ሩሲያ ፕሪጎዢን እንዲገደል ትዕዛዝ ሰጥታለች መባሏን ውድቅ አደረገች

የሩሲያው ቅጥረኛ ተዋጊ ቡድን (ቫግነር) መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢን ነበረበት የተባለው አውሮፕላን ተከስክሶ ሁሉም ተሳፋሪዎች መሞታቸውን የሩሲያ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። በአውሮፕላኑ ውስጥ የቫግነሩ ቡድን መሪ ፕሪጎዢን እንዲሁም የቅርብ አጋሩ ዲሚትሩ ኡትኪን እንዳሉበት ተገልጿል። ዝም ብለው የቆዩት ቭላድሚር ፑቲን ስለአደጋው ሐሙስ ምሽት አስተያየት ሰጥተዋል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ሩሲያ የቫግነሩን አዛዥ ፕሪጎዥን እንዲገደል ትዕዛዝ ሰጥታለች መባሏን ውድቅ አደረገች

    የቭጌኒ ፕሪጎዥን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሩሲያ የቅጥረኛው ተዋጊ ቡድን (ቫግነር) አዛዥ የቭጌኒ ፕሪጎዥን እንዲገደል ትዕዛዝ ሰጥታለች መባሏን ውድቅ አደረገች።

    የፑቲን ቃለ አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ክሬምሊን ፕሪጎዥን እንዲገደል ትዕዛዝ ሰጥቷል መባሉ "ፍጹም ሃሰት ነው" ብለዋል።

    ቃለ አቀባዩ በአውሮፕላኑ ላይ ስለደረሰው አደጋ እንዲሁም ተሳፍረው ስለነበሩት ግለሰቦች "አሳዛኝ ሞት" "በርካታ መላ ምቶች እየተሰነዘሩ ነው" ብለዋል።

    "በምዕራቡ ዓለም በእርግጥ ይህ መላ ምት የሚመጣው ከተወሰነ አቅጣጫ ነው። ሁሉም ፍጹም ሃሰት ነው። በእርግጥ ስለ አደጋው ስንነጋገር በመረጃዎች እና በእውነታዎች ብቻ ልንመራ ይገባል" ብለዋል።

    አክለውም "በአሁኑ ጊዜ ብዙ መረጃዎች የሉም።በአሁኑ ወቅት ይፋዊ ምርመራ የተከፈተ ሲሆን ያሉትም መረጃዎች ሊፈተሹ ይገባል" ብለዋል።

    በርካታ ሩሲያውያን ከሁለት ቀናት በፊት ህይወቱን ቀጥፏል የተባለው የአውሮፕላን አደጋ ጀርባ ያለው ክሬምሊን ነው የሚል ጥርጣሬ አላቸው።

    ከሩሲያውያን በተጨማሪም ምዕራባውያን አገራትም ከግድያው ጀርባ ያሉት የሩሲያ ባለስልጣናት እንደሆኑ ጠቁመዋል።

    ነገር ግን ሩሲያ በጭራሽ ይህንን "ፍጹም ሃሰት" ነው ስትል ክዳለች።

    በትናንትናው ዕለት የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በአውሮፕላን አደጋ ለሞቱት ቤተሰቦች ሃዘናቸውን ገልጸዋል።

    ፑቲን የቅጥረኛው ተዋጊ ቡድን መሪ ፕሪጎዢን ከሟቾቹ መካከል መኖሩን በይፋ አላረጋገጡም።

  2. የፕሪጎዥን ደጋፊዎች ሐዘን እና የፑቲን ንግግር

  3. ዩናይትድ ኪንግደም ፕሪጎዢን ሞት እርግጥ ሳይሆን አይቀርም አለች

    ዬቭጌኒ ፕሪጎዢን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) የቫግነሩ አለቃ የቭጌኒ ፕሪጎዢን መሞት እርግጥ ሳይሆን አቀይቀርም አለች።

