'ኢራን፤ ትልቅ ስህተት ፈፅመሻል!' ዶናልድ ትራምፕ ለኢራን ያስተላለፉት መልዕክት

የፎቶው ባለመብት, AFP
ኢራን የአሜሪካን ወታደራዊ ድሮን [ሰው አልባ አውሮፕላን] መትታ መጣሏ 'እጅግ በጣም ትልቅ ስህተት ነው' ሲሉ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ተደምጠዋል።
'መቼም ከሰው ስህተት አይጠፋምና' ኢራን ተሳስታ ይሆናል ድሮኑን የመታችውም ብለዋል ትራምፕ። «እኔ በበኩሌ አራን ከልቧ ሆና ይህንን ታደርጋለች ብዬ አላምንም» ነበር ከጋዜጠኞች ለቀረለበላቸው ጥያቄ የሰጡት ምላሽ።
ኢራን ሰው አልባው አውሮፕላን 'ድንበሬን ጥሶ ገብቷል' ብትልም አሜሪካ ግን ወቀሳው ውሃ አያነሳም ባይ ናት።
ሁለቱ ሃገራት ጠብ ያለሽ በዳቦ ላይ ናቸው።
ኢራን 'አሜሪካ ድንበሬን ጥሳ ገብታለች፤ ድሮኗ የመጣችው ለስለላ ነው' የሚል ክስ አሰናድታ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ልትሄድ እንደሆነ የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጃቫድ ዛሪፍ አሳውቀዋል።
በነጩ ቤተ-መንግሥታቸው ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ የነበሩት ትራምፕ 'ድሮኗ በዓለም አቀፍ ከባቢ ላይ እንጂ የአራን ድንበርን አልጣሰችም» ብለዋል።
«እኔ በበኩሌ ስህተት ነው 'ሚመስለኝ። እንደውም ሳስበው አንድ ግለሰብ ነው በስህተት ድሮኗ እንድትመታ ያዘዘው። አንድ ደደብ የሆነ ሰው ይሆናል ይህን የፈፀመው።»
የሩስያው ፕሬዝደንት ቭላዲሚር ፑቲን በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ጦርነት ቢከሰት መዘዙ የከፋ ነው ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
የተባባሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉዌቴሬዝም ሁለቱ ሃገራት ረጋ ብለው እንዲያስቡ መልዕክት ልከዋል።
የአሜሪካ ሕዝብ እንደራሴዎች አፈ-ጉባዔ ዴሞክራቷ ናንሲ ፔሎሲ 'አሜሪካ ለጦርነት ያላት አምሮት ቀንሷል' ሲሉ የቀጣዩ ምርጫ ተፎካካሪ የሆኑት የቀድሞው ምክትል ፕሬዝደንት ጆ ባይደን 'በሁለቱ ሃገራት መካከል ያለው ውጥረት የትራምፕ 'ግብዝነት' ውጤት ነው ሲሉ ፕሬዝደንቱን ወርፈዋል።
ሳዑዲ አራቢያ ለአሜሪካ የወገነች ትመስላለች፤ 'የኢራን ድርጊት ተቀባይነት የለውም' ባይም ነች።
የሁለቱን ሃገራት ውጥረት ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ በ15 በመቶ ጨምሯል።












