ሙስናን በመቃወም የምትታወቀው ዩክሬናዊት የምክር ቤት አባል ከደረሰባት የአሲድ ጥቃት በኋላ ሕይወቷ አለፈ

የፎቶው ባለመብት, FACEBOOK/UAKATERYNA
ሙስናን በመቃወም የምትታወቀው ዩክሬናዊት የአሲድ ጥቃት ከደረሰባት ከሶስት ወር በኋላ ሕይወቷ አለፈ። የ33 ዓመቷ ካትሪና ሀንድዚዩክ በአሲድ ጥቃቱ የሰውነቷ 40 በመቶ እንዲሁም አይኗ ክፉኛ ተጎድቶ ነበር።
ይህች ሙስናን በመታገል የምትታወቅ እንስት የኬርሰን ከተማ ምክር ቤት አባል የነበረች ሲሆን ከአሲድ ጥቃቱ በኋላ 11 ቀዶ ጥገናዎችን አድርጋ ነበር።
ፕሬዚዳንት ፔትሮ ፖሮሴንኮ እሁድ ዕለት ጥቃት አድራሾቹ እንዲቀጡ ጠይቀዋል። አምስት ግለሰቦች ጥቃቱን በማድረስ ተጠርጥረው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል።
ወይዘሪት ሀንድዚዩክን ለሞት ያበቃት ትክክለኛ ምክንያት ባይታወቅም የሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ግን የደም መርጋት ነው ሲሉ ዘግበዋል።
በመስከረም ወር ላይ በፀረ ሙስና አቋሟ የምትታወቀው ይህች ተሟጋች ዩክሬናውያን ሙስናን በመታገል በጋራ እንዲቆሙ የሚጠይቅ ተንቀሳቃሽ ምስል ለጥፋ ነበር።
ግለሰቧ ከዩክሬን ለመነጠል በሚንቀሳቀሱ እና በሩሲያ የሚደገፉ ኃይሎችንም በመቃወም ትታወቃለች።
"አሁን መልከ ጥፉ እንደምመስል አውቃለሁ። ቢያንስ ግን ሕክምና አግኝቻለሁ" ብላ የነበረ ሲሆን አክላም "በዩክሬን ካለው የፍትህ ስርዓት የተሻለ ደምግባት እንደሚኖረኝ ግን እርግጠኛ ነኝ ምክንያቱም የፍትህ ስርዓቱን ማንም አላከመውም" ብላ ነበር።
በዚህች ተሟጋችና የምክር ቤት አባል ሞት ዩክሬናውያን በማህበራዊ መገናኛ ብዙኃን ላይ ድንጤያቸውን ሲገልፁ ተስተውሏል።