    የዩኬ መከላከያ ሚኒስቴር ምንም እንኳ እስካሁን ድረስ የቡድኑ መሪ በተከሰከሰው አውሮፕላን ላይ ተሳፍሮ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ባይኖርም፣ መሞቱ ግን እርግጥ ሳይሆን አይቀርም ብሏል።

    የቭጌኒ ፕሪጎዢን ተሳፍሮበታል በተባለው ከሞስኮ ወደ ሴንት ፒተርስበርግ ከተማ እየበረረ የነበረው አውሮፕላን ከተከሰከ በኋላ የቫግነሩ መሪ መሞት በስፋት ተዘግቧል።

    ምንም እንኳ እስካሁን ድረስ በየትኛውም አካል ለየቭጌኒ ፕሪጎዢን መሞት ማረጋገጫ ባይሰጥም፣ ሞስኮ በተከሰከሰው አውሮፕላን ተሳፍረው ከነበሩት መካከል ፕሪጎዢን አንዱ መሆኑን እንዲሁም ተሳፋሪዎቹ በሙሉ ሕይወታቸው ማለፉን አስታውቃለች።

  4. የፕሪጎዢን አውሮፕላን መከስከስን በተመለከተ እስካሁን የምናውቃቸው 4 ነገሮች

    የተከሰከሰው አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የተከሰከሰው አውሮፕላን
    • በአደጋው ፕሪጎዢን ሕይወቱ ሳያልፍ አይቀርም

    የአውሮፕላኑን መከስከስ ተከትሎ እስካሁን የቫግነር ቡድን መሪ ስለመገደሉ ይፋዊ ማረጋገጫ አልተሰጠም።

    ይሁን እንጂ ፕሪጎዢን ሳይሞት እንዳልቀረ አሜሪካ አስታውቃለች። የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲንም በፕሪጎዢን ሞት ማዘናቸውን እና ምርመራ እንደሚካሄድ ገልጸዋል።

    • ፍንዳታ ለአውሮፕላኑ መከስከስ ምክንያት ነው

    የቅጥረኛ ቡድኑ ቫግነር መሪ ዮቭጌኒ ፕሪጎዢን ተሳፍሮበት የነበረው አውሮፕላን ተከስክሶ ሕይወቱ ሳያልፍ አይቀርም መባሉን ተከትሎ በርካቶች ለአውሮፕላኑ መከስከስ ምክንያት ነው ያሉትን መላምት ሲሰነዝሩ ቆይተዋል።

    ለአውሮፕላኑ መከስከስ ከተሰጡ መላምቶች መካከል ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው ትልቁን ቦታ ይይዛል።

    ይሁን እንጂ አሜሪካ አውሮፕላኑ በሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው ትንተና እውነት የመሆን ዕድሉ ጠባብ ነው ብላለች።

    አንድ በስም ያልተጠቀሱ የአሜሪካ መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን በተመሳሳይ ለሲቢኤስ ሲናገሩ አውሮፕላኑ በሚሳኤል ተመትቶ ሳይሆን የተከሰከሰው ምናልባት አውሮፕላኑ ላይ የነበረ ቦምብ ከፈነዳ በኋላ ነው አደጋው የደረሰው ብለዋል።

    አውሮፕላኑ ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው መላምት በስፋት ተሰራጭቷል።

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, አውሮፕላኑ ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው መላምት በስፋት ተሰራጭቷል።
    • ለአውሮፕላኑ መከስከስ ፑቲን ተጠያቂ ሆነዋል

    ምንም እንኳ እስካሁን ለአውሮፕላኑ መከስከስ ትክክለኛው መንስዔ በይፋ ባይገለጽም ለአውሮፕላኑ መከስከስ በሞስኮ ያሉ ባለስልጣናት ተጠያቂ ሆነዋል።

    ለቅጥረኛ ቡድኑ ቅርበት ያለው የቴሌግራም ገጽ አውሮፕላኑ ሞስኮ ባሉ ‘ከሃዲዎች’ ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል ብሎ ነበር።

