የተቀዱበት ማኅበረሰብን ማንነት ለማጉላት የተጠቀመችባቸው ነባር እሴቶችም አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አንተነህ አክሎ ይገልጻል።

ኢትዮጵያ ያለችበት ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ሁኔታ

እረኛዬ ድራማ በአገሪቱ ካለው እውናዊ ሕይወት በትይዩ ይሳል እንጂ፣ የማኅበረሰቡን ስምና አድራሻ በቅጂነት ከነምግባሩ አያነሳም።

ገጸ ባህሪያቱ በምናብ በተፈጠረ መንደር፣ አብነት፣ ልቦለዳዊ ኑሯቸውን መስርተዋል።

የማኅበረሰቡን ኑሮ አይኑሩ እንጂ፣ ለኑሮው መስታወት ሆነው የራሱ የዕለት ተለት ገመና መልሶ እንዲመለከት አድርገውናል።

በድራማው ውስጥ የማኅበረሰቡን እንከን፣ ሠላም የማጣት፣ የመናቆር፣ ይቅር ማለት አለመቻል ፍጥጥ ብሎ እንዲታይ አድርጓል።

ለዚህም እንቆቅልሽ ብሎ በመጠየቅ ከራስ መልስ እንደመጠየቅ አይነት ነው።

ደራሲዎቹ በገጸ ባህርያቱ ሕይወት በኩል እንቆቅልሽ ብለው ይጠይቃሉ። ተመልካቹም ፍንጮቹን እየተከተለ የሕይወትን እንቆቅልሽ የመፍታት ድርሻን ይወስዳል።

አንተነህ ይህንን ሃሳብ ሲያጠናክር “ወቅቱን የሚገልፁ፣ ሰዉ ልብ ውስጥ ያለውን፣ በአደባባይ መተንፈስ መናገር የማይችለውን ነገር በድራማ መልክ ስለማንነታችን፣ ስለ እርስ በእርስ ግንኙነታችን ስለአናኗራችን አሁን ስላለው ፖለቲካዊ ሁኔታ፣ በጥሩም ይሁን በመጥፎ ያነሳሳል” ይላል።

ላለው ወቅታዊ ፖለቲካዊ ሁኔታ ጥያቄ ነው ያለውን ድራማው ያነሳል፤ እንደ ታምራት ገለፃ መልስ ነው መፍትሔ ይሆናል ያለውንም እዚያው ይጠቁማል፤ ይመልሳል።

ሲራክም ሆነ አንተነህ በድራማው በኩል የራሳችን ገበና፣ ከአደባባይ ርቀን በማጀታችን የምናወራው ነገር ሲቀርብልን፣ መተንፈሻ ፉካ ሆኖን በማገልገል ተወዳጅነትን አትርፏል ይላሉ።

ሲራክ አክሎም ዳይሬክተሯ ቅድስት አገሪቷ ያሉባትን ችግሮች፣ አገር በቀል በሆነ እውቀት ውስጥ መፍትሔ መፈለግን እንደ ስልት ይዛዋለች ይላል።

የእረኛዬ ድራማ ደራሲያን ከግራ ወደ ቀኝ ቅድስት ይልማ፣ ቤዛ ኃይሉ፣አዜብ ወርቁ

የፎቶው ባለመብት, Arts TV

ጀግኒት ፀሐፊያን እና አዘጋጅ

የኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ የወንዶች ዓለም ነው በሚለው ሀሳብ አንተነህና ሲራክ ይስማማሉ።

አብዛኞቹ ታሪክ ነጋሪዎችና ፀሐፊዎች ወንዶች በመሆናቸው በወንድ ዐይን ነው ዓለሙን የሚያሳዩን ይላል አንተነህ።

የምንኖረውን የአባታዊ ሥርዓት፣ በምንታደመው የጥበብ መድረክ ላይም የምናየው ሕይወት የወንዶች ምናብ ውጤት ነው በማለት ያክላል ሲራክ።

