ደቡብ አፍሪካ በናይጄሪያ የሚገኘውን ኤምባሲዋን ዘጋች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ደቡብ አፍሪካ በናይጀሪያ የሚገኘውን ኢምባሲዋን መዝጋቷ ተሰምቷል። በደቡብ አፍሪካ ናይጄሪያዊያን የሚደርስባቸውን ጥቃት ተከትሎ ናይጄሪያውያን በአቡጃ የአጸፋ እርምጃ ይወስዳሉ በሚል ስጋት ነው በጊዜያዊነት ኤምባሲው የተዘጋው።
በንግድ እንቅስቃሴዋ በምትታወቀው ጆሃንስበርግ ከእሁድ እስከ ረቡዕ በተካሄደው ጥቃትና ዘረፋ በርካታ ሱቆች መዘረፋቸው ተነግሯል። ይህንን ተከትሎም 420 ሰዎች ታስረዋል።
የደቡብ አፍሪካ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ናለዲ ፓንዶር ክስተቱን "አሳፋሪ" ብለውታል።
"በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ዜጎች ላይ በደረሰው ጥቃትና ዘረፋ መንግሥታችን ከልብ ተጸጽቷል" በማለት አክለዋል በመግለጫቸው። በመሆኑም ዲፕሎማቶች ላይ በሚደርሰው ማስፈራሪያ ምክንያት በናይጄሪያ አቡጃ የሚገኘውን ከፍተኛ ኮሚሽንና የሌጎስ ሚሲዮን እንዲዘጋ ትዕዛዝ ሰጥተዋል።
ናይጄሪያውያን ተገድለዋልን?
በማህበራዊ ሚዲያ የሚዘዋወሩት ተንቀሳቃሽ ምስሎች ናይጄሪያውያን መገደላቸውን የሚገልጹ ሲሆን ችግሩን አባብሶታል። ይህንን ተከትሎ ማክሰኞና ረቡዕ በበርካታ የናይጄሪያ ከተሞች የደቡብ አፍሪካውያን የቢዝነስ ሱቆች ጉዳት ደርሶባቸዋል። የደቡብ አፍሪካው ግዙፉ የቴሌኮም ኩባንያ ኤም ቲ ኤንም በክስተቱ በመስጋት ተዘግቷል።
ሁለት ታዋቂ የናይጀሪያ ዘፋኞችም (ቡርና ቦይ እና ቲዋ ሳቬጅ) የደቡብ አፍሪካ ሥራቸውን ማቋረጣቸውን ተናግረዋል።
በግርግሩ ቢያንስ ሁለት የውጭ ሀሃገር ዜጎችን ጨምሮ 10 ሰዎች የሞቱ ሲሆን ከሟቾቹ መካከል ናይጄሪያውያን ስለመኖራቸው ግን የተረጋገጠ ነገር የለም። ረቡዕ ዕለት የናይጄሪያ የዉጭ ጉዳይ ሚንስትር ጂኦፍሪ ኦንያማ "በናይጄሪያውያን ላይ ብዙ ነገር ይባላል። ከህንጻ እንደተወረወሩና እንደተቃጠሉም ይነገራል። ጉዳዩ ግን ይህ አይደለም" ብለዋል።
ናይጀሪያውያን ስለመገደላቸው መረጃ ባይኖረንም እንደመንግሥት ግን የናይጄሪያውያን ንብረት ኢላማ ስለመደረጉ እርግጠኞች ነን ብለዋል ሚንስትሩ።
በጥፋቱ ፕሬዝዳንት ቡሃሪ ሳይቀሩ መጨነቃቸውን በመግለጽ ናይጄሪያውያን በደቡብ አፍሪካውያን የቢዝነስ ተቋማት ላይ የሚያደርጉትን የበቀል እርምጃ እንዲያቆሙም አሳስበዋል።
የናይጄሪያ መንግሥት ለምን መናገር ፈለገ?
በቅርቡ በኬፕታውን የሚካሄደውን የአለም የኢኮኖሚ ፎረም የናይጀሪያ መንግሥት ግርግሩን በመቃወም ሳይሳተፍ ቀርቷል። የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ "ለዚህ ጉዳይ ቢያንስ የሞራል ግዴታችንን ልንወጣ ይገባል" በማለት የጉባኤውን መቅረት ገልጸውታል።
ፕሬዝዳንቱም በግርግሩ የተሰማችውን መከፋት ለመግለጽ ወደ ደቡብ አፍሪካ ልዑክ ልከዋል። ናይጀሪያውያን መንግሥት በውጭ ሃገር ለሚደርሰው ችግር የሚያሳየውን ፍጥነት በሃገር ውስጥ ሲሆን ግን አይደግመውም ብለዋል።
ሌሎች አፍሪካውያንስ ምን አሉ?
ትናንት በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ሁለተኛዋ ትልቅ ከተማ የተቃውሞ ሰልፍ ተደርጓል። በመዲናዋ ኪንሻሳም አነስተኛ ሰልፍ ተካሂዷል።
የታንዛኒያ አውሮፕላንም ወደ ጆሃንስበርግ እንደይበር የታንዛኒያ የትራንስፖርት ሚንስትር አስታውቋል።
የማዳጋስካር እግር ኳስ ፌደሬሽንም ቅዳሜ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ለሚያደርጉት የወዳጅነት ጨዋታ ቡድኑን እንደማይልክ ተናግሯል።
ረቡዕ ዕለት በዛምቢያ ዋና ከተማ ሉሳካ ተማሪዎች የደቡብ አፍሪካውያንን ሱቆች አዘግተዋል።
የአፍሪካ ኅብረትም ጥፋቱን የሚያወግዝ መግለጫ አውጥቷል።
ዘረፋውና ጥቃቱን በምን ተነሳ?
ጥቃቱ የደረሰው የጭነት መኪና አሽከርካሪዎች የውጭ ሃገር ሰዎች መቀጠር የለባቸውም በማለት አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ ነው። አድማ ከማድረግም በተጨማሪ መንገዶችን በመዝጋት የውጭ ሃገር አሽከርካሪዎችን መደብደብ ሲጀምሩ ጥቃቱ በብዙ ቦታዎች ተቀጣጠለ።
ምክንያቱም በርካታ ደቡብ አፍሪካውያን ሥራ አልባ የሆኑት በውጭ ዜጎች ምክንያት እንደሆነ ያስባሉ። በአሁኑ ወቅት የደቡብ አፍሪካ የሥራ አጥነት መጠን 28 በመቶ እንደሆነ ይነገራል። አሃዙ ከ11 ዓመታት በኋላ ከፍተኛው እንደሆነ ተገልጿል።














