አሜሪካ ህወሃት ወደ ደሴ እና ኮምቦልቻ የሚያደርገውን ግስጋሴ እንዲገታ ጥሪ አቀረበች

ኔድ ፕራይስ

የፎቶው ባለመብት, KEVIN LAMARQUE

ህወሃት ወደ ደሴ እና ኮምቦልቻ ከተሞች የሚያደርገውን ግስጋሴ እንዲገታና እንዲሁም ከአማራና አፋር ክልሎችም እንዲወጣ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥሪ አቀረበ።

አሜሪካ በቃለ አቀባይዋ ኔድ ፕራይስ በኩል በትናንትናው ዕለት ጥቅምት 21፣ 2014 ዓ.ም በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫም በሰሜን ኢትዮጵያ የሚካሄደው ጦርነት መስፋፋት አሳስቦኛል ብላለች።

ከዚህም በተጨማሪ ህወሃት በከተሞች ላይ ከባድ የጦር መሳሪያዎችን እንዳይጠቀም ከማሳሰብ በተጨማሪ የኢትዮጵያ መከላከያ በመቀለና በተለያዩ የትግራይ ክልሎች የሚያደርገውንና ለበርካቶች ሞት ምክንያት የሆነውን የአየር ጥቃትም ማቆም አለበት ብሏል።

ጥቅምት 21፣ 2014 ዓ.ም የደቡብ ወሎ ዞን ዋና ከተማ የሆነችው የደሴ ከተማ የፌደራሉ ሠራዊት ማፈግፈጉንና የህወሓት ኃይሎች መግባታቸው መዘገቡን ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥት ከተማዋ አሁንም በቁጥጥሩ ስር መሆኗን ገልጿል።

ቢቢሲ ቅዳሜ ረፋድ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች የህወሓት አማፂያን ወደ ከተማው ሲገቡ መመልከታቸውንና የመንግሥት ኃይሎች ማፈግፈጋቸውን ገልፀዋል።

በተጨማሪም አማፂያኑ ወደ ሰኞ ገበያ፣ ተቋም እና ሳላይሽ አካባቢዎች ሲያመሩ እንደታዩና በከተማዋ ዳርቻ አካባቢ ተኩስ እንደሚሰማ ለቢቢሲ ገልፀው ነበር።

የ X ይዘትን ይለፉት
ይዘቱን X ይፈቅዳሉ?

ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።

ማሳሰቢያ፡ የሦስተኛ ወገን ይዘቶች ማስታወቂያ ሊኖራቸው ይችላል

የ X ይዘት መጨረሻ

ጥቅምት 24 አንድ አመት የሚደፍነውና በትግራይ ተከስቶ በአማራና አፋር ክልሎች የተዛመተው ጦርነት በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ህይወት ቀጥፏል ፣ ሚሊዮኖችን አፈናቅሏል እንዲሁም የአገሪቱን ምጣኔ ኃበትም አሽመድምዷል።

ከዚህም ጋር በተያያዘ አሜሪካ ለዚህ ጦርነት ምንም አይነት ወታደራዊ መፍትሄ እንደሌለው በተደጋጋሚ ያስታወቀች ሲሆን በትናነትናውም ዕለት ይህንኑ ሃሳብ በማንሳት ሁሉም ወገኖች ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የተኩስ አቁም ድርድር መጀመር እንዳለባቸውም አሳስባለች።

ከዚህም በተጨማሪ አሜሪካ አሁንም በትግራይ፣ በአማራ ወይም በአፋር ክልል ላሉ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ህይወትን ለመታደግ ሰብዓዊ ዕርዳታ ለማድረስ ቁርጠኛም መሆኗንም አስታውቃለች።

በሰሜን ኢትዮጵያ ሆን ተብሎ የሰብአዊ እርዳታ መከልከሉን የሚገልጹ ሪፖርቶች መውጣታቸው ስጋት እንደሆነባትም አሜሪካ በመግለጫዋ ጠቅሳ በትግራይ ክልል 900 ሺህ የሚገመቱ ነዋሪዎች በረሃብ አፋፍ ላይ እንዳሉና የኢትዮጵያ መንግሥት መድሃኒት፣ ነዳጅና ለእርዳታ ድርጅቶች የሚውል ገንዘብ ጨምሮ አስቸኳይ ሰብዓዊ እርዳታዎችን አግዷል ስትልም ወቅሳለች።

ከዚህም ጋር በተያያዘ በጦርነቱ ተሳታፊ የሆኑ ወገኖች በሙሉ ያልተቋረጠ ሰብአዊ አገልግሎት እንዲሰጡ እና እንዲያመቻቹ ጥሪ ቀርቦላቸዋል።

ከዚህ ቀደም አሜሪካ በተደጋጋሚ እንደምትለው ሁሉም ወገኖች ሲቪል ዜጎችን እንዲጠብቁ፣ የሰብዓዊ መብት ረገጣዎች እና አለም አቀፍ የሰብዓዊ ህግ ጥሰቶችንም እንዲያቆሙም በትናንትናው መግለጫው ያሳሰበች ሲሆን በጦርነቱ ጥሰት የፈፀሙ አካላትም ተጠያቂ ሊሆኑም እንደሚገባ አስታውቃለች።