በጥዋት ከእንቅልፍ መነሳት ውጤታማ ያደርጋል?

የፎቶው ባለመብት, Media for Medical
ሁላችንም በተለምዶ የምናደርገው አልያም ብዙ ሰዎች የሚነግሩን በጊዜ ተኝቶ በጠዋት መነሳት ውጤታማ እንደሚያደርግ ነው።
የታዋቂው የስልክ አምራች አፕል ዋና ስራ አስኪያጅ ቲም ኩክ ከእንቅልፉ ሌሊት 9፡45 ሲሆን የሚነሳው፤ የፊያት መኪና አምራች ድርጀት ሃላፊ ደግሞ 9፡30 ነው ከአልጋው የሚወርደው።
ነገር ግን አንዳንድ ውጤታማ የሆኑ ሰዎች በጠዋት መነሳት ስለሚወዱ፤ ሁሉም ውጤታማ ሰዎች ይህንን ይከተላሉ ማለት አይደለም።
ምናልባትም ልዩነቱን ሊፈጥር የሚችለው በጠዋት ተነስቶ እንቅስቃሴ ማድረግ፣ የቀኑን ውሎ አስቀድሞ ማቀድ፣ ቁርስ በትክክል መመገብና በመሳሰሉት ሊሆን ይችላል።
በቅርቡ የተሰራ አንድ ጥናት እንሚያሳየው ግን 50 በመቶ የሚሆነው የዓለማችን ህዝብ በጠዋት መነሳትም በጊዜ መተኛትም ላይ እምብዛም ሲሆን በሁለቱ መካከል የሚቀመጥ ነው።
ከአራት ሰዎች አንዱ በጠዋት መነሳት የሚወድ ሲሆን ከሌሎች አራት ሰዎች መካከል ደግሙ አንዱ አምሽቶ መተኛት የሚወድ ነው።
ጥናቱ እንደጠቆመው በጠዋት የሚነሱ ሰዎችና አምሽተው በሚተኙ ሰዎች መካከል ያለው ልዩነት በቀኝ የአንጎላቸው ክፍል ውስጥ ያለው እንቅስቃሴ ነው።
በጠዋት የሚነሱት ነገሮችን ማሰላሰል የሚችሉና ተባባሪዎች ሲሆኑ አምሽተው የሚተኙት ደግሞ ከፍ ያለ የፈጠራ ችሎታና ግለኝነት ያጠቃቸዋል።
በጠዋት የሚነሱ ሰዎች ለራሳቸው ከፍ ያለ ግብ ማስቀመጥ የሚወዱና ስለወደፊቱ አብዝተው የሚጨነቁ ናቸው።
በዚህ ዙሪያ የተሰሩ ብዜ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት የጠዋት ሰዎች ቶሎ የማይሸነፉ፣ ነገሮችን በራሳቸው የሚያከናውኑና ተስማምተው መስራች የሚችሉ ናቸው።
በተቃራኒው አምሽተው የሚተኙና አርፍደው የሚነሱት ግን የድብርት ስሜት የሚስተዋልባቸውና ለመጠጥ እንዲሁም ሲጋራ ሱስ የተጋለጡ ናቸው ይላሉ።
ምንም እንኳን የጠዋቶቹ ሰዎች ትምህርት ላይ ከፍ ያለ ውጤት የማስመዝገብ አቅም ቢኖራቸውም፤ አርፍደው የሚነሱት ግን ከፍ ያለ የማስታወስ ችሎታ፣ አዲስ ነገሮችን ቶሎ መላመድና አዳዲስ ሃሳቦችን ማፍለቅ ይችላሉ።
የትልልቅ ድርጅቶች ሃላፊ ለመሆንና ስኬታማ ለመሆን በጠዋት መነሳት ወሳኝ ነው ብለው ያምናሉ? ከሌሊቱ 11 ሰአት ለመነሳት በስልክዎ አላርም ይሞላሉ?
ይህን ከማድረግዎ በፊት እነዚህን ነገሮች ከግምት ውስጥ ያስገቡ።
ሰዎች በሚመቻቸውና የመጫጫን ስሜት በማይፈጥርባቸው ሰአት ከእንቅልፋቸው መነሳት ከቻሉ በጠዋት ከሚነሱት ያልተናነሰ ውጤታማና ደስተኛ መሆን እንደሚችሉ በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የሚያስተምሩት ካታሪና ዉልፍ ይገልጻሉ።
በሌላ በኩል እራስን በጠዋት እንዲነሱ ማስገደድ ላልተፈለገ የጤና እክል ሊያጋልጥም ይችላል ይላል።

የፎቶው ባለመብት, UniversalImagesGroup
አንዳንድ ጥናቶች እንሚያሳዩት ደግሞ በጠዋት የመነሳትና አርፍዶ የመነሳት ልማድ 47 በመቶ የሚሆነውን የምንወርሰው ከቤተሰቦቻችን ነው።
በጠዋት የመነሳት ፍላጎት እንደ ልምዳችን የሚወሰን ሲሆን ህጻናት ብዙ ጊዜ በጠዋት መነሳት ይመርጣሉ። እያደጉ ሲመጡና በተለይ ደግሞ በሃያዎቹ የእድሜ ክልል ውስጥ ሲሆኑ አርፍዶ ወደመነሳት ያዘነብላሉ።
ወደ ሃምሳዎቹ የተጠጉት ደግሞ ተመልሰው በጠዋት መነሳትን ያዘወትራሉ።
ሰዎች ስኬታማነትንና ደስተኝነትን በጠዋት ከመነሳት ጋር እንዲያያይዙት የሚገደዱት ደግሞ ትምህርትም ሆነ ስራ ብዙ ጊዜ የሚጀምሩት ከጠዋቱ 2 ሰአት ጀምሮ ባለው ጊዜ ሲለሆነ ነው።
ስለዚህ በጠዋት መነሳት የሚችሉ ሰዎች ትምህርቱንም ሆነ ስራውን ከአርፋጆቹ በተሻለ የመፈጸምና ስኬታማ የመሆን እድል ሊኖራቸው ይችላል።
በሌላ በኩል በጠዋት ከሚነሱት ጋር እኩል ለመሆንና በዚህ ፈጣን ዓለም ውስጥ ለመቆየት ሲሉ አርፍደው የሚነሱት ሰዎች ብዙ የፈጠራ ስራዎችንና አዳዲስ ሃሳቦችን እነዲያመነጩ ይገደዳሉ።
''ብዙዎቻችን በጠዋት የሚነሱ ሰዎች ንቁና ውጤታማ እንዲሁም አርፍደው የሚነሱት ደግሞ ሰነፍና አርፋጆች እንደሆኑ እየተነገረን ስለሆነ ያደግነው፤ በጠዋት መነሳትን እንፈልጋለን።''
''ነገር ግን በጠዋት መነሳታችን ብቻ ስኬታማ አልያም የትልቅ ድርጅት ባለቤት አያደርገንም። ዋናው ነገር ከእንቅልፋችን ከተነሳን በኋላ የምንሰራው ስራ ነው'' ይላሉ በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ባዮሎጂ የሚያስተምሩት ካትሪና ዉልፍ።












