አይስላንድ አንድ ተማሪ ብቻ የቀረውን ትምህርት ቤት ልትዘጋ ነው

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በሃገረ አይስላንድ ግሪምሲይ በምትሰኝ ከተማ የሚገኝ ትምህርት ቤት አንድ ተማሪ ብቻ ስለቀረው ሊዘጋ ስለመሆኑ ተነገረ።
በአነስተኛ የደሴት ከተማ ላይ የሚገኘው ትምህርት ቤቱ፤ እአአ 2001 ላይ 14 ተማሪዎች ነበሩት። ይሁን እንጂ ከአንድ ዓመት በፊት የትምህርት ቤቱ የተማሪዎች ቁጥር ወደ 4 ዝቅ ብሎ ነበር። የአንድ ቤተሰብ አባላት ደሴቷን ለቀው ወደ ሌላ ሥፍራ ለመዘዋወር መወሰናቸው በትምህርት ቤቱ አንድ ተማሪ ብቻ እንዲቀር ምክንያት ሆኗል።
የቀረው አንድ ተማሪ በቀጣዩ የትምህርት ዓመት ወደ ዘጠነኛ ክፍል ይዘዋወር ነበር። ነገረ ግን ላልተወሰነ ጊዜ ትምህርት ቤቱ ዝግ ሆኖ ይቆያል ተብሏል።
''ትምህርት ቤቱ ከተገነባ ከ40 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል። ለአካባቢው ማኅብረሰብም ዘረፈ ብዙ አገልግሎቶችን ሲሰጥ ቆይቷል። የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የህጻናት መዋያ፣ የሃኪሞች ቢሮ ሆኖ አገልግሏል። ትምህርት ቤቱ ተዘግቶ ይቀራል ብዬ አላስብም።'' በማለት የትምህርት ቤቱ ርዕሰ መምህርት ካረን ኖት ቪኩዳጉር ለተሰኝ ለአካባቢው ጋዜጣ ተናግረዋል።
ግሪምሲይ ለተሰኘችው ይህች የደሴት ከተማ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የአሳ ምርት የነበረ ሲሆን በአካባቢው የነበሩ አሳ አምራቾች ንግድ አልሳካ ቢላቸው አካባቢውን ለቀው ወጥተዋል። ጎብኚዎችም ቢሆኑ ይህችን በረዷማ አካባቢ የሚጎበኙት በሞቃታማ ወራት ብቻ ነው።
ምንም እንኳ የአይስላንድ መንግሥት ተደራሽ ወዳልሆኑት ግሪምሲይ እና ሌሎች ሥፍራዎች በድጎማ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ቢያቀርብም ይህ ነው የሚባል ፋይዳ ለአካባቢው እንዳላመጣ ይታመናል።