“ዓለሙን፣ ሕይወትን፣ አገርን የሚተረጉሙት በወንድ መነጽር ነው” ይላል አንተነህ።

የእረኛዬ ደራሲዎች ግን ከዚህ ተቃራኒ ዕድል ነበራቸው።

እንዲህ ሴቶች በድርሰትም በዝግጅትም ሰብሰብ ብለው መምጣታቸው እንደ እረኛዬ አይነት በሥርዓተ ጾታ ላይ ጥንቁቅ የሆነ ድራማ እንድናገኝ ረድቶናል ይላል ሲራክ።

ለዚህም ነው የእረኛዬ ሴት ገጸባህሪያት የድራማው ደምና አጥንት ሆነው ነው የተሳሉት።

የአብነት መንደር ሕይወት በጫንቃቸው ነው። የአብዬ በቃሉ አደራ በደም ሥራቸው ይፈሳል።

የትምህርት ቤት ደጃፍ ባይረግጡም፣ የፊደል ዘር ባይለዩም ሕይወትን፣ በዙሪያቸው የተንሰራፋውን ዓለም በገባቸው ልክ የሚተረጉሙ እና እርሱንም አጽንቶ ለማቆም የሚታገሉ ናቸው።

የእረኛዬ ሴት ገጸ ባህሪያት ለከተማ ሕይወት ባዳ ሆነው፣ የቀለም ዘር ሳይለዩ ለመብታቸው የሚቆሙ ናቸው የሚለው ደግሞ አንተነህ ነው።

በዚህ ሃሳብ ሲራክም ይስማማል። “በእረኛዬ ድራማ ላይ ልፍስፍስ ሴት አትታይም፤ ከወንዶች እኩል የምትገዳደር ሴት እናገኛለን” ሲል ያክላል።

አንተነህ ሲያክልበት ደግሞ “ለእህቷ ለጓደኛዋ መብት የምትቆም ሴት. . .ልጆቿን ሕልውናዋን ለመመለስ የምትታገል ሴት. . .ቤቷን ብቻ ሳይሆን አካባቢዋን አጽንቶ ለማቆም የምትታገል እናት” ማየታችን በሴት ደራሲያን የመጻፉ ትሩፋት መሆኑን ያስረዳል።

የድራማው ደራሲያን ሴት መሆናቸው ወንዶች የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ሲጽፉ የሚያጎዱሉት ነገር ቁጭት እና እልህ አለባቸው የሚለው አንተነህ፣ ጠንካራ ሴት ገጸ ባህሪያትን በመሳል ረገድ እንደተዋጣላቸው ይመሰክራል።

ደራሲያኑ እንዲሁም ዳይሬክተሯ ሴቶች መሆናቸው “ለሚገባቸው ሚና የሚታመኑ ጠንካራ ገጸ ባህሪያትን” ጠንካራ ሴቶች እንድናይ አድርጎናል ሲል ይገልጻል።

የእረኛዬ ሴት ገጸ ባህሪያት ከእነርሱ ሕይወት ይልቅ የሚኖሩበት ማኅበረሰብ ሕልውና ያሳስባቸዋል።

በዋና ገጸ ባህሪይነት የተሳሉት ሴቶች ሁሉ ከራሳቸው በላይ ሰንደቅ ሆኖ የሚውለበለብ ዓላማ አላቸው።

የእናና ገጸ ባህሪ ደግሞ ለሞቷ ሰበብ የሆነውን የጥቅም ፈላጊዎች ጠብ፣ ለመኖሪያ ቀዬዋ ነዋሪዎች ቀጣይ የጠብ ጥንስስ መነሻ እንዳይሆን በመመሸግ፣ መስዋዕት እስከመሆን ትደርሳለች።

