በልጆቻችን ምሳ ዕቃ ሊቋጠር የሚገባው ምግብ ምንድን ነው?

ልጅ በዕድሉ አያድግም። ይልቁንም በቂ እንክብካቤ፣ እንቅልፍ፣ አካላዊ እንቅስቃሴ እና መልካም ከባቢን ጨምሮ በርካታ ጉዳዮች ከግምት ውስጥ ገብተው የልጆችን ዕድገት ይወስናሉ።

የምግብ ድርሻ ግን እጅግ ወሳኝ ከሚባሉት ውስጥ ነው። የምናወራው ስለጤናማና የተሟላ ዕድገት ነው። በቁመት መመዘዝ እና አካላዊ ለውጥ የተሟላ ዕድገት ነው ማለት አስቸጋሪ ነው።

ታዲያ የተሟላ ዕድገት ምንድን ነው? ከምግብስ ጋር ምን ያገናኘዋል?

በጳውሎስ ሚሊኒም ሆስፒታል እና ሜዲካል ኮሌጅ ረዳት ፕሮፌሰር እና የህጻናት ሐኪም የሆኑት ዶክተር ፋሲል መንበረ የህጻናት የተሟላ ዕድገት አካላዊ፣ አዕምሯዊ፣ ሥነ ልቦናዊ እና ማኅበራዊ ዕድገቶችን እንደሚያጠቃልል ይገልጻሉ።

እነዚህን እድገትን የሚያግዙ በርካታ ጉዳዮች ቢኖሩም "ከዚህ ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ የሚይዘው ምግብ ነው" ይላሉ።

ይህም ልጆች ቤት ውስጥ ሊሚመገቡትም ሆነ በምሳ ዕቃቸው ሊሚይዙት የሚገባው ምግብ ምንድን ነው? የሚል ጥያቄ ማስከተሉ አይቀርም።

ቢቢሲ ያነጋገራቸው የህጻናት ሐኪሙ እና የተለያዩ የሥነ ምግብ ባለሙያዎች በጉዳዩ ዙሪያ ወላጆችን ሊጠቅሙ የሚችሉ ወሳኝ ነጥቦችን አንስተዋል። ከዚያ በፊት ግን የሚከተሉት ነጥቦች ወሳኝ ናቸው።

ምግብና የህጻናት ሁለንተናዊ ዕድገት

በህጻናት አካላዊ ዕድገት ውስጥ ምግብ ሁለት አይነት ተግባራትን ይከውናል።

የመጀመሪያው በሰውነት ውስጥ የተለያዩ ተግባራት ያላቸው ህዋሳትን ለሥራ ብቁ ማድረግ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ አካላዊ መጠንን ማሳደግ ነው።

አዕምሮአዊ ዕድገት ደግሞ ነገሮችን የመገንዘብ፣ የማሰብ እና ምክንያታዊ የመሆን ብቃትን የሚመለከት ነው።

"ከተወለዱ በኋላ ስድስት ወር የእናት ጡት ብቻ የወሰዱ እና ከዚያ በኋላ ከእናት ጡት በተጨማሪ በቂ ምግብ ያገኙ ህጻናት ከፍተኛ የሚባል የአዕምሮ ብቃትን ያስመዘግባሉ" የሚሉት ዶ/ር ፋሲል ህጻናት በመጀመሪያው አንድ ዓመት አእምሯቸው እስከ 70 በመቶ እንደሚያድግ ያስረዳሉ።

በማኅበራዊ ዕድገት ውስጥ ደግሞ "የሚቀርብላቸው ምግብ ከቤተሰብ እንክብካቤ ጋር ስለሚያያይዙት አዕምሯቸውም እንዲሁም ከሰዎች ጋር ያላቸው መስተጋብር በጥሩ ሁኔታ እያደገ ይሄዳል ማለት ነው" ብለዋል።

የመጀመሪያዎቹ 1000 ቀናት

በህጻናትና የተሞላ ዕድገት ውስጥ ወሳኙ ጊዜ ከተጸነሱበት ቀን ጀምሮ ሁለት ዓመት እስከሚሞላቸው ድረስ ያሉት አንድ ሺህ ቀናት ናቸው።

እንደ ጤና ሚኒስቴር መረጃ በመጀመሪያዎቹ 270 ቀናት ወይም ከጽንስ እስከ ወሊድ ባሉት 9 ወራት እናት ከአትክልት፣ ከእንስሳት ተዋፅኦ፣ ከጥራጥሬ እና ከሌሎች የምግብ ዘርፎች በማሰባጠር በበቂ ሁኔታ ብትመገብ ጽንሱ ይፋፋል።

