በወልዲያ እና ፍኖተ ሰላም ማረሚያ ቤቶች በተነሳ እሳት በንብረትና ሰው ላይ ጉዳት ደረሰ

የፎቶው ባለመብት, Facebook
በምዕራብ ጎጃም ፍኖተ-ሰላም እና በሰሜን ወሎ ወልዲያ ከተሞች ውስጥ በሚገኙ ማረሚያ ቤቶች ውስጥ የተቀሰቀሰን ግርግር ተከትሎ ባጋጠመ የእሳት ቃጠሎ በንብረት ላይ ውድመት መድረሱን የማረሚያ ቤቶቹ ኅላፊዎች ለቢቢሲ ተናገሩ።
በፍኖተ-ሰላም ከተማ ውስጥ የሚገኘው ማረሚያ ቤት ዛሬ ጠዋት 2 ሰዓት ላይ በወንዶች ማረሚያ ቤት ቆጠራ ሊካሄድ ሲል በታራሚዎች መካከል አምቧጓሮ መነሳቱን የሚናገሩት የማረሚያ ቤቱ ህዝብ ግንኙነት ረዳት ሳጅን ግርማ ሙሉጌታ ምክንያታቸው የአቃቢ ህጉ በቴሌቪዥን ቀርበው የሰጡት መግለጫ እንደሆነ ይናገራሉ።
ታራሚው ለምን አንፈታም በሚል ተቃውሞ ማሰማቱን የሚናገሩት ረዳት ሳጅን ግርማ አንቆጠርም በማለት ማስቸገራቸውን ገልፀዋል። የፖሊስ አባላት የታራሚውን ማመፅ ሲያዩ ወጥተው ጥበቃ ማጠናከራቸውን ወዲያውም በማረሚያ ቤቱ የሚገኘው የሸማ ማምረቻ ክፍል በእሳት እንደተያያዘ ያስረዳሉ።
ጨምረውም 26 የታራሚዎች ማደሪያ ክፍሎች ሙሉ በሙሉ በእሳት መውደማቸውን፤ በእሳቱ የታራሚዎች አያያዝና የሬጅስትራር ቢሮም መቃጠሉንም ተናግረዋል።
በቢሮው ውስጥ የነበሩት ኮምፒውተሮችን ማውጣት በመቻላቻው ከውድመት እንደተረፉ ገልፀዋል።
በተመሳሳይ ዜና በወልዲያ ማረሚያ ቤት ዛሬ ጠዋት 2 ሰዓት ላይ እሳት መነሳቱንና ሙሉ በሙሉ የወንዶች ማደሪያ እንዲሁም የስልጠና ማዕከሉ መሳሪያዎችና ማዕከሉ መውደሙን የማረሚያ ቤቱ የሕዝብ ግንኙነት ኮማንደር እንዳለ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ተቃውሞው የጀመረው ሰሞኑን ስኳር ባለመኖሩ ሻይ ስላልነበራቸው ሻይ ይግባልን በማለት እንደሆነ ያስረዱት ኮማንደሩ አስከትለውም ታራሚዎቹ ድንጋይ ውርወራ መጀመራቸውን ገልፀዋል።
እስካሁን ድረስ ሁለት ታራሚዎች መቁሰላቸውንም ጨምረው ነግረውናል።
በትናንትናው ዕለት በደብረማርቆስ ማረሚያ ቤት ቃጠሎ መድረሱም የሚታወስ ሲሆን አዲስ አበባ ቃሊቲና አርባ ምንጭ ውስጥ በሚገኙ ማረሚያ ቤቶች ውስጥ ታራሚዎች ተመሳሳይ የእንፈታ ጥያቄ በማቅረብ አለመረጋጋት እንደነበር ተገልጿል።
















