መምህራንን ተክቶ ያስተማረው ወታደር እየተወደሰ ነው

ጃይረስ ሙሊማ

የፎቶው ባለመብት, Education Development Trus

የምስሉ መግለጫ, ጃይረስ ሙሊማ ሒሳብ ሲያስተምር

ኬንያ ውስጥ በአንድ ትምህርት ቤት የሚያስተምሩ መምህራን በስራ ገበታቸው ባለመገኘታቸው በአካባቢው የነበረ አንድ ፖሊስ ወደ ክፍል ውስጥ በመግባት ሲያስተምር የሚያሳየው ምስል የሃገሬውን ሰዎች በእጅጉ አስገርሟል።

ኬንያውያንም ጀግናችን ነህ እያሉ በማህበራዊ ሚዲያዎች እያሞካሹት ነው። ምስሉን በፌስቡክ ለህዝብ ይፋ ያደረገው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እንደገለጸው ጃይረስ ሙሊማ የተባለው የፖሊስ ሃይል አባል በኢትዮጵያ እና ኬንያ ድንበር ላይ በሚገኝ ፎሮሌ በተባለ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ሂሳብ ሲያስተምር ነበር።

የድርጅቱ ሃላፊ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ አካባቢው የደህንነት ስጋት አለበት በማለት መምህራኑ በስራ ገበታቸው ላይ እየተገኙ አይደለም። በዚህም ምክንያት ተማሪዎች በክፍል ውስጥ ያለምንም ትምህርት ተቀምጠው እንዲውሉ ተገደዋል።

''ከትምህርት ቤቱ ሃላፊ ፍቃድ ካገኘ በኋላ ጃይረስ ሙሊማ አምስተኛ ክፍል በመግባት የሂሳብ ትምህርት ሲያስተምር ነበር'' ብለዋል ሃላፊው።

ትምህርት ቤቱ በሚገኝበት አካባቢ በተለያዩ ጊዜያት ሽፍታዎች ድንገተኛ ጥቃት የሚያደርሱ ሲሆን ጥቂት ለማይባሉ ሰዎችም ህይወት ማለፍ ምክንያት ሆኗል።

በርካታ ኬንያውያን ጃይረስ ሙሊማ የሰራው ስራ እጅግ የሚያኮራና ለሁላችንም ምሳሌ መሆን ያለበት ነገር ነው በማለት በማህበራዊ ሚዲያዎች እየተቀባበሉት ነው።

አንድ ኬንያዊ ያልተዘመረለት ጀግና ሲል አሞካሽቶታል።

ጃይረስ ሙሊማ በድንበር አካባቢ የተከሰተውን አለመረጋጋት ለመቆጣጠር ከተመደቡ የጸጥታ ሃይሎች አንዱ ሲሆን በትምህርት ቤቱ አካባቢ ጥበቃ ሲያደርግም ነበር ተብሏል።

ጃይረስ የሂሳብ ትምህርት ሲያስተምር በክፍሉ ውስጥ የነበሩት ወደ ትምህርት ቤት ለመምጣት ድፍረት የነበራቸው ጥቂት ሴት ተማሪዎች ብቻ ነበሩ ተብሏል።