ፓኪስታን ክርስትያኗን አሲያ ቢቢን ከእስር ለቀቀች

አሲያ ቢቢ

የፎቶው ባለመብት, Handout

ፓኪስታናዊቷ ክርስቲያን በእስልምና ሃይማኖት ላይ ስድብ ሰንዝረሻል ተብላ ሞት ተፈርዶባት ስምንት ዓመት በእስር ቤት ካሳለፈች በኋላ ከእስር ነፃ መውጣቷን ጠበቃዋ ተናገሩ።

አንዳንዶች ከእስር ቤት እንደወጣች አውሮፕላን መሳፈሯን የዘገቡ ሲሆን መዳረሻዋ ግን ገና አልታወቀም።

የከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ ከአክራሪዎች ዘንድ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን መንግሥትም ፓኪስታንን ለቅቃ እንዳትሄድ አደርጋለሁ ብሎ ነበር።

ባለቤቷም ሕይወታቸው ስጋት ውስጥ መውደቁን ተናግሮ ሀገራት ጥገኝነት እንዲሰጧቸው ጠይቆ ነበር።

የአምስት ልጆች እናት የሆነችው አሲያ ቢቢ ሙልታን ከተማ ከሚገኘው እስር ቤት መለቀቋን ጠበቃዋ ሰይፍ ሙሎክ ተናግሯል።

ቢቢ አሲያ ኖሪን በመባልም የምትታወቅ ሲሆን በ2010 ነበር በእስልምና ሃይማኖት ላይ ስድብ ሰንዝረሻል በሚል የተከሰሰችው።

ከዚያ በኋላም በርካታ ሐገራት ጥገኝነት ለመስጠት ፈቃደኛ ሆነዋል።

ቢቢ እንደምትለቀቅና ሀገር ለቅቃ እንደምትወጣ ከተሰማ በኋላ በርካቶች የተቃውሞ ድምጻቸውን ሲያሰሙ ነበር። የፓኪስታን መንግሥት ከእስር ብትለቀቅም ከሀገር እንዳትወጣ እንዲከለከል በፍርድ ቤት እንደሚጠይቅ ተናግሮ ነበር።

በርካታ ተቃዋሚዎች የእስልምና ሃይማኖትን በመሳደብ የሚደርሰውን የሕግ ቅጣት የሚደግፉና አሲያ ቢቢ በስቅላት እንድትገደል የሚጠይቁ ናቸው።

የአንድ እስላማዊ ቡድን መሪ ሶስቱም የከፍተኛው ፍርድ ቤት ዳኞች "ሊገደሉ ይገባል" ሲል ተናግሯል።

በጠንካራ ተቃውሞው የሚታወቀው ቲ ሊፒ ፓርቲ የቢቢ መለቀቅ ከመንግሥት ጋር ያለን ስምምነት መፍረስ ምልክት ነው ብሎታል።

"መሪዎቹ ታማኝ እንዳልሆኑ አሳይተውናል" ብሏል የፓርቲው ቃል አቀባይ ኢጃዝ አሻሪፍ ለሮይተርስ።

በፓኪስታን ከ1990 ጀምሮ ቢያንስ 65 ሰዎች የእስልምና ሃይማኖት ላይ ስድብ ሰንዝረዋል በሚል ተገድለዋል።