    ቭላድሚር ፑቲን በአደጋው አዝኛለሁ ካሉ በኋላ የአደጋው መንስዔ ይጣራል ብለዋል።

    የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ ደግሞ አውሮፕላኑን ማን መትቶ እንደጣለ ዓለም ያውቃል በማለት ጣታቸውን ፑቲን ላይ ቀስረዋል።

    • የአውሮፕላኑ መከስከስ

    የቫግነሩን መሪን ጨምሮ 10 ሰዎችን አሳፍሮ የነበረው ኤምባሪዬር-135 የመንገደኞች አውሮፕላን ከሞስኮ ወደ ሴንት ፒተርስበርግ ሲበር ነበር አደጋው በሩሲያ አየር ክልል ውስጥ የደረሰው።

    የዓይን እማኞች አውሮፕላኑ ኩዝሄንኪኖ በተባለች መንደር ውስጥ ከመውደቁ በፊት ሁለት የፍንዳታ ድምጾችን ሰምተናል ብለዋል። የሩሲያ ባለስልጣናት ሁሉም ተሳፋሪዎች ሕይወታቸው አልፏል ብለዋል።

  5. አሜሪካ የፕሪጎዢን አውሮፕላን በሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል መባሉ ሐሰት ሊሆን ይችላል አለች

    የቴንታጎን ቃል አቀባይ

    የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE/REX/Shutterstock

    አሜሪካ ፕሪጎዢን ተሳፍሮበት የነበረው አውሮፕላን ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው ትንተና የሚያስኬድ አይደለም አለች።

    የአሜሪካ መከላከያ ቢሮ ፔንታጎን ክስተቱን በተመለከተ በሰጠው መግለጫ ምናልባት አውሮፕላኑ የተከሰከሰው ተጠምዶበት የነበረው ቦምብ መፈንዳትን ተከትሎ ነው ብሏል።

    የቅጥረኛ ቡድኑ ቫግነር መሪ ዬቭጌኒ ፕሪጎዥን ተሳፍሮበት የነበረው አውሮፕላን ተከስክሶ ሕይወቱ ሳያልፍ አይቀርም መባሉን ተከትሎ በርካቶች ለአውሮፕላኑ መከስከስ ምክንያት ነው ያሉትን መላምት ሲሰነዝሩ ቆይተዋል።

    ለቅጥረኛ ቡድኑ ቅርበት ያለው የቴሌግራም ገጽ አውሮፕላኑ ሞስኮ ባሉ ‘ከሃዲዎች’ ከምድር ወደ ሰማይ በሚወነጨፍ ሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል ብሏል።

    ይሁን እንጂ የአሜሪካ መከላከያ ቃል አቀባይ ብርጋዲዬር ጀነራል ፓትሪክ ራይደር የአውሮፕላኑን መከስከስ ተከትሎ የዩቭጌኒ የመሞት ዕድል ከፍተኛ መሆኑን ተናግረው አውሮፕላኑ ግን በሚሳኤል ተመትቶ ወድቋል የሚለው እውነት የመሆኑ ዕድል ጠባብ ነው ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ፣ ኤምባሪዬር የተባለው የመንገደኞች አውሮፕላን በሚሳኤል ተመትቶ ስለመውደቁ የሚያረጋግጥ ምንም አይነት መረጃ እንደሌለም ተናግረዋል።

    አንድ በስም ያልተጠቀሱ የአሜሪካ መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን በተመሳሳይ ለሲቢኤስ ሲናገሩ አውሮፕላኑ በሚሳኤል ተመትቶ ሳይሆን የተከሰከሰው ምናልባት አውሮፕላኑ ላይ የነበረ ቦምብ ከፈነዳ በኋላ ነው አደጋው የደረሰው ብለዋል።

    ኃላፊው አውሮፕላኑ ላይ ለታየው ፍንዳታ እስካሁን ትክክለኛው ምክንያት ምን ሊሆን እንደሚችል ግልጽ ባይሆንም ቦምብ የመሆን ዕድሉ ግን ሰፊ መሆኑን ገልጸዋል።

