የአሜሪካ ምርጫ ትንበያ፡ ማን እየመራ ነው - ትራምፕ ወይስ ሃሪስ?

ጥቅምት 25/2017 ዓ.ም አሜሪካውያን ቀጣዩን ፕሬዝደንት ለመምረጥ ወደ ድምጽ መስጫ ጣቢያዎች ያመራሉ።
ይህ ምርጫ ከአራት ዓመት በፊት ከተካሄደው እና ጆ ባይደን ካሸነፉበት ምርጫ ጋር ይመሳሰላል ተብሎ ተጠብቆ ነበር።
ሆኖም ባለፈው ሐምሌ ፕሬዝዳንት ባይደን ከፉክክሩ እራሳቸውን እንዳገለሉና በምትኩ ምክትላቸው ካማላ ሃሪስ እንዲወዳደሩ ይሁንታ ከሰጡ በኋላ የዘንድሮው ምርጫ የተለየ መልክ እንደሚኖረው ተገምቷል።
ትልቁ ጥያቄ ግን ማን ያሸንፋል የሚለው ነው? - አወዘጋቢው ትራምፕን ዳግም ፕሬዝዳንት ያደርጋል ወይስ አሜሪካ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሴት ፕሬዝዳንት ይኖራታል?
የድምጽ መስጫ ቀኑ እጅግ እየተቃረበ መሆኑ እና ከትናንት በስቲያ ሁለቱ ፕሬዝዳንታዊ እጩዎች ያደረጉት ሙግት ለዋይት ሃውስ ማን ይበልጥ ይቀርባል የሚል ግምት በስፋት እንዲሰጥ አድርጓል። በቅድመ ምርጫ ትንበያዎች (polls) ማን እየመራ ነው የሚለውን እንመለከት።
ቅድመ ምርጫ ትንበያዎቹ ማን ያሸንፋል አሉ?
ከትናንት በስቲያ ትራምፕና ሃሪስ ለመጀመሪያ ጊዜ ፊት ለፊት ተገናኝተው ክርክር አድርገዋል። በዚህ ሙግት የወቅቱ የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝደንት ካማላ ሃሪስ ከዶናልድ ትራምፕ ተሽለው መገኘታቸውን ብዙዎች ይናገራሉ።
ከብዙዎች አስተያየት ባሻገር የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች ምን አሉ? - ብሔራዊውን እና ትልቁን ምስል የሚያስመለክተውን ትንበያን ለማግኘት ጥቂት ቀናት መቆየት የግድ ይላል።ሆኖም ሌሎች ትንበያዎችን መመለከት እንችላለን።
‘ዩጎፍ ሰርቬይ’ በተሰኘ እና ባለፈው ማክሰኞ የተደረገውን ክርክር የተመለከቱ ከ2 ሺህ በላይ ድምጽ ሰጪዎች ባሉት የቅድመ ምርጫ ትንበያ ድረ ገጽ ውጤት መሰረት ሃሪስ 54 በመቶ ደምጽ ሲያገኙ ትራምፕ ደግሞ 31 በመቶ ማግኘታቸውን ይጠቁማል።
ያለፈውን የእጩ ፕሬዝዳንቶች ሙግት የተመለከቱ 600 ደምጽ ሰጪዎች ባሉት የሲኤንን/ ‘ኤስ ኤስ አር ኤስ’ የምርጫ ትንበያ መሠረት ሃሪስ 63 በመቶ ደምጽ አግኝተዋል። ተቀናቃኛቸው ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ በ37 በመቶ ማግኘታቸውን ያመለክታል።
በዚህ ትንበያ ላይ የተሳተፉ ደምጽ ሰጪዎች 4 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ባለፈው ማክሰኞ የተደረገውን ክርክር ከተመለከቱ በኋላ ማንን መምረጥ እንዳለባቸው የሀሳብ ለውጥ ሊያደርጉ እንደሚችሉ ገልጸዋል።ስለዚህ ክርክሩ በመራጮች ፍላጎት ላይ ምን ያህል ተጽዕኖ እንዳመጣ ጥቂት ቀናትን መጠበቅ ይጠይቃል።
በብሔራዊ ትንበያው ላይ ማን እየመራ ነው?
