15 ሕፃናትን በማቀዝቀዣ ውስጥ ጭኖ ወደ እንግሊዝ ለመግባት የሞከረ መኪና በቁጥጥር ስር ዋለ

ኒውሔቨን ወደብ

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, መኪናው የተያዘው በኒው ሔቨን ወደብ አካባቢ ነው።

21 ሰዎች ማቀዥቀዣ ባለው መኪና ውስጥ ተደብቀው ወደ እንግሊዝ ሊገቡ ሲሉ ተያዙ። በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል ዕድሜያቸው 12 ዓመት የሚሆናቸው ታዳጊዎች ይገኙበታል።

ወደ እንግሊዝ ሊገቡ ሲሉ የተያዙት እነዚህ ስደተኞች ቬትናማዊያን እንደሆኑ ተገምቷል። ስደተኞቹን የጫነው ባለማቀዝቀዣ መኪና የታሸገ ውሃ የጫነ ሲሆን ስደተኞቹም ከታሽገው ውሃ መካከል መገኘታቸው ነው የተዘገበው።

የድንበር ጠባቂዎች ዝርዝር መረጃ ባይሰጡም ምርመራ ግን መጀመሩ ታውቋል።

መኪናውን ያሽከረክር የነበረ ሮማኒያዊ ያለ ህጋዊ ፈቃድ ሰዎችን ወደ እንግሊዝ ለማስገባት በመሞከር ተብሎ በቁጥጥር ስር ውሏል።

የታሸገ ውሃ የጫነው መኪና ከፈረንሳይ የመጣ ሲሆን ሁሉም ስደተኞች ቬይትናማዊ ነን ያሉ 15 ህፃናትና 6 አዋቂ ሰዎችን አሳፍሯል።

ህፃናቱ ማህበራዊ ድጋፍ ወደ ሚያገኙበት ስፍራ ሲወሰዱ 18 አመት የሆነው ወጣትና 27 ዓመት የሚሆናት ሴት ከእንግሊዝ እንዲለቀቁ ተደርጓል።

4 አዋቂ ሰዎች ግን በስደተኞች ማቆያ ጣቢያ ሆነው ጉዳያቸው እየታየ ይገኛል።