  6. ቭላድሚር ፑቲን በፕሪጎዢን ሞት ማዘናቸውን እና ምርመራ እንደሚካሄድ ገለጹ

    ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Sputnik/Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን

    የቫግነር ቡድን አዛዥ የሆነው የቭጌኒ ፕሪጎዢን ሞቶበታል የተባለውን የአውሮፕላን አደጋን በተመለከተ ወዲያውኑ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበው የቆዩት የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ዝምታቸውን ሰብረዋል።

    ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን የዓለም መነጋገሪያ የሆነውን እና ረቡዕ እለት የተከሰተውን የአውሮፕላን አደጋ የሰሙት ሐሙስ ጠዋት መሆኑንም ገልጸዋል።

    ፑቲን በአደጋው ሕይወታቸው ላለፈ ሰዎች ቤተሰቦች ሐዘናቸውን የገለጹ ሲሆን፣ የቫግነር ቡድን መሥራች እና መሪ የነበረውን ፕሪጎዢንን “ባለተሰጥኦ የንግድ ሰው” ሲሉ ገልጸውታል።

    ፑቲን በቴሌቪዥን በተላላፈ ንግግራቸው ላይ የአውሮፕላን አደጋውን በተመለከተ ምን እንደተከሰተ ምርመራ እንደሚካሄድ፣ ነገር ግን ጊዜ እንደሚፈልግ አስረድተዋል።

    ፑቲን “ፕሪጎዢንን ከ1990ዎቹ መጀመሪያ አንስቶ ለረጅም ጊዜ አውቀዋለሁ” በማለት በንግግራቸው የነበራቸውን ግንኙነት ጠቅሰው፣ ሌሎችንም ጉዳዮች አንስተዋል።

    ባለፈው ሰኔ ወር አጋማሽ ላይ በፕሪጎዢን ተመርቶ የከሸፈውን አመጽ በማመልከትም “ፕሪጎዢን የተወሳሰበ ዕጣ ፈንታ የነበረው፣ በሕይወቱም ከባድ ስህተቶችን የፈጸመ ሰው ነው። ነገር ግን በጠየቅሁት ጊዜ ለእራሱ እና ለእኔም ጠቃሚ ውጤቶችን አስገኝቷል” ብለዋል።

    አደጋው በደረሰበት አውሮፕላን ውስጥ ከፕሪጎዢን ጋር ምክትሉ ዲሚትሪ ኡትኪንን ጨምሮ አምስት የቫግነር አባላት እንዲሁም ሦስት የአውሮፕላኑ ሠራተኞች ነበሩ።

    ፑቲንም “የመጀመሪያ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የቫግነር ኩባንያ ሠራተኞች በአውሮፕላኑ ተሳፍረው ነበር” ብለዋል።

    ፑቲን ጨምረውም “እነዚህ ሰዎች የጋራ አላማችን የሆነውን በዩክሬን ውስጥ የኒዮ-ናዚ እንቅስቃሴን በመዋጋት በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን መጥቀስ እፈልጋለሁ።”

    “ይህንንም እናውቃለን፣ እናስታውሳለን፤ ፈጽሞም አንዘነጋውም” ብለዋል።

  7. በፕሪጎዢን ሞት ውስጥ የማን እጅ እንዳለበት ሁሉም ያውቃል - ዜሌንስኪ

    ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ
    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ

    በቫግነር ቡድን መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢን ሞት ውስጥ ዩክሬን ምንም አይነት ሚና እንደሌላት ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ተናገሩ።

    “በዚህ ሁኔታ ውስጥ በእርግጠኝነት ምንም ተሳትፎ የለንም። በክስተቱ ውስጥ የማን እጅ እንዳለበት ሁሉም ሰው ያውቃል ብዬ አስባለሁ” ሲሉ የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ዋና ከተማ ኪየቭ ውስጥ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ሩሲያ በዩክሬን ላይ በፈጸመችው ወረራ ውስጥ ፕሪጎዢን የሚመራው የቫግነር ቡድን ከሩሲያ ጦር ሠራዊት ጎን በመሠለፍ የተዋጋ ሲሆን፣ ባኽሙት በተባለቸው ከተማ ውስጥ በተካሄደው ውጊያ ሩሲያ ላገኘችው ድል ቡድኑ ጉልህ ሚና ተጫውቷል።