ከወሊድ በኋላ ባሉት 180 ቀናት ወይም ልጁ 6 ወር እስኪሞላው የእናት ጡት ብቻ ሲመክር፤ በተቀሩት 550 ቀናት ወይም ከስድስት ወር እስከ ሁለት ዓመት ባለው ጊዜ ከእናት ጡት በተጨማሪ ከተለያዩ የምግብ ዘርፎች ስብጥሩን የጠበቀ ምግብ ለልጁ ማቅረብ ህጻኑ የተቀና የዕድገት ጉዞ እንዲኖረው ይረዳል።

ከዚህም በኋላ ባሉት ጊዜያት የህጻናት አመጋገብ ትኩረት የሚፈልግ ነው። ወደ ትምህርት ቤት መሄድ የጀመሩ ህጻናት ምን ይመገቡ የሚለውን እንመልከት።

ለትምህርት የደረሱ ልጆች እና ምግብ

እንደ ዶ/ር ፋሲል ገለጻ ከ5 እስከ 10 ዓመት ያሉ ህጻናት እድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ይባላሉ። ከሁለት ዓመት በታች ያሉ ህጻናት ሁለንተናዊ ዕድገታቸው ፈጣን የሚባል ሲሆን ለትምህርት ዝግጁ በሚሆኑበት ጊዜ ግን እድገታቸው ዝግ ያለ ቢሆንም የማያቋርጥ ነው።

ታዲያ በዚህ ጊዜ ልጆች የሚመገቧቸው ምግቦች በሦስት መልኩ ይጠቅማቸዋል። የመጀመሪያው ጤናማ አካላዊ ዕድገት፣ ማለትም የተስተካከለ ክብደት እና ቁመት እንዲኖራቸው ይረዳል። ሁለተኛው የበሽታ መከላከል አቅማቸውን ለማዳበር እጅግ አስፈላጊውን ተግባር ይከውናል።

ሦስተኛው ደግሞ ጤናማ የአመጋገብ ሥርዓትን የሚተዋወቁበት ጊዜ ነው።

በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምግብ ሳይንስ እና የሥነ ምግብ መምህሩ ዶ/ር ይሁኔ አየለ፣ ህጻናት ለትምህርት የሚደረሱበትን ጊዜ [ከ5 እስከ 10 ዓመት ያለው] የእድሜ ልክ የአመጋገብ ባህላቸው የሚቀረጽበት ጊዜ ሲሉ ነው ሲሉ ይገልጻሉ።

"ይህ ጊዜ አስተሰሰባቸው የሚቀረጽበት ነው እንደምንለው ሁሉ በአመጋገብም መሠረታዊ የምግብ ባህላቸው የሚቀረጽበት ነው።

"ልጆች በዚህ ጊዜ የወደዱትና የለመዱት ሥርዓት በህይወታቸው ልክ አብሯቸው ያድጋል። ስለዚህ ወላጆች ጥሩ ጥሩ የምግብ ባህሎችን ማስለመድ - አትክልት፣ ፍራፍሬና ጥራጥሬን ማስለመድ" ተገቢ እንደሆነ ገልጸዋል።

በዚህ ሃሳብ የሚስማሙት ዶ/ር ፋሲል "አብዛኞቹ ከአምስት ዓመት በላይ ያሉ ህጻናት ጥሩ የምግብ ፍላጎት ስላላቸው ይህንን በመጠቀም ብዙ አይነት ምግብ በማቅረብ ጣዕም እንዲለዩ ማድረግ ያስፈልጋል" ብለዋል።

ልጆችን ምን እንመግባቸው?

በአሜሪካ በዩኒቨርሲቲ ኦፍ ላስቬጋስ በምግብ ዝግጅት እና ሥነ ምግብ ትምህርታቸውን የተከታተሉት ሼፍ አዲስዓለም ብዙአየሁ ልጅነት አካላዊ ዕድገት በተከታታይ የሚጨምርበት ብቻ ሳይሆን በጫዋታዎች ከፍተኛ ኃይል የሚወጣበት ጊዜ ስለመሆኑ ይናገራሉ።

በዚህም ሳቢያ ለልጆች የሚቀርበው ምግብ እነዚህን ታሳቢ ያደረግ መሆን እንደሚገባው ገልጸው፣ ለዚህም ፕሮቲን እና ካርቦሃይድሬት ያላቸውን ምግቦች ወሳኝ መሆናቸውን ጠቁመዋል። እንቁላል፣ ሥጋ፣ የወተት ውጤቶች፣ ለውዝ፣ ቦሎቄና ከመሰሉ ምግቦች ፕሮቲንን ማግኘት ይችላል።

