የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ግምት፡ አርሰናል ከሊቨርፑል ማን ያሸንፋል?

የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ማክሰኞ፣ ረቡዕ እና ሐሙስ ይካሄዳሉ።
የሊግ ሰንጠረዡን እየመራ የሚገኘው አርሰናል የአምናው ቻምፒዮን ሊቨርፑልን በሜዳው ኤሜሬትስ ያስተናግዳል።
አንፊልድ ላይ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ ቀያዮቹ በስቦዝላይ አስደናቂ ቅጣት ምት 1 ለምንም ማሸነፋቸው ይታወሳል። በወቅቱ ሊቨርፑል የሊጉ መሪ ነበር። አሁን አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ለመሆኑ በኤሜሬትስ በሚደረገው ፍልሚያ ሊቨርፑል የሊጉን መሪዎች ይፈታተን ይሆን?
የቢቢሲ ስፖርት ተንታኙ ክሪስ ሱተን የሳምንቱ አጋማሽ ጨዋታዎችን ግምት አስቀምጧል።
ዌስት ሀም ከኖቲንግሀም
ኖቲንግሀም ፎረስት አራት ጨዋታ በተከታታይ ተሸንፈዋል። ነገር ግን ዌስትሀም ከዚህም የባሰ አቋም ላይ ነው የሚገኘው።
ባለፈው ቅዳሜ በዎልቭስ የተሸነፉበት መንገድ አሠልጣኝ ኑኖ ላይ ጫና እንዲበረታ አድርጓል።
ኑኖ የኖቲንግሀም አሠልጣኛ እያሉ በዌስት ሀም 3-0 መሸነፋቸውን ተከትሎ ከሥራቸው መሰናበታቸው ይታወሳል። አሁን በተመሳሳይ ውጤት ቢያሸንፉ ደስ ይላቸዋል። የሚሆን ግን አይመስለኝም።
የሾን ዳይች ቡድን ከዚህ ጨዋታ ውጤት ያገኛል ብዬ ገምታለሁ።
ግምት፡ 0 - 1

ቦርንመዝ ከቶተንሀም
ቦርንመዝ ካለፉት 11 ጨዋታዎች አንዱንም ማሸነፍ አልቻሉም። በአንዳንድ ጨዋታዎች ዕድል ከእነሱ ጋር አልነበረችም።
ጎል የማግባት ችግር የሌለባቸው ቦርንመዞች ከቼልሲ 2 አቻ ሲለያዩ እንዲሁም በአርሰናል 3-2 ሲሸነፉ ይህን አሳይተዋል።
አንትዋን ሴሜንዮ በያዝነው ወር ማንቸስተር ሲቲን እንደሚቀላቀል ይታወቃል። ነገር ግን በዚህ ጨዋታ ይሰለፋል?
እሱ ተሰለፈም አልተሰለፈ ቶተንሀም ይህን ጨዋታ ያሸንፋል ብሎ መገመት ከባድ ነው።
13 ደረጃ ላይ የሚገኘው ቶተንሀም ወጥ አቋም ማሳየት የተሳነው ቡድን ሆኗል።
ግምት፡ 1 - 0
ብሬንትፈርድ ከሰንደርላንድ
የውድድር ዘመኑ ከመጀመሩ በፊት ይህ ጨዋታ ጥር ላይ ሰባተኛ እና ስምንተኛ ደረጃ ላይ ቡድኖች መካከል ይካሄዳል ብሎ ቢገምት የሚስቅበት ብዙ ነበር።
ቶማስ ፍራንክ ወደ ቶተንሀም ሲመጡ ብሬንትፈርድ ሊቸገር እንደሚችል ተጠብቆ ነበር። ኪዝ አንድሪውስ ግን ይህን ግምት ውድቅ አድርገዋል።
አጥቂው ኢጎር ቲያጎ ከኤቨርተን ጋር በነበረው ፍልሚያ ሦስት ግቦች አስቆጥሮ ሀት-ትሪክ ሠርቷል።
ወደ ሰንደርላንድ ስንመጣ በያዝነው የውድድር ዘመን ጥቂት ግቦች የተቆጠረባቸው አርሰናል፣ ሲቲ እና ጥቋቁር ድመቶቹ ናቸው።
ይህ ጨዋታ በሁለት ጥሩ አቋም ላይ ባሉ ቡድኖች መካከል የሚካሄድ እንደመሆኑ አሸናፊ ላይኖር ይችላል።
ግምት፡ 1 - 1
ክሪስታል ፓላስ ከአስተን ቪላ
ፓላስ ካለፉት አምስት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ ብቻ ነው ያገኙት። ምናልባት በጥር ወር የዝውውር መስኮት አዳዲስ ተጫዋቾች በማምጣት ይነቃቁ ይሆናል።
ፓላስ ባለፈው የውድድር ዘመን ቪላን ከሁለት የዋንጫ ውድድሮች ውጭ ከማድረጉ ባለፈ በሜዳው 4-1 በቪላ ሜዳ ደግሞ 3-0 ማሸነፉ ይታወሳል።
በዚህ ጨዋታ ግን ይህ ይሆናል የሚል ግምት የለኝም። የኡናይ ኤምሪ ቡድን የልብ መተማመኑ ከፍ እያለ መጥቷል።
ግምት፡ 1 - 2
ኤቨርተን ከዎልቭስ
ዎልቭስ በያዝነው የውድድር ዓመት የመጀመሪያውን ድል ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ተጎናጽፏል።
አሠልጣኝ ሮብ ኤድዋርድስ ተዓምራዊ በሆነ መንገድ ዎልቭስ ከወራጅ ቀጣና ያስወጡት ይሆን? የዎልቭስ ደጋፊዎች እንደሚያዝኑብኝ ባውቅም መልሱ ግን አይሆንም የሚል ነው።
የኤቨርተኑ አሠልጣኝ ዴቪድ ሞየስ አዳዲስ ተጨዋቾችን ማምጣት እንዳለበት ባምንም በሜዳው ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች ይሸነፋል ብዬ አልጠብቅም።
ግምት፡ 2-1
ፉልሀም ከቼልሲ
ሊያም ርዝንዮር አዲሱ የቼልሲ አሠልጣኝ ይሆናሉ ተብሎ እየተወራ ይገኛል። ለዚህ ጨዋታ ሊደርሱም ይችላሉ።
አሠልጣኙ ማንም ቢሆን ይህ ለቼልሲ ከባድ የሚሆን ጨዋታ ነው።
ምንም እንኳ ለፉልሀም ያለኝ ግምት ከፍ ያለ ቢሆንም ቼልሲ ከዚህ ጨዋታ ውጤት እንደሚያገኝ አስባለሁ።
የምዕራብ ለንደን ደርቢ አሸናፊ ቼልሲ ይሆናል።
ግምት፡ 1 - 2