  8. የቫግነር ደጋፊዎች በፕሪጎዢን ሞት ሐዘናቸውን እየገለጹ ነው

    የቅጥረኛው የቫግነር ቡድን ወታደሮች እና ደጋፊዎች በአውሮፕላን አደጋ መሞቱ በተነገረው የቡድኑ መሪ የቭጌኒ ፕሪኮጎን ሞት የተሰማቸውን ሐዘን ሩሲያ ውስጥ በአደባባይ እየገለጹ ነው።

    በሴንት ፒተርስበርግ እና ኖቮሲቢርስክ ውስጥ የፕሪጎዢን እና የምክትሉ ምስል በተቀመጠባቸው የመታሰቢያ ስፍራዎች በመገኘት ሻማ በማብራት እና አበባዎችን በማኖር ሐዘናቸውን ሲገልጹ ታይተዋል።

    የቫግነር ደጋፊዎች በፕሪጎዢን ሞት ሐዘናቸውን እየገለጹ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ሴንት ፒተርስበርግ - ሩሲያ
    የቫግነር ደጋፊዎች በፕሪጎዢን ሞት ሐዘናቸውን እየገለጹ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኖቮሲቢርስክ - ሩሲያ
    የቫግነር ደጋፊዎች በፕሪጎዢን ሞት ሐዘናቸውን እየገለጹ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኖቮሲቢርስክ - ሩሲያ
  9. ፑቲን ከአውሮፕላኑ መከስከስ በኋላ በብሪክስ ጉባኤ ንግግር አደረጉ

    ፑቲን በቪዲዮ ለብሪክ ጉባኤ ንግግር አድርገዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፑቲን በቪዲዮ ለብሪክ ጉባኤ ንግግር አድርገዋል

    ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በጆሃንስበርግ እየተካሄደ ለሚገኘው የብሪክስ ጉባኤ አጭር የቪዲዮ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ፕሬዝዳንቱ የደቡብ አፍሪካ አቻቸውን ሲሪል ራማፎሳን ጉባኤውን ስላስተናገዱና ብሪክስ የአባላቱ ቁጥር እንዲሰፋ ላደረጉት ጥረት አመስግነዋል።

    ብሪክስን ኢትዮጵያ፣ ግብጽ፣ የተባበሩት አርብ ኤሜሬትስ፣ ሳዑዲ፣ ኢራንና አርጀንቲና ብሪክስን መቀላቀላቸው ከተሰማ በኋላ ነው ፑቲን ንግግር ያደረጉት።

    ሆኖም የትላንት ምሽቱን ክስተት በተመለከተ ያሉት ነገር የለም።

  10. የሩስያ መገናኛ ብዙሃን እና የአውሮፕላን አደጋው

    የሩሲያ ዜና አቅራቢያ

    የፎቶው ባለመብት, Rossiya 1

    በሌላ በኩል ይህ ዓለምን እያነጋገረ ያለ ክስተት በሩስያ መገናኛ ብዙሃን ብዙ ሽፋን እየተሰጠው አይደለም።

    የአውሮፕላኑ መከስከስ በመንግስታዊው ሮዚያ 1 ሚዲያ አጭር የሰበር ዜና ሽፋን ተሰጥቶት ነበር።

    ዜናው 10 ሰው የያዘ አውሮፕላን መውደቁን እና ሁለም ማለፋቸውን ዘግቧል።

    ሌላ የሩስያ መንግሰት ቴሌቪዥን ጣቢያ ደግሞ ከሞስኮ ወደ ሴንት ፒተርስበርግ ሲበር የነበረ የግል አውሮፕላን ተከስክሶ 7 ተሳፋሪዎችና ሶስት የበረራ ባለሙያዎች መሞታቸውን ዘግቧል።

    የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች በስፍራው እንደተሰማሩም ጨምሯል።

    ሁለቱም ዘገባዎች የሩስያን አቪዬሽን ባለስልጣን ጠቅሰው በተሳፋሪዎች ዝርዝር ውስጥ የፕሪጎዢን ስም እንደሚኝ ገልጸዋል።

    ግን የዘገባ አውድ ወይም አስተያየት ከመስጠት ግን ተቆጥበዋል።

  11. ቫግነር መፈንቅለ መንግስት ከሞከረ በኃላ የሩስያ መንግስት እያደከመው ነበር ተባለ

    የቫግነር ተዋጊዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ባለፉት ሁለት ወራት ቫግነር ቀስ በቀስ እየሞተ ነበር ይላሉ ጀስቲን ክራምፕ።

    ክራምፕ በብሪታኒያ ወታደራዊ ደህንነት አማካሪ ድርጀት መሪ ናቸው።

    ለቢቢሲ 4 ሬዲዮ በሰጡት አስተያየት አሁን የሰውዬው ሞት ቅጥረኛ ተዋጊውን “በውስን አማራጭ” ላይ ነበር ይላሉ።

    እንደሳቸው ገልጻ ልክ የዛሬ ሁለት ወር በሩስያ መፈንቅለ መንግስት ከተደረገ በኋላ የተዋጊ ቡድኑን መጪ ጊዜ በተመለከተ አሉባልታዎች ሲናፈሱ ነበር።

    በዩክሬን የተሰማሩት የቅጥረኛ ቡድኑ ተዋጊዎች ወደ ድንበር እየወጡ ነው የሚሉ መረጃዎች እየወጡ ነው።

    “ቫግነር ይህን አድርጓል አላደረገም የሚሉ ክሶች አሉ። እንደሚመስለኝ አሁን ያለው እውነታ ቡድኑ ባለፉት ጥቂት ወራት እየተበተነ ነበር” ብለዋል።

    አክለውም “ቡድኑ ከሁለት ወር በፊት ከነበረበት ሁኔታ እንዳይሻሻልና ክንድ እያፈረጠመ እንዳይሄድ ከፍተኛና ጥብቅ ክትትል ሲደረግብት ነበር ”ብለዋል።

  12. ስለተከሰከሰው አውሮፕላን የፑቲን ቢሮ ምን አለ?

    ፕሬዝዳንት ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቫግነሩን መሪ የያዘው አውሮፕላን ተከስክሶ ሰውዬው መሞታቸው ከተነገረ በኋላ ፕሬዝዳንት ፑቲን የሰጡት አስተያት የለም።

    ጽህፈት ቤታቸው በተከሰከው አውሮፕላን ውስጥ ተሳፍረው ከሞቱት 10 ሰዎች የቭጌኒፕሪጎዢን ስለመኖራቸው የሰጠው ማረጋገጫ የለም።

    በሩስያ የምርመራ ኮሚቴ ከአደጋው ጋር በተያያዘ “የወንጀል ክስ መዝገብ” መክፈቱን የኮሚቴው ቃል አቀባይ ሴቭታልና ፔትሪንኮ ተናግረዋል።

    እሳቸው እንደሚሉት የምርመራ ቡድን አደጋው ወደ ተከሰተበት ስፍራ የተላከ ሲሆን የማስረጃ ማሰባሰብና ምርመራ ተደርጓል።

    ትላንት ከሞስኮ በሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ ባለቸው የሩሲያዋ ቴቨር ግዛት 10 ሰዎችን ይዞ የተከሰከሰው የግል አውሮፕላን የቫግነሩ መሪ እንደነበሩበት ይታመናል።

    ‘ኢምባራ 135’ የተሰኘው የቭጌኒፕሪጎዢን የግል አውሮፕላን ከሞስኮ ወደ ሴንት ፒተርስበርግ ሲጓዝ የነበረ ሲሆን 7 ተሳፋሪዎችና 3 የበረራ ባለሙያዎችን ያካተተ እንደነበር የሩስያ አቪይሽን ባለስልጣን ገልጿል።

  13. የቭጌኒ ፕሪጎዢን ማን ነው?