ጤናማ ካርቦሃይድሬትን ደግሞ ከአፕል፣ ሙዝ፣ እንጆሪን ከመሰሉ ፍራፍፍሬዎች እና ከዳቦና ፓስታ ዓይነት ምግቦች ይገኛሉ።

ከእነዚህ የምግብ አይነቶች በተጫማሪ ጤናማ የቅባት ምግቦች፣ ፋይበር ወይም የቃጫ ዝርያ ያላቸው ምግቦች፣ ማዕድን እና ቫይታሚንም ሊካተት እንደሚገባ ዶ/ር ፋሲል ያስረዳሉ።

ልጆች ከእነዚህ የምግብ ዓይነቶች ከቁርስ፣ ምሳና እራት እና በየማሃሉ ፍራፍሬዎችን በ'ስናክ' ወይም መክሰስ መልክ በቀን እስከ ስድስት ጊዜ እንዲመገቡ ይመክራሉ። ሐኪሙ ለልጆች የምግብ ሰዓት የሚሆኑ የምግብ አማራጮችን ጠቁመዋል።

ቁርስ፡ እንቁላል፣ ወተት፣ ፍራፍሬ፣ ገብስ እና ሩዝን የመሰሉ የእህል ዘሮችን፣ ለውዝ/የለውዝ ቅቤ [ከአንድ ወይም ከሁለት የሻይ ማንኪያ ያልበለጠ]፣ ሳንድዊች፣ ባቄላ፣ አተር፣ አኩሪ አተር፣ ቦሎቄ።

እነዚህ ምግቦች ሃይል ሰጪ በመሆናቸው በቀን ውስጥ በቂ ኃይል እንዲኖራቸው ከማገዙም በተጨማሪ ሰውነታቸውን በጥሩ ሁኔታ እንዲገነባ ያግዛል ሲሉ ዶ/ር ፋሲል አስረድተዋል።

ምሳና እራት፡ እንጀራና ዳቦ የመሰሉ ከእህል ዘር የሚዘጋጁ ምግቦች፣ ጎመን፣ ካሮት፣ ቆስጣን የመሰሉ አትክልቶች ሲሆን ከሚመገቡት ግማሽ ያህሉን መሸፈን እንደሚገባው ጠቁመዋል። የተቀረው ክፍል ሥጋና እንቁላልን ወይም ቦሎቄን በመሰለ ፕሮቲን እንዲሁም በፓስታና በመኮሮኒ በመሳሰሉ ካርቦሃይድሬት ሊሸፈን ይገባዋል።

በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢኒስቲትዩት የምግብ ሥርዓት እና ሥነ ምግብ ምርምር ዳይሬክተሩ ዶ/ር ማስረሻ ተሰማ ልጆች የሚመገቧቸው ምግቦች "የኢኮኖሚ ሁኔታን ባገናዘበ መልኩ" የተሰባጠረ መሆን ይገል" ይላሉ።

ይህም ማለት የተለያዩ የምግብ አይነቶች የተለያየ ዓይነት ንጥረ ነገሮችን ስለሚይዙ የምግቦቹ አይነት በበረከተ ቁጥር የሚያገኙት ጥቅም ከፍ ይላል።

ለምሳሌ "ፓስታ ወይም መኮሮኒ ብቻ [አዘውትረው] የሚመገቡ ከሆነ በዋናነት 'ኢነርጂ' [ኃይል] ብቻ ነው እንጂ የሚያገኙት ሌሎች አስፈላጊ ንጥረ ነገሮችን አያገኙም ማለት ነው። ልጆች ደግሞ በቂ የሆነ ንጥረ ነገር ይፈልጋሉ" ሲሉ ያስረዳሉ።

ልጆቻችን ማዘውተር የሌለባቸው ምግቦች የትቹ ናቸው?

