በምዕራብ ኦሮሚያ ስድስት ሰዎች መገደላቸው ተሰማ

ሰኞ አመሻሽ ላይ በምዕራብ ኦሮሚያ ቄለም ዞን በመከላከያ ሠራዊት አባላት ላይ ተወረወረ በተባለ የእጅ ቦንብ ቢያንስ የስድስት ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተነገረ።
በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው የአካባቢ ነዋሪዎችና ባለስልጣናት ቦንብ መወርወሩን ለቢቢሲ አረጋግጠው ፍንዳታውን ተከትሎ ያገጠመ ጉዳትን በተመለከተ የተለያየ ሃሳብ ሰጥተዋል።
የቄለም ዞን፣ የዞን ጽሕፈት ቤት ፐብሊሲቲ ኃላፊ አቶ ሐምዛ አብዱልቃድር አደጋው የደረሰው በዞናቸው አንጪሌ ወረዳ ሙጊ 02 ቀበሌ የሚባል ቦታ ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
ሰኞ አስር ሰዓት አካባቢ የኦነግ ሸኔ አባላት በመከላከያ ሠራዊት አባላት ላይ የደፈጣ ጥቃት መፈፀማቸውን የሚናገሩት ኃላፊው የወረወሩት ቦንቡ ፈንድቶ በአካባቢው የሚገኙ ስድስት ሰዎች መሞታቸውን አስረድተዋል።
የመከላከያ ሠራዊት አባላቱ ከጋምቤላ ወደ ሙጊ ቀበሌ በእግርና በመኪና እየተጓዙ የነበሩ መሆናቸውን የጠቀሱት ኃላፊው በቦንቡ ጉዳት የደረሰባቸው ግን የደፈጣ ጥቃቱን ሊፈጽሙ በነበሩት የኦነግ ሸኔ አባላት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
በአካባቢው ነዋሪ የሆኑ ሰዎች ለቢቢሲ እንደገለፁት ሰኞ እለት ቦንብ መወርወሩን እንደሚያውቁ ነገር ግን የቦንብ ፍንዳታውን ተከትሎ የመከላከያ ሠራዊት አባላት በወሰዱት የአፀፋ እርምጃ ሰባት ንፁሀን ተገለዋል ብለዋል።

















