የፈረንሳይ ጦር ደራሲያንን "የወደፊቱን ተንብዩልኝ" አለ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የፈረንሳይ ጦር የወደፊቱን ተግዳሮት የሚተነብዩ ሳይንሳዊ ልብ ወለዶችን የሚደርሱ "የጸሀፍት ቡድን" ሊያቋቁም መሆኑ ተሰማ።
ከመከላከያ የፈጠራ ኤጀንሲ ሪፖርት መረዳት እንደተቻለው፤ ምጡቅ ምናባዊ ደራሲያን የወታደሩ ስትራቴጂስቶች ያልጠበቋቸውን ነገር ግን "ሊገጥሙ የሚችሉ እንቅፋቶችን" ይገምታሉ።
ሪፖርቱ አክሎም የጸሀፍቱ ቡድን የሚሠሩት ሥራ የተንኮል ተግባራትን ለመዋጋት ጠቃሚ ነው ብሏል።
ይህ የፈረንሳይ ጦር የመከላከል አቅሙን በተለያዩ የፈጠራ ውጤቶች ለማገዝ የሚያደርገው ጥረት አካል መሆኑ ተገልጿል።
እሁድ ዕለት በፈረንሳይ ተከብሮ በዋለው የመከላከያ ሠራዊት ቀን ላይ በሞተር ከፍ ብሎ የሚንሳፈፍ ወታደር፣ መሣሪያ ታጥቆ ከስሩ እንደ ጉንዳን የሚርመሰመሱ ጠላቶቹ ላይ በግርማ ሞገስ ሲገለጥ የሚያሳው ትዕይንት በርካቶችን እጃቸውን በአፋቸው ያስጫነ የፈጠራ ውጤት ነበር።
ከዚህ የፈጠራ ውጤት ትዕይንት በኋላ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማርኮን በቲውተር ገጻቸው ላይ" ዘመናዊና በአዳዲስ ፈጠራ በታገዘው የጦር ሠራዊታችን ኮርቼያለሁ" ብለዋል።
የ"ጸሀፍት ቡድኑ" እነማን ናቸው?
ይህ የደራሲያን ስብስብ 'ሬድ ቲም' የሚባል ሲሆን አራት ወይንም አምስት የሳይንስ ልብወለድ ደራሲያን በአባልነት ይይዛል።
ደራሲዎቹ የሚጠበቅባቸው ከተለመደው ወጣ ያለ፣ ከባህላዊው ውትድርና ያፈነገጠ፣ ጥበብና ትንበያን በአንድ ያጣመረ የፈጠራ ሥራ ማሰብ ነው።
በሚና ነጠቃ እና ሌሎች ስልቶች የአሸባሪ ድርጅቶች ወይንም ባዕዳን እንዴት የተሻሻሉና ዘመኑን የቀደሙ ቴክኖሎጂዎችን እንደሚጠቀሙ ያሰላስላሉ።
የፈረንሳይ መከላከያ ሚኒስትር ፍሎረንስ ፓርሊ አገራቸው በውትድርናው መስክ ያለን ፈጠራ "በእሽቅድድሙ ላይ የበላይነቱን" ለመያዝ እንደምትሠራ ገልጠዋል።
ባለፈው ሳምንት በተካሄደው የፈረንሳይ መከላከያ ሠራዊት ቀን ላይ የሰው አልባ አውሮፕላኖችን ሲግናል መከላከል የሚያስችል ፈጠራ "Nerod F5 microwave jammer" ለእይታ ቀርቧል።
በአሁኑ ወቅት የፈረንሳይ ጦር በማሊ በሚያደርገው ግዳጅ ላይ ሮቦቶች እንዲያግዙት የሚያስችል ሙከራ እየተካሄደ ነው።
ከዚህ በፊት በሳይንሰዊ ልብወለድ ውስጥ የታዩና እውን የሆኑ ስራዎች
ዘ ሙን ላንዲንግ፡ በ1865 የተደረሰው የጁለስ ቨርኔ ረዥም ልብ ወለድ ከፍሎሪዳ ሶስት ሰዎች ወደ ጨረቃ ሲላኩ የሚያሳይ የታሪክ ፍሰት ላይ ተመስርቶ የተጻፈ ነው። ከ104 ዓመት በኋላ ተመሳሳይ ተልዕኮ ያለው ጎዞ ወደ ጨረቃ ተደርጓል።
ተንቀሳቃሽ ምስል የሚያሳዩ ስልኮች፡ በ1927 ለእይታ የበቃው ሜትሮፖሊስ ፊልም ላይ፣ ምንም እንኳ ስልኩ ከዛሬው ተንቀሳቃሽ ስልክ ከፍያለ ቢሆንም፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ተንቀሳቃሽ ምስል የሚታይበት ስልክ የታየው ያኔ ነበር።
አቶሚክ ቦምብ፡ ኤችጂ በ1914 በደረሰው ረዥም ልብወለዱ ላይ አቶሚክ ቦምብን ተንብዮ ነበር። በልብወለዱ ላይ ያኔ በነበረው የአቶሚክ ሳይንስ ቦምቡ ሲፈነዳ የሚያሳይ ትዕይንቶች በመጽሐፉ ላይ ሰፍረው ነበር።