ጆ ባይደን ‘ከምርጫው ወጥቻለሁ’ እስኪሉ ድረስ የቀድሞ ፕሬዝደንት ትራምፕ ከተፎካካሪያቸው የተሻለ የማሸነፍ ዕድል እንደነበራቸው ትንበያዎች በተከታታይ አሳይተዋል።
የዲሞክራቶች ዕጩ ተቀይረው ሃሪስ በመጡበት ሰሞንም ከቀድሞ ዕጩ ጆ ባይደን የተሻለ ውጤት በትንበያዎች አለማሳየታቸው ተገምቷል።
ሆኖም ሃሪስ በምርጫ ቅስቀሳቸው ጠንካራ ሥራዎችን ከሰሩ በኋላ ከተቀናቃኛቸው ትራምፕ ብሔራዊ ቅድመ ትንበያ ላይ በጥቂት ልዩነት የተሻለ ሆነው ታይተዋል።
ከፕሬዝዳንታዊ ሙግቱ በፊት የነበረው የጨረሻው ብሔራዊ የትንበያ ውጤት በተፎካካሪዎቹ መካከል ሰፊ ልዩነትን አያሳይም።
ጠቅላላ ውጤቱ ሃሪስ ለፕሬዝዳንትነት ለመወዳደር ከመጡ በኋላ እያገኙት ያለው ድምጽ በዝግታ እየጨመረ መሄዱን ያመለክታል።
ዲሞክራቶች በቺካጎ ካደረጉት 4 ቀናት የቆየ ጉባዔ በኋላ ሃሪስን ዕጩ አድርገው ሲያቀርቡ 47 በመቶ ደምጽ አግኝተዋል። ከዚያ ጊዜ በኋላ በቅድመ ትንበያው እያገኙ የሄዱት ድምጽ ብዙም ፈቀቅ ያለ አይደለም።
የትራምፕ አማካይ የትንበያ ውጤትም ብዙም ለውጥ ሳያሳይ 44 በመቶ አካባቢ ላይ ቆይቷል። ሮበርት ኬኔዲ የተባሉት ዕውቅ ፖለቲከኛ በግል ለፕሬዝደንትነት የሚያደርጉትን ፉክክር አቁመው ድጋፋቸውን በይፋ ለትራምፕ ከገለጹ በኋላም በትራምፕ ቅደመ ትንበያ ላይ የታየ ሰፊ ልዩነት የለም።
ብሔራዊ የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ የትኛው ዕጩ ተወዳጅ ነው የሚለውን ሊያመለክቱ ቢችሉም የምርጫው ውጤት ይህ ነው የሚያስብል ለእውነታ የቀረበ ግምትን አያስቀምጡም።
ምክንያቱም አሜሪካ ወሳኝ ድምጽ ያላቸው ግዛቶች ያሉት የምርጫ ስርዓትን ወይም electoral college system ስለምትከተል ነው። በዚህ ስርዓት መሠረት በሌሎቹ ግዛቶች ከፍተኛ ውጤት ቢመዘገብም ወሳኝ ድምጽ ካላቸው ግዛቶች የሚወጣ ጥቂት ድምጽ የበለጠ ዋጋ ሊኖረው ይችላል።
በአሜሪካ ካሉት 50 ግዛቶች አብዛኞቹ ብዙውን ጊዜ ለተመሳሳይ ፓርቲ ደምጽ የመስጠት ልምድ አላቸው። በጣም ጥቂት የሚባሉት ግዛቶች ላይ ብቻ ሁለቱ ፕሬዝዳንታዊ ዕጩዎች ተፎካክረው የማሸነፍ ዕድል አላቸው።
ተከታዮቹ ግዛቶች ቀጣዩ የአሜሪካ ፕሬዝደንት ማን ሊሆን እንደሚችል የሚወስኑ ናቸው። እነዚህ ጥቂት ግዛቶች ለአንድ ፓርቲ፣ ለዲሞክራቶችም ይሁን ለሪፐብሊካኖች ብቻ ድምጽ የመስጠት ልምድ ስለሌላቸው ወሳኝ ይሆናሉ።
በአሜሪካ ወሳኝ ግዛቶች ማን እየመራ ነው?
