ኢትዮጵያና ኤርትራ፡ አዲስ ዓመትን በቡሬና በዛላምበሳ

የፎቶው ባለመብት, FITSUM AREGA/TWITTER
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድና ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ሁለቱን ሃገራት በሚያዋሰኑባቸው በቡሬ በዛላምበሳ አካባቢዎች ተገኝተው ከሕዝቡና ሠራዊታቸው ጋር አዲስ ዓመትን አከበሩ።
ይህ በሁለቱ ሃገራት መካከል የተጀመረውን ግንኙነትን የማሻሻል እርምጃን ተከትሎ ተዘግተው የነበሩትን የሁለቱን ሃገራት የድንበር መተላለፊያዎች በመክፈት በኩል ትልቁ እርምጃ ነው ተብሏል።
በትናንትናው ዕለት ከሃያ ዓመታት በፊት ሁለቱ የሃገራት የድንበር ጦርነት ሲቀሰቀስ ጀምሮ ተዘግቶ የነበረው ከዛላምበሳ ወደ ሰንዓፈ የሚወስደውን መንገድ ተከፍቷል።
በአካባቢው የነበሩ የዓይን እማኞች እንደተናገሩት ከዚህ በተጨማሪ በስፍራው የነበረው የኤርትራ ጦር ምሽግም እንዲፈርስ ተደርጓል።
ሁለቱን ሃገራት የሚያገናኘው የድንበር መተላለፊያ አካባቢ ተቀብረው የነበሩ ፈንጂዎችን ማፅዳት ሥራ በሁለቱም ሠራዊት አባላት በጋራ ሲያከናውኑ ማየታቸውን የዓይን እማኞቹ ተናግረዋል።
የሁለቱ ሃገራት መሪዎች በሌላኛው ሃገር ያደረጉትን ጉብኝት ተከትሎ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ከማደሳቸው ባሻገር የአየር ትራንስፖርት ተጀምሯል።
ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው ከጂቡቲ በተጨማሪ ኢትዮጵያ ለወጪና ለገቢ ቁሳቁሶች ማንቀሳቀሻ ሁለቱን የኤርትራ ወደቦችን እንድትጠቀም ማስቻል ቀጣዩ እርምጃ እንደሚሆን ተነግሯል።

የፎቶው ባለመብት, FITSUM AREGA/TWITTER












