ካንታስ፡ ያለእረፍት ከአስራ ዘጠኝ ሰዓት በላይ የበረሩ መንገደኞች ምርመራ ተደረገላቸው

የአውስትራሊያ የአየር መንገድ ካንታስ ያለምንም እረፍት ያለማቋረጥ ረዥም ሰዓት ያደረገው በረራ ተጠናቋል።

የምርምር አካል የሆነው ይህ በረራ ረዥም በረራዎች በመንገደኞች፣ በፓይለቶችና በአውሮፕላን አስተናጋጆች ላይ የሚያደርሰው ተፅእኖን በጥልቀት የሚያይ ይሆናል።

ቦይንግ 787-9 አውሮፕላን አርባ ዘጠኝ መንገደኞችን አሳፍሮ የነበረ ሲሆን አስራ ዘጠኝ ሰዓታት ከአስራ ስድስት ደቂቃ በሯል።

መነሻውን ኒውዮርክ አድርጎ የአውስትራሊያ መዲና ሲድኒ ለመድረስም የ16 ሺህ ሁለት መቶ ኪሎ ሜትር ርቀትን በሯል።

አየር መንገዱ በሚቀጥለው ከለንደን ወደ ሲድኒም የሚደረግ በረራንም አቅዷል።

እነዚህ በረራዎች ካንታስ በተያዘው የአውሮፓያውያን ዓመት የሚጀምረውን የበረራ መስመር የሚወስን ይሆናል።

በረራዎቹም ከተሳኩ በሚቀጥሉት አራትና አምስት ዓመታት ውስጥ ሙሉ በሙሉ በረራ የሚጀመር ይሆናል።

እስካሁን ባለው መረጃ መንገደኞችንና እቃ ጭኖ ያለምንም እረፍት ይህን ያህል ሰዓት መብረር የቻለ አውሮፕላን እንደሌለ ሮይተርስ ዘግቧል።

ለዚህም በረራ ቅድመ ዝግጅቶች የተደረጉ ሲሆን፤ አውሮፕላኑ የነዳጅ እጥረት እንዳያጋጥመውና፤ ነዳጅ ለመሙላትም እንዳይቆም ሙሉ በሙሉ ነዳጅ ከመሞላት በተጨማሪ፤ የተወሰኑ የመንገደኛ ሻንጣዎችን ብቻ ጭኖ ሌላ ምንም አይነት እቃ እንዳይጭን እንደተደረገ ተገልጿል።

መንገደኞቹ ከተሳፈሩበት እስኪወርዱበት ባሉት ሰዓታት ውስጥ በጥብቅ ቁጥጥር ስር የነበሩ ሲሆን፤ አውሮፕላኑ ላይ እንደተሳፈሩም ወዲያው እንዳይተኙም ተደርጓል።

ከስድስት ሰዓት በኋላም ከፍተኛ የካርቦሃይድሬት መጠን ያለው ምግብ እንዲመገቡ የተደረገ ሲሆን፤ በአውሮፕላኑ ውስጥ ያለው የብርሃን መጠን ተቀንሶ እንዲተኙ ተበረታትተዋል።

በአውሮፕላኑ ውስጥም የፓይለቶችን የአዕምሮ እንቅስቃሴ፤ የእንቅልፍን ሁኔታ የሚቆጣጠረውን የሜላቶንን ሆርሞን መጠን እንዲሁም ካላቸው የንቃት ሁኔታም ጋር ተያይዞ ክትትሎች ነበሩ ተብሏል።

መንገደኞቹ የተለያዩ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርጉ የነበረ ሲሆን በተለይም የተለያየ መልክአ ምድርን በሚያልፉበት ጊዜ ሰውነታቸው ላይ የሚመጣውንም ለውጥ ለማየት ተሞክሯል።

በቅርቡ ረዥም ሰዓትን የሚበሩ አየር መንገዶች ቁጥራቸው እየጨመሩ ሲሆን ለምሳሌም የሲንጋፖር አየር መንገድ ከሲንጋፖር ወደ ኒውዮርክ የአስራ ዘጠኝ ሰዓታት በረራ ባለፈው ዓመት ጀምሯል። በአሁኑም ሰዓት ረዥሙ በረራ የሚባለው ይኸው ነው።

ባለፈው ዓመትም እንዲሁ ኳንታስ የ17 ሰዓታት በረራ ከፐርዝ ወደ ለንደን የጀመረ ሲሆን፤ የኳታር አየር መንገድም በተመሳሳይ ከኦክላንድ ወደ ዶሃ የ17.5 ሰዓታት ጉዞ ጀምሯል።