በአሜሪካ ምርጫ ወሳኝ ደምጽ ያላቸው 7 ግዛቶች አሉ።አሁን ላይ በእነዚህ ግዛቶች የቅድመ ምርጫ ትንበያው እጅግ የጠበበ ልዩነት ይታይበታል።በዚህም ምክንያት ማን እየመራ ነው የሚለውን ለመናገር አስቸጋሪ ነው።
በእነዚህ ግዛቶች ከብሔራዊ ቅድመ ምርጫ ትንበያው ያነሰ ትንበያ ነው ያለው። በመሆኑም ዝቅ ያለ መረጃ በመኖሩ ውጤቱን ተገማች ለማድረግ አስቸጋሪ ያደርገዋል።
ፔንሲልቬንያ ግዛት በአሜሪካ ፕሬዝዳንት ለመሆን የሚያስፈልገውን 270 ድምጽ ለማግኘት ከሁሉም ወሳኝ የሚባለው ነው። በዚህ ግዛት አሸናፊ መሆን የአሜሪካን ምርጫ ለማሸነፍ መንገዱን ቀላል ያደርገዋል።
ፔንስልቬንያ፣ ሚሺጋን እና ዊስኮንሰን የዲሞክራቶችን ዕጩ የመምረጥ ልምድ ነበራቸው። ሆኖም በአውሮፓውያኑ 2016 ድምጻቸውን ለትራምፕ ሰጥተው ይህንን ልምድ ቀይረዋል።
ሆኖም በ2020 ዲሞክራቶች በዕጯቸው ጆ ባይደን አማካኝነት የእነዚህን ግዛቶች ድምጽ ጠቅልለው ወስደዋል።እናም በዚህ ምርጫ ካማላ ሃሪስ ተመሳሳይ ዕድል ከቀናቸው ፕሬዝዳንታዊው ወንበር ላይ የመቀመጣቸው ነገር አይቀሬ ይሆናል።
የአሜሪካው የዜና ጣቢያ ኤቢሲ ኒውስ ያዘጋጀው 538 የተባለ የቅድመ ምርጫ ትንበያ መሰብሰቢያ 6 ወሳኝ ድምጽ ወይም ‘ኢሌክቶሪያል ቮት’ ባለው ኔቫዳ፣ 16 ‘ኢሌክቶሪያል ቮት’ በያዘው ኖርዝ ካራሎይና፣ 19 ‘ኢሌክቶሪያል ቮት’ ባሉት ፔንሲልቬንያ፣ እንዲሁም እያንዳንዳቸው 15 እና 10 ‘ኢሌክቶሪያል ቮት’ ባላቸው ሚሺጋን እና ዊስኮንሲን ግዛቶች እጅግ በጠበበ ልዩነት ሃሪስ እየመሩ እንደሆነ ያመለክታል።
በተመሳሳይ በተቀሩት እና እያንዳንዳቸው 16 እና 11 ‘ኢሌክቶሪያል ቮት’ ባላቸው ጆርጅያ እና አሪዞና ግዛቶች ትራምፕ ከአንድ በመቶ በታች በሆነ ልዩነት እየመሩ እንደሆነ ይጠቁማል።
የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች ይታመናሉ?
አሁን ያሉት የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች የወቅቱ የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝደንት ካማላ ሃሪስ እና የቀድሞ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ በብሔራዊም ይሁን በሰባቱ ወሳኝ ግዛቶች የምርጫ ትንበያ እጅግ የጠበበ ልዩነት እንዳላቸው ያሳያሉ።
በዚህ ምክንያት ከዲሞክራቶችም ይሁን ከሪፐብሊካኖች ዕጩ አሸናፊው ይህ ነው ለማለት አስቸጋሪ ይሆናል።
ባለፉት ሁለት ምርጫዎች ማለትም በአውሮፓውያኑ 2016 እና 2020 የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች የተሳሳተ ትንበያን አስቀምጠዋል። በእነዚህ ትንበያዎች ትራምፕ ያላቸው ድጋፍ ከእውነታው የራቀ ነበር።
የቅድመ ምርጫ ውጤት የሚተነብዩ ድርጅቶች ይህንን ችግር ለማስተካከል እየጣሩ እንደሆነ ይናገራሉ። ይህም ደምጽ የሚሰጡ ሰዎችን ስብጥር ማስተካከል ይጨምራል።
ድርጅቶቹ ማሻሻያ ቢያደርጉ የምርጫ ትንበያዎች ትክክለኛውን ውጤት ማንጸባረቅ ሊሳናቸው ይችላል። ምክንያቱም በመጪው ጥቅምት 2017 የመጨረሻ ሳምንት የሚካሄደውን ምርጫ ማን እንደሚያሸንፍ የሚወስነው ለመምረጥ የሚወጣው ሰው ቁጥርም ነው።