    የቭጌኒ ፕሪጎዢን

    የፎቶው ባለመብት, TELEGRAM

    ስለ ቫግነሩ መሪ የቭጌኒፕሪጎዢን ብዙ ተብሏል።

    ሰውዬው የቫግነር ቅጥረኛ ተዋጊ ከተመሰረተበት ከአውሮፓያኑ 2014 ጀምሮ መሪ ነበር።

    ለፑቲን ቤተ መንግስት ወይም ክሪምሊን ምግብ ሲያቀርብ ስለነበር “የፑቲን ሼፍ” በሚል የሚታወቀው ፕሪጎዢን ባለሃብት የነበረ ሲሆን የወንጀልተሳትፎ እንዳለውይነገራል።

    ባለፈው ሰኔ ወር ለአጭር ጊዜ የቆየ ወታደራዊ አመጽ የመራ ሲሆን ተዋጊዎቹ በደቡባዊ ሩስያ የምትገኝ ከተማን ተቆጣጥረው ወደ ሞስኮ ማቅናት ጀምረው ነበር።

    የዚህ እንቅስቃሴ ዓላማም ወደ ወታደራዊ አመራርን ማስወገድ የሚል ነበር።

    ሆኖም ፕሪጎዢን ከሩስያ መንግስት ጋር በቤላሩሱ መሪ አሌክስአንድር ሉካሼንኮ አማካኝነት ከተደራደሩ በኃላ ወደ ሞስኮ የሚያደርገውን ወታደራዊጉዞ አቁሟል።።

    ይህ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዲቆም በተደረገው ስምምነት ፕሪጎዢንላይ የተመሰረተው ክስ የተቋረጠ ሲሆን ወደ ቤላሩስ እንዲያቀናም ተመቻችቶለት ነበር።

    እስከዚያ ጊዜ ድረስ ስለሰውዬው ብዙም አይታወቅም ነበር።

    ከትቂት ቀናት በፊት በተሰራጨ አንድ ቪዲዮ ላይ በአንድ የአፍሪካ ሀገር እንደሚገኝ ጠቁሞ ነበር።

  14. የቭጌኒ ፕሪጎዢን ይዞ እንደነበር በታመነው አውሮፕላን የነበሩት ሌሎች ተሳፋሪዎች እነማን ናቸው?

    የተከሰከሰው አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቫግነሩ መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢንእና ቀኝ እጃቸው ናቸው የሚባሉት ዲሚትሪ ኡትኪን ሲጓዙበት እንደነበረ የታመነው አውሮፕላን 7 ሰዎች መሞታቸውን የሩሲያ አቬሽን ባለስልጣን ገልጿል። የተቀሩት አምስት ሰዎች ማን ናቸው?

    ቫልሪይ ቼክሎቭ

    ቫልሪይ ቼክሎቭ የፕሪጎዢንየቅርብ ጓደኛ ከሆኑት መካከል ሲሆኑ ከአውሮፓውያኑ 2000 ጀምሮ የቫግነር ትውውቅ እንደነበራቸው ይነገራል።

    ቼክሎቭ የቫግነር የሎጀስቲክስ ኃላፊ ነበሩ። በተጨማሪም ለቫግነር ተዋጊዎች ምግብ የሚያቀርበውን ተቋም እና ከስነ ምድር፣ የነዳጅ ምርትና ግብርና ጋር የተያያዙ ፕሮጀክቶችን ይቆጣጠራሉ።

    በሶሪያ ውስጥም ተሳትፎ ነበራቸው።

    ቼክሎቭ እንደ የቫግነሩ መሪ በመሆን ለሩስያ የጦር መሳሪያ በማቅረብ አሜሪካ ማዕቀብ ጥላባቸው ነበር።

    ዬቪግኒ ማካራያን

    ቀድሞ የአውራጃ አስተዳዳሪ የነበሩት ማካራያን ቫግነርን የተቀላቀሉት እንደ አውሮፓውያኑ በ2016 እንደነበር መረጃዎች ያመላክታሉ።

