ኤርትራ በምሽት በሰርሃና ዛላምበሳ ድንበርን ማቋረጥ ከለከለች

በዛላምበሳ የፀጥታ ኃይሎች ድንበሩን የሚያቋርጡ ሰዎችን ሲመዘግቡ

ከኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ በሚያስገባው ሰርሃ አካባቢ በሚገኘው ጊዜያዊ ፍተሻ ከምሽቱ 12 ሰአት በኋላ መኪና መግባት እና መውጣት እንደማይችል የኤርትራ የፀጥታ ኃይሎች አስታወቁ።

ይህ ከትናንትና ጀምሮ የተተገበረ ሲሆን ሰንዓፈ ደርሶ ወደ አዲግራት ሲመለሱ ከነበሩት መካከል አንዱ የሆነው ሙሉብርሃን ገብረዋህድ ከአስመራ ሲመጡ ከነበሩ ሰዎች ጋር ማለፍ እንደማይፈቀድለት ተነግሮት ሰርሃ ለማደር እንደተገደዱ ለቢቢሲ ገልጿል።

ለምን ማለፍ እንዳልቻሉ የኤርትራ የፀጥታ ኃይሎችን እንደጠየቁ የተናገረው ሙሉብርሃን "ማታ የሚያጋጥም የመኪና አደጋ እየበዛ ስለሆነ መግባት እና መውጣት እንድንከለክል ታዘናል" የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸውም ጨምሮ ተናግሯል።

በዚህም የተነሳ በርካታ መኪኖች መንገድ ላይ እንዳደሩ እሱም መኪና ውስጥ ማደሩን ይናገራል።

የትግራይ ምስራቃዊ ዞን አስተዳደር ስለዚህ ጉዳይ መረጃ ይኖረው እንደሆን ጠይቀን የሚያውቁት ነገር እንደሌለ የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ፈረደ ተናግረዋል።

የተንቀሳቃሹ ምስል መግለጫ, ለሁለት አስርት ዓመታት ተፋጠው የነበሩት ኤርትራና ኢትዮጵያ ጉዟቸው ምን ይመስላል?