በመቅደላ ውጊያ ከኢትዯጵያ የተዘረፉ ቅርሶች በውሰት ለመለሱ ነው

V&A Museum, Maqdala 1868 display: Crown, gold and gilded copper with glass beads, pigment and fabric, made in Ethiopia, 1600-1850

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

የእንግሊዙ ቪክቶሪያና አልበርት ሙዚየም ከ150 ዓመታት በፊት በነበረው የመቅደላ ውጊያ በእንግሊዝ ወታደሮች ተዘርፈው የተወሰዱ በወርቅ የተንቆጠቆጠ ዘውድ፣ የሰርግ ቀሚስና የወርቅ ዋንጫዎችን በውሰት ሊመልስ ነው።

ከእነዚህ ቅርሶች መካከል የተወሰኑት እንደ አውሮፓውያኑ በ1868 የተካሄደው የመቅደላ ጦርነት አመታዊ በአል ሲዘከር ለእይታ መቅረባቸው ጥያቄዎችን አስነስቷል።

የእንግሊዝ ሃይል ቅርሶቹን ከመቅደላ ለመውሰድ 15 ዝሆኖችንና 200 በቅሎዎችን ለማጓጓዣነት ተጠቅመው እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ።

V&A Museum, Maqdala 1868 display: Cotton dress embroidered with silk, said to have belonged to Queen Woyzaro Terunesh, made in the 1860s

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

የምስሉ መግለጫ, በ1860 የተሰራው ይህ የሰርግ ቀሚስ የንግስት ጥሩነሽ እንደሆነ ይታመናል።

በ2008 ኢትዮጵያ ከመቅደላ የተዘረፉና በሚሊዮን ዶላር የሚገመቱ ቅርሶቿ እንዲመለሱላት ለተለያዩ የእንግሊዝ ቅርስ ተቋማት ጥያቄ አቅርባ ነበር።

የቪክቶሪያና አልበርት ሙዚየም ዳይሬክተር ትሪስትራም ሀንት ግን ቅርሶቹ የእንግሊዝ ሆነው እንደሚቀጥሉ ነገር ግን ለረዥም ጊዜ መቆየት ይችሉ ዘንድ በውሰት ወይም በብድር መልክ ለኢትዮጵያ ሊሰጡ እንደሚችሉ አስታወቁ።

Presentational grey line

መቅደላ 1868

V&A Museum, Maqdala 1868 display: Photograph of the Camp at Zoola during the Abyssinia Expedition 1868-9 by the Royal Engineers

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

  • በ19ኛው ክፍለ ዘመን ቴዎድሮስ ከእንግሊዝ ጋር ግንኙነት በመፍጠር አቢሲኒያን ለማዘመን ወሰኑ
  • ነገር ግን የወታደራዊ ድጋፍ ጥያቄያቸው በእንግሊዝ ችላ በመባሉ የአገራቱ ግንኙነት ሻከረ።
  • ለዚህ በምላሹም ቴዎድሮስ የእንግሊዝ ቆንስላና ሌሎች የውጭ ሃገር ዜጎችን አሰሩ።
  • ይህን ተከትሎ እንግሊዝ ወደ መቅደላው የንጉሱ ቤተ መንግስት ጦር ሃይል ላከች።
  • በእንግሊዞች እጅ አልወድቅም በማለት ቴዎድሮስ ራሳቸውን አጠፉ።
  • የእንግሊዝ ጦርም ውድ ብራናዎችን፣አክሊሎች፣መስቀል፣የወርቅ ዋንጫዎችን፣የንጉሳዊያንና የቤተ ክርስትያን ቁሳቁሶችን ጋሻና የመሳሰሉትን ዘርፈው ወሰዱ።
  • በጊዜው የንጉሱ የሰባት ዓመት ልጅም ወደ እንግሊዝ ተወስዶ በራግቢ ትምህርት ቤት እንዲማር ተደርጓል።
Maqdala 1868 display: Prince Alámayou, photograph, taken on the Isle of Wight, by Julia Margaret Cameron, July 1868

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

  • ልጃቸው በ18 ዓመቱ በሳንባ በሽታ ሲሞት በዊንድሶር ቤተመንግስት ተቀበረ።
  • የእንግሊዙ ቪክቶሪያና አልበርት ሙዚየም የወርቅ አክሊልና ዋንጫ አስቀምጧል።
  • ከመቅደላ የተዘረፉት ሌሎቹ ቅርሶች ከግለሰቦች ለሙዚየሙ በስጦታ የተበረከቱ ናቸው።
Presentational grey line

የሙዚየሙ ዳይሬክተር ሚስተር ሃንት ለአንድ የኪነጥበብ ጋዜጣ እንደገለፁት ሙዚየሙ ቅርሶቹን ለኢትዮጵያ ማዋስ እንደሚፈልግ በለንደን ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አስታውቀዋል።

አምባሳደሩ ሃይለሚካኤል አበራ አፈወርቅም "ከሙዚየሙ ጋር በተፈጠረው አጋርነት ተደስተናል ለጋራ ጥቅማችን አብሮ የመስራት ፍላጎትም አለን"ሲሉ ለጋርዲያን ተናግረዋል።

ሙዚየሙ እንዳስታወቀው ለዕይታ የቀረቡት እነዚህ ቅርሶች ታዳሚዎች የዕጅ ጥበብን ውበትና የብረታ ብረት ስራና የጥልፍ ዲዛይን ረቂቅነትን እንዲሁም ከቅርሶቹ ጋር የተያያዘውን አወዛጋቢ ታሪክ እንዲያስተውሉ እንደሚያደርግ ገልጿል።

V&A Museum, Maqdala 1868 display: L: Ethiopian silver leather and amber necklace formerly in the possession of Queen Terunesh R: Gold chalice with incised inscription, made by Walda Giyorgis, Gonder, Ethiopia, 1732-1740

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

የምስሉ መግለጫ, የንግስት ጥሩነሽ የአንገት ጌጥና ሙሉ በሙሉ ከወርቅ የተሰራ ዋንጫም ለእይታ ይቀርባሉ።

ለዘመናዊ ፎቶግራፍ መሰረት ነበሩ የተባሉ የጦር የእንግሊዝ ጦር ሃይል ፎቶግራፎችም ለእይታ እንደሚቀርቡም ሙዚየሙ አስታውቋል።

V&A Museum, Maqdala 1868 display: Maqdala church photograph by the Royal Engineers, Albumen print

የፎቶው ባለመብት, V&A Museum

የምስሉ መግለጫ, ይህ በመቅደላ የሚገኝ ቤተክርስትያን ፎቶ የተነሳው በእንግሊዝ ንጉሳዊ መሃንዲሶች ነው።