በእነብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞ መዝገብ ፖሊስ የጠየቀው የግዜ ቀጠሮ ውድቅ ተደረገ

እነብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞ

የፎቶው ባለመብት, FACEBOOK

በእነብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ የተከሰሱ ተጠርጣሪዎች ላይ ፖሊስ የጠየቀውን የግዜ ቀጠሮ ፍርድ ቤት ውድቅ አደረገ።

ሰኔ 15 በአማራ ክልል ተሞከረ ከተባለው 'መፈንቅለ መንግስት' ጋር በተያያዘ የጸጥታ ኃላፊዎችን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ በቁጥጥር ሥር የዋሉ ግለሰቦች ጉዳይ ዛሬ ሃምሌ 29 ቀን 2011ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ታይቷል።

ፖሊስ ተጨማሪ የ28 ምስክሮችን እና የተወሰኑ የሰነድ ማስረጃዎችን ማየቱን ለፍርድ ቤት አስታውቋል። ተጨማሪ የምስክሮችን ቃል ለመቀበል እየሰራ መሆኑን እና የፎሬንሲክ እና የስልክ ምርመራ ውጤቶች ያልደርሱ መሆናቸዉን በመጥቀስ ተጨማሪ የ14 ቀን የግዜ ቀጠሮ እንዲሰጠቀው ፍርድ ቤቱን ጠይቋል።

የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው በደንበኞቻቸው ላይ ምስክሮች አለመገኘታቸውን፤ ደንበኞቻቸው ቢወጡ በቴክኒክ እና በስልክ ምርመራ ላይ ምንም ተጽህኖ የማያሳድሩ መሆናቸውን እንዲሁም የሰው ማስረጃ ፣የቴክኒክ እና የሰነድ ማስረጃዎች ጎን ለጎን መካሄድ ነበረባቸው በሚል የግዜ ቀጠሮው ውድቅ እንዲሆን ጠይቀዋል።

ግራ ቀኙን ያዳመጠው ፍርድ ቤት የፖሊስን ተጨማሪ ግዜ ቀጠሮ ጥያቄ ውድቅ አድርጎ እስከ ነሐሴ 13 ቀን 2011 ዓ.ም ፖሊስ ክስ እንዲመሰርት ትዕዛዝ በመስጠት የዛሬውን ችሎት አጠናቋል።

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ 218 ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው የነበረ ሲሆን 160 የሚሆኑት በተለያየ ግዜ ተለቀዋል።