"ልጆች ናቸው ችግር የለውም እየተባለ ያለ ቁጥጥር የሚሰጣቸው ከፍተኛ ስኳር ያላቸው ምግቦች የኋላ ኋላ ዋጋ ያስከፍላል" የሚሉት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምግብ ሳይንስ እና ሥነ ምግብ ማዕከል ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶ/ር ቃለአብ ባዬ ናቸው።

ዶ/ር ቃለአብ በፋብሪካ የሚዘጋጁ ምግቦች፣ ስኳር፣ ከፍተኛ የስኳርና የጨው መጠን ያላቸው ጣፍጭ ምግቦችና መጠጦች፣ ከፍተኛ ስብ ወይም ቅባት ያላቸው ምግቦች፣ እንዲሁም የተጠበሰ ድንች ወይም ቺፕስን ጨምሮ ሌሎች በዘይት የሚጠበሱ ምግቦችን ልጆች አዘውትረው እንዲመገቡ ማድረግ በጊዜ ሂደት የጤና ጠንቅ ማስከተሉ አይቀርም ብለዋል።

ዶ/ር ፋሲል ልጆቻቸው ምግብ እንዲወስዱላቸው ስኳርና ቅባት የሚያበዙ ወላጆች እንዳሉ ጠቁመው ይህም የአጭር እና የረጅም ጊዜ መዘዝ ይዞ ይመጣል ይላሉ።

የጥርስ መበላሸት፣ መጥፎ የአፍ ጠረን እና በከፍተኛ ሁኔታ የምግብ ፍላጎት መቀነስ በስኳር ወይም በጨው መብዛት ምክንያት የአጭር ጊዜ ጉዳት ሆኖ ሊከሰት ይችላል።

በረጅም ጊዜ ወይም 20 ዓመት ከሞላቸው በኋላ ደግሞ "በፊት ያዘወተሩት ምግብ" ደም ግፊትና የልብ ችግርን ጨምሮ ለተለያዩ ችግሮች ሊያጋልጣቸው ይችላል።

እነዚህ ምግቦች ደግሞ ብዙ ጊዜ መነሻቸው የታሸጉ ወይም የፋብሪካ ምግቦች ናቸው። "ከውጪ አገራት የሚገቡና የታሸጉ ምግቦች የቆይታ ጊዜያቸውን ለማራዘም በጨው እና በተለያዩ ኬሚካሎች የታሹ ናቸው" ይላሉ ዶ/ር ይሁኔ።

ከዚህ ይልቅ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚዘወተሩ በቤት ውስጥ የሚዘጋጁ ምግቦችን ይመክራሉ። ለምሳሌ በሶን ብቻውን ወይም ከወተት ወይም ከለውዝ ጋር መሰጠት እጅግ ጠቃሚ ነው መሆኑን ጨምረው ይመክራሉ።

በልጆቻችን ምሳ ዕቃ ምን ይቋጠር?

ለዚህ ጥያቄ የዶ/ር ይሁኔ መልስ አጭር ነው 'ቤት ያፈራውን' የሚል። "ማንም ሰው በቤቱ ለልጆቹ ቤት ያፈራውን ምግብ ማዘጋጀት ይችላል። ቤት ያፈራው ሲባል ግን አንድ አይነት ምግብ ማለት አይደልም። ጠዋት ቁርስ እንጀራ፣ አስሮ የሄደውም [በምሳ ዕቃ] እንጀራ፣ ሲመጣም እንጀራ መሆን የለበትም። በተቻለ መጠን ወላጆች ባላቸው አቅም ምግቡን ለመለያየት መሞከር አለባቸው" ሲሉ ገልጸዋል።

ሼፍ አዲስዓለምም ይህንን ሃሳብ ይጋራሉ። በሥራ አጋጣሚያቸው የታዘቡትን ሲናገሩ "ልጆቹ የሚቋጠርላቸው ከእንጀራ ፍርፍር፣ ፓስታ፣ መኮሮና ሩዝ አያልፍም" ይላሉ።

ይህ በቂ ፕሮቲን ለሎች ንጥረ ነገሮችን እንዳያገኙ ምክንያት ይሆናል ይላሉ። "ፕሮቲን አላገኙም ማለት ዕድገታቸውን ሊረዳ የሚችል ነገር አላገኙም ማለት ነው። አትክልት የለም ማለት ደግሞ በሽታ የመከላከል አቅማቸው" ላይ ተጽእኖ እያሳደረ ነው ማለት ነው ሲሉ ገልጸዋል።

ፕሮቲን ከሥጋም፣ ከእንቁላልም፣ ከቦሎቄም፣ ከባቄላም ይገኛል። ሥጋና እንቁላሉ ውድ ነው ቢባል እንኳን ባቄላውን ባነሰ ዋጋ ማግኘት ይቻል ይሆናል።

ስለዚህ በምሳ ዕቃ ውስጥ ለልጆች ኃይልና ጉልበት እንዲሁም ፕሮቲን ሰጪ ምግቦችን ሊያካትት ይገባል። ይህም ከአትክልት፣ ከእንሳት ተዋጽኦ፣ ከፍራፍሬና ጥራጥሬዎች ማገኘት ይችላሉ። ታዲያ የምግብ ዘርፎቹ/አይነቶቹ በርከት ሲል ለዕድገት አስፈላጊ የሆኑ ነጥረ ነገሮች የመገኘቱ ዕድል ሰፊ ነው።

