ቀጥታ, አሜሪካ የኢራንን የጭነት መርከብን መያዟን አስታወቀች፤ ኢራን አጸፋውን እንደምትመልስ ዝታለች

በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን የዘጋችው አሜሪካ፤ በኢራን ባንዲራ የሚንቀሳቀስ የጭነት መርከብን መጥለፏን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ። ኢራን የአሜሪካ እርምጃ የተኩስ አቁም ጥሰት እንደሆነ የገለጸች ሲሆን “በትጥቅ የታገዘ የባሕር ላይ ውንብድና” ስትል ለጠራችው ለዚህ ድርጊት አጸፋውን እንደምትመልስ ዝታለች።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን በአሜሪካ መርከብ ላይ በድሮን ጥቃት መፈፀሟ ተዘገበ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ሚንቀሳቀሱ መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ቅዳሜ ዕለት በሆርሙዝ ወሽመጥ የነበሩ መርከቦች

    አሜሪካን የኢራንን ጭነት የሚያጓጉዝ መርከብን በቁጥጥር ስር ማዋሏን ተከትሎ፤ ቴህራን በኦማን ባሕረ ሰላጤ ላይ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር መርከቦች ላይ የድሮን ጥቃቶችን መፈጸሟን ከእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም ዜና ወኪል ዘገበ።

    አሜሪካ ትናንት የኢራን ባንዲራን አንግቦ እየተጓዘ የነበረ የጭነት መርከብን ጠልፋ በቁጥጥር ስር ማዋሏን ካስታወቀች በኋላ ኢራን አጸፋውን እንደምትመልስ ዝታ ነበር።

    አሁን በአሜሪካ ጦር መርከብ ላይ ተፈጽሟል በተባለው ጥቃት የደረሰ ጉዳት ስለመሆኑ እስካሁን መረጃ አልወጣም።

    የኢራን ጦር ኃይሎችን የሚያስተባብረው የተልዕኮ ማዘዣ ጣቢያ የሆነው ኻታም አል-አንቢያ የአሜሪካ ባሕር ኃይል በወሰደው እርምጃ የተኩስ አቁም ስምምነቱ መጣሱን እና የአሜሪካ ጦር ላይ የአፀፋ እርምጃ እንደሚወስድ ገልፆ ነበር።

  2. ትራምፕ የኢራን መርከብ በቁጥጥር ስር መዋሉን ካሳወቁ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    ነዳጅ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን ባንዲራ የሚያውለበልብ መርከብ በዋሽንግተን ቁጥጥር ስር መዋን ካሳወቁ በኋላ ሠኞ ጠዋት የዓለም ነዳጅ ገበያ ጭማሪ አሳየ።

    ይህ የሆነው ቅዳሜ ዕለት ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለንግድ መርከቦች እንደምትዘጋ በድጋሚ ካሳወቀች እና ወደ ወሽመጡ የሚጠጉ መርከቦችን ዒላማ እንደምታደርግ ካሳወቀች በኋላ ነው።

    ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በ4.74 በመቶ በመጨመር 94 ዶላር ገብቷል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በጥምረት ኢራን ላይ ጥቃት ከፈፀሙ እና ቴህራን 20 በመቶ የዓለም ነዳጅ እና ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ መጓጓዣን በመዝጋቷ ምክንያት የኃይል ገበያው ከፍተኛ ውጣ ውረዶችን አይቷል።

  3. አሜሪካ የኢራንን የጭነት መርከብን መያዟን አስታወቀች፤ ኢራን አጸፋውን እንደምትመልስ ዝታለች

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን የዘጋችው አሜሪካ፤ በኢራን ባንዲራ የሚንቀሳቀስ የጭነት መርከብን መጥለፏን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ በሶሻል ትሩዝ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው እንዳስታወቁት ‘ቱስካ’ የተሰኘው መርከብ የተያዘው ጉዞውን እንዲያቆም በአሜሪካ ባሕር ኃይል የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ባለማክበሩ ነው።

    ኢራን የአሜሪካ እርምጃ የተኩስ አቁም ጥሰት እንደሆነ የገለጸች ሲሆን “በትጥቅ የታገዘ የባሕር ላይ ውንብድና” ስትል ለጠራችው ለዚህ ድርጊት አጸፋውን እንደምትመልስ ዝታለች።

    እርምጃው እንደተወሰደ የተገለጸው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለመቋጨት ፓኪስታን ውስጥ በሚካሄደው ሁለተኛ ዙር ድርድር ላይ የአሜሪካን ልዑክ እንደሚመሩ ዋይት ሀውስ ካረጋገጠ በኋላ ነው።

    እስካሁን ኢራን በድርድሩ የመሳተፏን ነገር አላረጋገጠችም። የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን እንደገለጹት የአገሪቱ ባለሥልጣናት የአሜሪካ እገዳ በተጣለበት ሁኔታ ድርድር ውስጥ አንሳተፍም የሚል አቋም ይዘዋል።

    ትራምፕ መርከቡ መጠለፉን ባስታወቁበት ልጥፋቸው፤ “ዛሬ የኢራንን ባንዲራ ያነገበ፣ 900 ጫማ የሚጠጋ ቁመት ያለው እና ክብደቱ ከአውሮፕላን ተሸካሚ የጦር መርከብ ጋር የሚቀራረብ ቱስካ ተሰኘ መርከብ የጣልነውን የባሕር እግድ ለማለፍ ሞክሯል፤ ጥሩ አልሄደላቸውም” ሲሉ ጽፈዋል።

    አሜሪካ መርከቡ እንዲቆም ማስጠንቀቂያ ብትሰጥም እንዳልተቀበለው ገልጸዋል። “ስለዚህ ባሕር ኃይላችን ኢንጅን የሚገኝበት ክፍል ላይ በመምታት አቁሟቸዋል” ሲሉ የተወሰደውን እርምጃ ተናግረዋል።

    “ቱስካ ከዚህ ቀደም በነበረው የሕገ ወጥ ተግባር እንቅስቃሴ ምክንያት በአሜሪካ ግምጃ ቤት ማዕቀብ ተጥሎበታል። መርከቡ ላይ ሙሉ በሙሉ ቁጥጥር አለን፤ የተጫነውንም ነገር እያየን ነው” ብለዋል።

    የኢራን ጦር ዋና መስሪያ ቤት ኻታም አል አንቢያ ቃል አቀባይ ባወጡት መግለጫ አሜሪካ “ከኢራን የንግድ መርከቦች አንዱ በኦማን ባሕር ላይ እያለ ተኩስ በመክፈት፣ የጉዞ ስርዓቱን በማጥፋት እና መርከቡ ላይ በመውጣት የተኩስ አቁም ጥሰት ፈጽማለች” ብለዋል።

    ይህንን ያደረገችው ወታደሮቿን በማሰማራት እንደሆነ ጠቅሷል። “ኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጦር ኃይሎች በቅርቡ ምላሽ ይሰጣሉ፤ ለዚህ በአሜሪካ ባሕር ኃይል ተፈጸመ በትጥቅ የታገዘ የባሕር ላይ ውንብድና ድርጊት አጸፋውን ይመልሳሉ” ሲሉም ዝተዋል።