እንደ ግለሰብ የኢትዮጵያዊነት ግዴታን እንዴት መወጣት ይቻላል?

ይህ ጥያቄ ምናልባት እ.አ.አ በ1961 የዚያን ጊዜው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩትን የጆን ኤፍ ኬኔዲን የመጀመሪያ ንግግር ያስታውስ ይሆናል። እሱም "ስለዚህ ውድ [የሃገሬ] ሰዎች ሃገሬ ለእኔ ምን ታደርግልኛለች ብላችሁ ሳይሆን ለሃገሬ ምን ላድርግላት ብላችሁ ጠይቁ" ያሉትን ነው።
እንደ ግለሰብ የዜግነት ግዴታን እንዴት መወጣት ይችላል?
ቀለል ባለ መልኩ 'ሳውዝ ሳውዝ ዊሜን' በሚል ስያሜ በናይሮቢ ከተማ በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ከተለያዩ የዓለማችን ደቡባዊ ክፍል ከተወጣጡ 8 ሴቶች መካከል ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ነበሩ።
ሃና ፀጋዬ ለሃገሯ አልፎም ለአካባቢዋ የተሻሉ ነገሮችን ለመሥራት እየጣረች ያለች ጠንካራ ሴት ነሽ ተብላ ወደ ኬንያ ተጋብዛ ነበር። ሃገሯን ወክላ የ'ሳውዝ ሳውዝ ዊሜን ሌጋሲ ቶክስ' የተባለው የውይይት መድረክ መክፈቻ ላይ ተገኝታ በአሁን ሰዓት እየሠራች ያለቻቸውንና ወደፊት ደግሞ ለመሥራት የምታቅዳቸውንም አካፍላለች።
"መንግሥት ምን ይሥራ ብቻ ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ምን ዓይነት አስተዋጽዖ ማድረግ አለብን ብለን ማሰብ ያስፈልጋል" የምትለው ሃና ወደፊት በኢትዮጵያ የገጠር ክፍሎች ውስጥ የሚሰጠውን የትምህርት ደረጃ ከፍ የማድረግ ሕልም እንዳላት ትናገራለች።
አክላም "በግለሰብ ደረጃ በተለያየ ዘርፍ እየተሰማራን የዜግነት ግዴታችንን የምንወጣበትንና የሃገራችንን የተለያዩ ችግሮች የምንቀርፍበትን መንገድ መወያየትና መፍትሔ የማምጣት ግደታ አለብን" ትላለች።
በአሁን ሰዓት ጠንክራ እየሠራች ያለችው የኢትዮጵያን የመድሃኒት ዘርፍ ለማሻሻል ሲሆን ቢኒፋርማ ፒ.ኤል.ሲ የተሰኘ የመድሃኒት ማምረቻ አቋቁማ በዓመት ጊዜ ውስጥ ሥራ ለመጀመር ከመንግሥት ጋር ንግግር ላይ እንደሆነች ትናገራለች።
ሃና የቢኒ ፒ.ኤል.ሲ የሥራ ሂደት ኃላፊ ስትሆን ያላትን ልምድ ተመርኩዛ "ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡት መድሃኒቶች አብዛኛውን ጊዜ ደረጃቸውን የጠበቁ አይደሉም። ጥሩ መድሃኒት ለማግኘት ደግሞ ገንዘብ ያስፈልጋል። ይህ ደግሞ ትክክል ነው ብዬ አላምንም ምክንያቱም ሁሉም ግለሰብ ደረጃውን የጠበቀ መድሃኒት የማግኘት መብት አለው" ትላለች።

ሌላኛዋ ተሳታፊ ሳምራዊት ሞገስ የአስጎብኚ ድርጅት ባለቤት ናት። ከዚህ በተጨማሪ በእርሻ ተሰማርታለች። አበቦችና የአተር ዓይነቶችን በማምረት ወደ ሆላንድ በመላክ ትተዳደራለች። ሳምራዊት በ'ሳውዝ ሳውዝ ዊሜን' ተገኝታ ተሞክሮዋን እንድታካፍል የተደረገው ተቀጣሪ ሆነው በእርሷ ሥር የሚሠሩት አብዛኛዎቹ ሴቶች በመሆናቸው ነው።
ሳምራዊት ከምታስተዳድራቸው 600 ሠራተኞች 90 በመቶዎቹ ሴቶች ናቸው። ለምን ስትባል "ለሴቶች ያለነው ሴቶች ነን" ብላ እንደምታምን ትናገራለች።
ሠራተኞቿ በሚወልዱበት ጊዜ የነበራቸውን ሥራ እንዲያቆሙ ወይም ደግሞ ወልደው ሲመለሱ እንደ አዲስ እንዲጀመሩ መገደዳቸውን ተመልክታ ይህንን እውነታ ለመቀየር ስትል እያጠቡ ወደ ሥራ ገበታቸው እንደሚላለሱ በመፍቀድ ኑሯቸው ሳይጎሳቆል መቀጠል የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸቷን ትገልጻለች።
"በአካባቢያችን ያሉትን ክፍተቶች ለይቶ በማወቅ ለመሸፈን መጣራችን አስፈላጊ ነው። እኔ ኢትዮጵያን ከልብሴ በተጨማሪ በሥራዬም ማስጠራት እፈልጋለሁ" የምትለው ሳምራዊት በማንኛውም ዘርፍ የተሰማራ ሰው የአቅሙን የመሥራቱን ጠቀሜታ ታጎላለች።

አክላም "ሴቶች ስንደጋገፍ ብዙ ነገሮችን ማሳካት እንደምንችል አምናለሁ። ሴት ፕሬዚዳንቷን ኢትዮጵያ ስትሾም ውጪ የምትማረው ልጄ ማመን አቅቷት ደስታዋን ገልፃልኝ ነበር። ሆኖም ግን ሴት ብቻ ስለሆንን መሆን የለበትም፤ የሥራ ዕድል የሚሰጠን ለሥራው መሆን አለበት" በማለት ለወንዶችም ሆነ ለሴቶች እኩል ዕድል የመስጠቱን አስፈላጊነት ታጠብቃለች።
የዚህ 'ሳውዝ ሳውዝ ዊሜን' የውይይት መድረክ መስራች ዛይና 'አፍሪካ' ከኬንያ ስትወጣ የነበራት ሕልም ከዓለም የተለያዩ ክፍል የተወጣጡ ሴቶችን በአንድ ላይ በማገናኘት ሁሉም የሚማማርበትን መድረክ መፍጠር ነበር።
ዛይናም ሃሳቡ ከተጠነሰስም ከዓመታት በኋላ መጀመሪያውን የውይይት መድረክ ሁለት ኢትጵያውያንን በመጋበዝ ለማስጀመር ችላለች።
ትኩረቱን ለምን ከደቡባዊ የዓለማችን ክፍል በመጡ ሴቶች ላይ አተኮረ? ብለን ስንጠይቃት ዛይና "የሌላው ዓለም ክፍል ብዙ ዕድሎችና አማራጮች፣ የመማሪያና የመማማሪያ መድረኮችም በነፃም ሆነ ተከፍሎበት አሏቸው። ከዓለም የተለያዩ የደቡብ ክፍሎች የሚወጡ ሴቶች ግን የሚገናኙበትም ሆነ የሚተዋወቁበት አጋጣሚ ለማግኘት ከባድም አናሳም ነው። ለዚህ ነው 'ሳውዝ ሳውዝ ዊሜን' አስፈላጊ የሚሆነው" ትላለች።













