የሶማሌ ላንድ መስጊዶች ድምፅ እንዲቀንሱ ተጠየቁ

የመስጊድ ሚናር

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የራስ ገዝ አስተዳዳር በሆነችው ሶማሌ ላንድ የሚገኙ መስጊዶች ሌሊቱን ሙሉ በሚያካሂዱት የፀሎት ሥነ ሥርዓት ድምፅ እንዲቀንሱ አሊያም ሙሉ በሙሉ እንዲያጠፉ ማስጠንቀቂያ ተሰጣቸው።

የሃይማኖት ጉዳዮች ጀኔራል ዳይሬክተር አዳን አበዲላሂ አባዳሌ ለቢቢሲ እንደገለፁት ኢማሞችና የመስጊዶቹ ባለሥልጣናት ጎረቤቶቻቸውን በማክበር በተለይ ግዴታ ያልሆነውንና ከእኩለ ሌሊት በኋላ የሚደረገውን የታሃጁድ ፀሎት እንዲተዉ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል ብለዋል።

ታሃጁድ ከኢንሻ ሶላት በኋላ የሚደረግ የፀሎት ሥነ ስርዓት ነው።

በመስጊዶቹ አቅራቢያ የሚኖሩ ሰዎች ከመስጊዶቹ ከተገጠሙት የድምፅ ማጉያ የሚወጡት ድምፆች ከእንቅልፋቸው እንደሚረብሻቸው ቅሬታቸውን እቅርበዋል። በተለይ ድምፁ ለአዛውንቶችና በህመም ላይ ላሉ ሰዎች ከባድ ነው ብለዋል።

ሌሎች ደግሞ መስጊዶች አዛን በማድረግ የእምነቱን ተከታዮች ማንቃትና መጥራት መብታቸው ነው ሲሉ ይከራከራሉ። አክለውም መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገባ አስጠንቅቀዋል።

በሶማሌ ላንድ የሚኖሩት አብዛኞቹ የእስልምና እምነት ተከታዮች ሲሆኑ ግዛቷ ራሷን የምታስተዳድር ቢሆንም በዓለም አቀፍ ደረጃ አንደ አንድ ራሷን እንደቻለች አገር እውቅና አልተሰጣትም።