አልጀሪያውያን ለስድስት አመታት ያላዩዋቸውን መሪ ይውረዱ እያሉ ነው

የ82 ዓመቱ የአልጄሪያው መሪ አብዱላዚዝ ቡተፍሊካ ለአምስተኛ ጊዜ ለስልጣን መወዳደራቸውን በመቃወም ዛሬ ከፍተኛ የተቃውሞ ሰልፍ ሊደረግ ነው።

ይህ ዜና ከተሰማበት ቀን አንስቶ ባለፈው ወር በእያንዳንዱ ቀን የተቃውሞ ሰልፍ ሲደረግ የነበረ ሲሆን ፕሬዝዳንቱ በስዊዘርላንድ ጄኔቫ ህክምና እየተከታተሉ ነው።

የተቃውሞ ሰልፉን የጠሩት የቃዋሚ ፓርቲ አቀንቃኞች ሰልፉን የ20 ሚሊየኖች ጉዞ የሚል ስያሜ ሰጥተውታል። አልጄሪያውያንም መንገዶችን እነዲያጥለቀልቁ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

እንደ ጎርጎሳውያኑ አቆጣጠር በ2014 በሀገሪቱ በተካሄደው ምርጫ አሸንፈው በ1999 የተረከቡትን ስልጣን ሲያስቀጥሉ በቴሌቭዥን መስኮት ብቅ ብለው መልዕክት ካስተላለፉ በኋላ የውሃ ሽታ ሆነው የቀሩት ፕሬዝዳንቱ እራሳቸውንም መርዳት ስለማይችሉ በጋሪ (wheelchair) እየተገፉ ነው የሚንቀሳቀሱት።

ፕሬዝዳንቱ ባስነበቡት ደብዳቤ በመጪው ሚያዚያ በሚካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ የሚያሸንፉ ከሆነ ብሔራዊ መድረክ በማቋቋም እሳቸው የማይሳተፉበት አዲስ የምርጫ ስርአት እንደሚዘረጉ ገልጸው ነበር።

ይህ ቃላቸው ግን አብዛኛውን አልጄሪያዊ ከማመጽ የሚያስቆመው ሆኖ አልተገኘም።

በዚህ ሳምንት ፕሬዝዳንቱ ሃገሪቱን ለመምራት አካላዊም ስነልቦናዊም ብቃት የላቸውም በማለት በርካታ የህግ ባለሙያዎች ተቃውሟቸውን ገልጸው ነበር።

ባለፈው ሳምንት ደግሞ በአዛውንት አንመራም ያሉ በርካታ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ወጣቶች በዋና ከተማዋ አልጀርስ ከባድ የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል።

30 በመቶ የሚሆነው የአልጄሪያ ወጣት ስራ የሌለው ሲሆን አብዛኛዎቹ ደግሞ ዕድሜያቸው ከ30 ዓመት በላይ ነው።

በፈረንጆቹ 1999 ወደ ስልጣን የመጡት ፕሬዝዳንት አብደላዚዝ ቡተፍሊካ በሃገሪቱ ተከስቶ የነበረውንና የ100 ሺ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈውን የእርስ በርስ ጦርነት ማስቆማቸው ይታወሳል።

ነገር ግን አልጄሪያውያን ለሰሩት ነገር ሁሉ እናመሰግናለን፤ አሁን ግን ይበቃዎታል እያሏቸው ይመስላል።