ኦባማ፡ ሴቶች ከወንዶች የተሻሉ ናቸው

የቀድሞ ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ

የፎቶው ባለመብት, European Photopress Agency

ሁሉንም የዓለም ሃገራት የሚመሩት ሴቶች ቢሆኑ ኖሮ የተሻለ የህይወት ዘይቤ ይኖረን ነበረ ሲሉ የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ ተናገሩ።

በሲንጋፖር በተካሄደ መድረክ ላይ ሴቶች ፍጹም ባይሆኑም "ያለምንም ጥርጥር ከወንዶች የተሻሉ ናቸው" ብለዋል።

ኦባማ ዓለማችን ከሚያጋጥሟት የአብዛኞቹ ችግሮች መነሾ ያረጁ ወንዶች በተለይ ስልጣን ላይ ያሉት ናቸው ሲሉ ተደምጠዋል።

ኦባማ በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት ዓለም በሴት መሪዎች ብትመራ ምን ልትመስል እንደምትችል ያልሙ እንደነበረ ተናግረዋል።

"ሴቶች፣ አሁን እንድትረዱት የምፈልገው ፍጹም አይደላችሁም ግን ያለምንም ክርክር ከእኛ ትሻላላችሁ"ብለዋል።

"በጣም በእርግጠኝነት የምናገረው ሁሉም ሃገር ለሁለት ዓመታት በሴቶች ቢመራ፤ የተሻለ የኑሮ ዘይቤ እና ደረጃ ይኖረናል። በሁሉም ዘርፍ ለውጥ እንመለከታለን" ብለዋል።

ወደፊት ወደ ፖለቲካ መድረኩ የመመለስ ዕቅድ ካላቸው የተጠየቁት የቀድሞ ፕሬዝደንት፤ ይልቁንም ለሌሎች የፖለቲካ መሪዎች ቦታ መልቀቅ እንደሚያሳምናቸው አስረድተዋል።

"ዓለምን በትኩረት ከተመለከትናት የችግሮቿ ምንጮች ብዙ ጊዜ ያረጁ ስልጣን ያለመልቀቅ አባዜ ያላቸው እምቢተኛ ወንዶች ናቸው" ብለዋል።

"የፖለቲካ መሪዎች ማወቅ ያለባቸው እና ሁሌም እራሳቸውን ማስታወስ የሚገባቸው፤ እዛ ቦታ ላይ ተሹመው የተቀመጡት ሥራ ለማከናወን ነው። የህይወት ዘመናቸውን ለመጨረስ አይደለም እዛ የተቀመጡት።"

ኦባማ አሜሪካን ለሁለት የስልጣን ዘመናት ከእአአ 2009 እስከ 2017 መምራታቸው ይታወሳል።

ከዋይት ሃውስ ከወጡ በኋላ ከባለቤታቸው ሚሼል ኦባማ ጋር ባቋቋሙት ፋውንዴሽን በመላው ዓለም የሚገኙ ወጣት መሪዎችን እየደገፉ ይገኛሉ።