ጎምቱ እና ተወዳጅ ተዋንያን መሳተፋቸው

በእረኛዬ ድራማ ላይ የተሳተፉት ተዋንያንም ቢሆኑ ስምና ዝና ያላቸው፣ ክህሎትም ቢሆን ጠንቅቀው የተካኑ መሆናቸው ለተወዳጅነቱ አስተዋጽኦ ማድረጉን አንተነህ እና ሲራክ የሚስማሙበት ጉዳይ ነው።

“ከእረኛዬ ድራማ የተመቸኝ አንድ ነገር ቢኖር ገጸ ባህሪ አሳሳሉ እና ተዋናይ መረጣው ነው” ይላል ሲራክ።

እረኛዬ ድረማ “የደርቢ ስብስብ ይመስላል” የሚለው ደግሞ አንተነህ ነው። ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ በድራማው ላይ ወሳኝ ስፍራ የያዙት ተዋንያን ስምም ዝናም ያላቸው መሆናቸውን ነው።

በእርግጥ በድራማው ላይ አዳዲስ ፊቶች የታዩ ቢሆንም እንደ አበበ ባልቻ፣ ሙሉዓለም ታደሰ፣ ድርብ ወርቅ ሠይፉ፣ ሳያት ደምሴ፣ ኩራባቸው ደነቀ፣ አማኑኤል ሐብታሙ፣ ቃልኪዳን ጥበቡ እንዲሁም ሠለሞን ቦጋለ ያሉ ተዋንያንን ማሳተፉ አድናቂዎቻቸውን ወደ ድራማው በመጥራት ረገድ አስተዋጽኦ ማድረጉን ይጠቅሳል።

ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ ተዋንያኑ የተወከሉበትን ገጸ ባህሪ በሚገባ መጫወታቸው፣ ተደራሲያንን ወደ ታሪኩ ጎትቶ በማስገባት ረገድ የላቀ ሚና እንደነበረው ያነሳል።

ከተለመደው አቀራረብ ወጣ ማለቱ

የእረኛዬ ገጸ ባህሪያት ከሚኖሩበት አብነት መንደር ርቀው አይሄዱም። ወደ ተለያዩ ከተሞች ልጇን ፍለጋ የምትባዝነው ወጋየሁም ብትሆን ትንንሽ የገጠር ከተሞችን ታካልላለች እንጂ ሕንጻ ወደተንጠለለበት ከተማ ጎራ አትልም።

ይህ ግን ተደራሲው ላይ ያጎደለው ነገር የለም። ድራማው የሚያነሳው አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን በየቀኑ የሚውሉበትን፣ የሚወጡ የሚወርዱበትን በመሆኑ በታሪኩ ላይ ጉድለት አልፈጠረም።

እረኛዬ ታሪኩን የመሰረተው ከከተማ ውጪ ያለ ሕይወት ላይ መሆኑ፣ ተመልካቹ ከለመደው ውጪ ነገር ይዞ መቅረቡ ለተወዳጅነቱ አስተዋጽኦ ማድረጉን አንተነህ ያነሳል።

ይህ የታሪክ አቀራረቡ በተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ እንዲሁም ፊልም ከተለመደው ውጪ መሆኑ የራሱ ድርሻ ነበረው።

ሲራክ በበኩሉ በበርካታ የፊልም ባለሙያዎች ዘንድ ኢትዮጵያዊ ፊልም መስራት የሚለው አጀንዳ ሲነሳ እሰማለሁ በማለት ኢትዮጵያዊ ድራማ ማለት ገጠር ውስጥ የሚከወን ብቻ መሆኑ ላይ ጥያቄ ያነሳል።

የእረኛዬ ድራማ በአብነት የገጠር መንደር መኖራቸው፣ ከተማ ጠል መሆናቸው ባይጎረብጠውም ኢትዮጵያዊ ለማድረግ ብቻ ግን ገጠሩን መምረጥ አዋጭ ሃሳብ አለመሆኑን አንስቶ ይሞግታል።

በማጠቃለያውም ላይ ከተሜ ሆኖ ኢትዮጵያዊ ወግ ባሕል የሚታይበት ኑሮ እኮ አለ ሲል ያክላል።