ማንቸስተር ሲቲ ከብራይተን
ከሰንደርላን እና ቼልሲ አቻ ለወጣው ማንቸስተር ሲቲ ይህ ሌላ አስቸጋሪ ጨዋታ ነው።
በብራይተን ሜዳ በነበረው ፍልሚያ ሲቲ ተሸንፎ ነው የተመለሰው። ብራይተን ለመገመት እጅግ ከባድ ከሆኑ ቡድኖች መካከል ነው።
ዲያዝ እና ግቫርዲዮል መጎዳታቸው ለሲቲ አሳዛኝ ዜና ነው። ቢሆን የፔፕ ቡድን ተጨማሪ ነጥብ ማጣት የሚፈልግ አይመስለኝም።
በዚህ ጨዋታ የሲቲ አጥቂ ኧርሊንግ ሀላንድ ሀት-ትሪክ ያስቆጥራል ብዬ እገምታለሁ።
ግምት፡ 2 - 1
በርንሊ ከማንቸስተር ዩናይትድ
ሩበን አሞሪም ከዩናይትድ አመራሮች ጋር በገቡት እሰጥ አገባ ምክንያት ከሥራቸው ተባረዋል።
ካለፈው የውድድር ዘመን ጋር ሲነፃፀር የተሻሉ የሆኑት ባለፈው ዓመት በጣም ደካማ አቋም ስለነበራቸው ነው።
በርንሊ ወደ ኦልድ ትራፈርድ ተጉዞ እስከ 97ኛው ደቂቃ ድረስ ታግሎ 3-2 ተሸንፎ ተመልሷል።
የትኛውም አሠልጣኝ ቢመጣ ይህ የዩናይትድ ቡድን ከአማካይ የዘለለ አቋም ያሳያል የሚል እምነት የለኝም።
ግምት፡ 1 - 1
ኒውካስል ከሊድስ
ኒውካስል በሜዳው ፓላስን በመርታት ሦስት ነጥብ ከማግኘቱ በተጨማሪ ከበርካታ ጨዋታዎች በኋላ ጎል ሳይቆጠርበት ወጥቷል።
ሊድስ ባለፉት ሰባት ጨዋታች አልተሸነፉም። ባለፈው እሑድ ከዩናይትድ በነበረው ግጥሚያ የሚገባቸውን አንድ ነጥብ አግኝተዋል።
ኒውካስል በሜዳቸው ሲጫወቱ ድል እንደሚቀናቸው ሁሌም እገምታለሁ።
ግምት፡ 2 - 0

አርሰናል ከሊቨርፑል
ሊቨርፑል ባለፉት ዘጠኝ ጨዋታዎች ሸንፈት አልገጠማቸውም። ውጤታቸው የሚያስከፋ አይደለም።
ጨዋታቸውን ስትመለከቱ አምና ከነበረው ጋር ፍፁም የማይመሳሰል ነው። አርሰናል አሁን ካለበት አቋም ጋር ሲነፃፀር ሊቨርፑል ደካማ የሚባል ቡድን ነው።
የመጀመሪያው ጨዋታ በጠባብ ውጤት ነው የተጠናቀቀው። ይህ ጨዋታ ግን ተመሳሳይ የሚሆን አይመስለኝም። የአርቴታ ልጆች ሊቨርፑል ላይ በርካታ ግቦችን ለማስቆጠር የሚሞክሩ ይመስለኛል።
አርሰናል በስድስት ነጥብ ልዩነት ሊጉን እየመራ ይገኛል። ሲቲ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ መጣሉ ለመድፈኞቹ ትልቅ ዜና ነው።
ግምት፡ 2 - 0















