የኬንያው ሳፋሪኮምና የደቡብ አፍሪካው ቮዳኮም በጋራ ወደ የኢትዮጵያ የቴሌኮም ገበያ የመግባት ፍላጎት አላቸው

የፎቶው ባለመብት, Construction Photography/Avalon
የኬንያ ትልቁ የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ኩባንያ ሳፋሪኮም፤ ከደቡብ አፍሪካ አቻው ቮዳኮም ጋር በመሆን ኢትዮጵያ በቀጣዩ የፈረንጆች ዓመት ልትሰጥ ካሰበቻቸው ሁለት የቴሌኮም አገልግሎት ፈቃዶች ውስጥ አንዱን ለማግኘት እየሠራ መሆኑን ሮይተርስ ዘገበ።
የሳፋሪኮም ተጠባባቂ ሥራ አስፈጻሚው ማይክል ጆሴፍ እንዳሉት፤ በቮዳኮምና በብሪታኒያው ቮዳፎን በከፊል ባለቤትነት ሥር ያለው ኩባንያ፤ በመንግሥት የሚተዳደረው ኢትዮ-ቴሌኮምን በከፊል በመግዛት፤ ከፍተኛ ትርፍ ወደሚያስገኘው የኢትዮጵያ የቴሌኮም ገበያ ለመቀላቀል ከውሳኔ አልደረሰም።
የቴሌኮም ሞገዱን ለማግኘት ከፍተኛ ወጪ እንደሚያስፈልግ የጠቀሱት ጆሴፍ፤ ለሮይተርስ እንደተናገሩት ፈቃዱን ለማግኘት የሚፈልጉ ተቋማት የደለበ የገንዘብ ምንጭ እንደሚያስፈልጋቸው ጠቁመዋል።
"ለአየር ሞገዱ በጨረታ መወዳደር ያስፈልጋል። ፈቃዱን ለማግኘት በቢሊዮን ዶላር የሚገመት ወጪ እንደሚጠየቅ እየተነገረ ነው" ሲሉ ተቋሙ ያገኘውን የመጀመሪያውን ግማሽ ውጤት ይፋ ካደረጉ በኋላ ተናግረዋል።








