ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በእንግሊዝ የክብር ማስታወሻ ምልክቶች ተቀመጠላቸው

የፎቶው ባለመብት, Bath In Time
ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንግሊዝ ውስጥ 'ባዝ' ተብሎ በሚታወቀው ቦታ ለነበራቸው ቆይታ እና 'ዌስቶን ሱፐር ሜር' የተባለውን ቦታ የጎበኙበትን ወቅት ለመዘከር በማሰብ የክብር ማስታወሻ የሆኑ ሁለት ሰማያዊ ምልክቶች በስማቸው ተቀመጠላቸው።
የጣልያን ጦር ኢትዮጵያን በተቆጣጠረበት ወቅት ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ እ.አ.አ. ከ1936 እስከ 1940 ድረስ በስደት ኑሯቸውን በእንግሊዟ ባዝ አድርገው እንደነበር ይታወሳል።
በእንግሊዝ ቆይታቸውም ዌስቶን ሱፐር ሜር ወደ ሚባል ቦታ በመሄድ በውሃ ዋና ይዝናኑ እንደነበር ይነገራል።
'ብሉ ፕሌክ' በመባል የሚታወቀው ይህ የክብር ማስታወሻ እንግሊዝ ውስጥ የማይረሳ ሥራ የሠሩ ሰዎችን ለማሰብና ትልቅ ታሪካዊ ክስተቶችን ለማስታወስ ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች የሚቀመጥ ሰማያዊ ምልከት ነው።

የዌስቶን ሲቪክ ማህበር ባዘጋጀው የክብር ምልክቱን የማኖር ሥነ-ሥርዓት ላይ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል ሚካኤል መኮንን የተገኙ ሲሆን ምልክቶቹንም በይፋ ከፍተው መርቀዋል።

የፎቶው ባለመብት, Bath In Time
''ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ በእንግሊዝ በነበራቸው ቆይታ ቦታዎቹን እንደ እራሳቸው ቤት ቆጥረው ይኖሩ ስለነበር እሱን ለማስታወስና ለእርሳቸው ክብር ለመስጠት ነው ይህንን ያደረግነው'' ብለዋል ከአዘጋጆቹ መካከል አንዱ የሆኑት ዶክተር ሾን ሶበርስ።
በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የዌስቶን ሱፐር ሜር ከተማ አስተዳዳሪ የሆኑት ማልኮም ኒኮልሰን ደግሞ ''ከተማችን ከኢትዮጵያ ንጉሣውያን ቤተሰቦች ጋር ስሟ በመያያዙ ትልቅ ኩራት ይሰማናል'' ሲሉ ተደምጠዋል።