ዶ/ር ቃለአብ 'ጊዜ የለኝም' ወይም 'ልጆቹ ይወዱታል' በሚል የታሸጉ ምግቦችን ለልጆች ሰጥቶ ወደ ትምህርት ቤት መላክ ተጊቢ አይደልም ሲሉ መክረዋል።

"ከዚያ ይልቅ ወይ ሙዝ ወይ ብርቱካን ቢሰጧቸው" ለጤናና ዕድገታቸው ጠቃሚ ነው። ፍሪጅ ውስጥ የተቀመጠ ምግብና አዲስ የተሰራን ምግብ ቀላቅሎ መቋጠር ምግብ እንዲበላሽ መክንያት ሊሆን እንደሚችልም ጠቁመዋል።

ዶ/ር ፋሲል የተቋጠረበት ምሳ ዕቃ ቀጥተኛ የፀሃይ ብርሃን እንዳያገኘው ማድረግ እና በከፍተኛ ንጽህናን መዘጋጀት አለበት ብለዋል።

ለልጆች የሚስማማውን ምግብ እንዴት እንስጣቸው?

'እርግጥ ነው ልጆች የሚመርጡት እና የሚመቻቸው ስኳር የበዛባቸው ጣፍጭ ምግቦችን ነው። ስለዚህ ጠቃሚ የሚባለውን ለመመገብ አሻፈረኝ ሊሉ ይችላሉ። ምንም እንኳን ጠቃሚ ቢሆን በኃይል እና በቁጣ ማድረግ የበለጠ ምግቡ እንዲጠሉት ሊያደርግ ይችላል ይላሉ ዶ/ር ማስረሻ።

ከዚያ ይልቅ ከሚወዷቸው ምግቦች ጋር ቀላቅሎ መስጠት አማራጭ ነው። "ፈጽሞ ሊያዩት የማይፈልጉት ዓይነት ምግብ ከሆነ" ይላሉ ሼፍ አዲስዓለም ቦሎቄን ምሳሌ በማድረግ "ተፈጭቶ ከሚወዱት ምግብ ጋር ሊሰጣቸው ይችላል" በማለት አስረድተዋል።

ዶ/ር ይሁኔ በቴሌቪዥን ወይም በሌሎች መንገዶች የህጻናትን ጉጉት ከፍ ሊያደርጉ የሚችሉ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችን ማስታወቂያ መላ ሊባሉ ይገባል ብለዋል።

"ህጻናት በከፍተኛ ሁኔታ ተጽእኖ እየተደረገባቸው ነው። ዛሬ ቲቪ ላይ ያዩትን ምግብ ነገ አምጡ ስለሚሉ" በዚህ ላይ የምግብ ግንዛቤ ሊሰራና ቁጥጥጥር ሊኖር እንደሚገባ ይጠቁማሉ።

የዚህን ሃሳብ ትክክለኝነት የሚገልጹት ዶ/ር ፋሲል ደግሞ ልጆችን ላይ ጫና የሚፈጥሩ የዚህ ዓይነት ማስታወቂያዎችን መቆጣጠር "የመንግሥት ሥራ ቢሆንም" ወላጆችም እንደወላጅ ለመሰል ማስታወቂያዎች እንዳይጋለጡ መጣር እንዳለባቸው አመላክተዋል።

በተጨማሪም ህጻናት በቂ መደበኛ እንቅስቃሴ የማያደርጉ ከሆነ፣ ረጅም ሰዓት ጌም የሚጨወቱ ወይም ቲቪ የሚመለከቱ ከሆነ የምግብ ፍላጎታቸውን እንዲቀንስ ሰበብ ይሆናል።

የህጻናት ሐኪሙ ዶ/ር ፋሲል ወላጆች ለልጆቸው በአመጋገባቸውም አርአያ መሆን ይገባቸዋል ይላሉ።

የአዋቂዎች ጤናማ የምግብ ዝርዝር መጠኑ ቢያንስም ለህጻናትም የተስማማ ነው። ህጻናት ደግሞ ከወላጆች ምክር በላይ ተግባሩን ይይዙታል። ስለዚህ በምግብ ግብይት ጊዜ ህጻናቱን ማሳተፍን ጨምሮ ልጆች ጤናማ አመጋገብን ማስለመድ ዋጋው ለራስ ነው።