    በሶሪያም ጦርነት ውስጥ የተሳተፉ ሲሆን ማከር የሚል መጠሪያም ነበራቸው።

    ሰርጌይ ፕሮፓስቲን

    ሰርጌይ ፕሮፓስቲን ከአውሮፓውያኑ 2015 ጀምሮ ቫግነርን የተቀላቀሉ ሲሆን “ከድር” የሚል መጠሪያም ነበራቸው። በሁለተኛው የቺቺኒያ ጦርነትም ተሳትፈዋል።

    መረጃዎች እንደሚያመለከቱት ሰውየው ለቫግነሩ መሪ የግል ጥበቃ ሲያቀርብ ከኖረ አሃድ ወይም ዩኒት ነው የተገኙት።

    አሌክስ አንድር ቶትሚን

    ቶት በመባል የሚጠሩት ቶትሚን ቅንጡ ህይወታቸውን የሚያሳዩ ፎቶዎችን ኢንስታግራም ላይ በማጋራት ይታወቃሉ።

    ኒኮላይ ማቱሲቭ

    ስለኚህ ግለሰብ ብዙ የሚታወቅ ነገር የለም። መረጃዎች ግለሰቡ በአውሮፓውያኑ 2017 ቫግነርን እንደተቀላቀሉ ያመከክታሉ።

  15. ፕሪጎዢን የተሳፈረበት አውሮፕላን ከተከሰከሰ በኋላ ሩሲያ ምን አለች?

    ክሬምሊን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሩሲያ በአስገራሚ ክስተቶች የተሞላች አገር ናት።

    ሰው አልባ አውሮፕላኖች ( ድሮኖች) በሩሲያ መሃል ሞስኮ በተደጋጋሚ ጥቃት በማድረስ ፍንዳታዎችን ከፈጠሩ እና ሕንጻዎችን ካፈራረሱ በኋላ በርካቶች ተደናግጠዋል።

    ከዚያም የሩሲያ መገበያያ ገንዘብ ሩብል ዋጋ ባልተጠበቀ ሁኔታ አሽቆልቁሏል።

    በአጭር ጊዜ ውስጥም የአንድ ዶላር ምንዛሬ ዋጋ ከ100 ሩብል በላይ ደርሷል።

    ጨረቃ ላይ ለማረፍ ያካሄደችው ተልዕኮዋም አልተሳካም። የሩሲያ ሉና- 25 ላንደር [ጨረቃ ወለል ላይ የሚያርፈው የመንኮራኩል አካል] ጠፈር ላይ ጠፍቶ የነበረ ሲሆን ባለፈው ሳምንት ከጨረቃ ወለል ጋር ተጋጭቶ ወድሟል።

    ዛሬ ደግሞ የቫግነር ቅጥረኛ ቡድን መሪ ዮቭጌኒ ፕሪጎዢን ተሳፍረውበታል የተባለው አውሮፕላን በሩሲያ ትቨር ክልል በእሳት ተያይዞ መከስከሱ ተሰምቷል።

    ይህ ግን በርካታ ሰዎችን እምብዛም ያስደነገጠ አይመስልም።

    እንዲያውም ሩሲያውያን ክስተቱ ቶሎ ባለማጋጠሙ ሳይገረሙ አልቀረም።

    ምክንያቱም በሩሲያ የየቭጌኒ ፕሪጎዥን ዕጣ ፈንታ ምን ሊሆን ይችላል በሚል ለሳምንታት የተለያዩ መላ ምቶች ሲሰነዘሩ ቆይተዋል።

  16. የቫግነር መሪን እንደያዘ የታመነው አውሮፕላን እጅግ ሳይጠበቅ መውደቁ ተነገረ

    የተከሰከሰው አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቫግነሩን መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢንንአሳፍራ የነበረችው አውሮፕላን ከመከሰከሷ 30 ሰከንድ አስቀድሞ ባሉት ጊዜያት ምንም ለአደጋ የሚያጋልጥ ምልክት እንዳልታየባት የበረራመከታተያ መረጃዎች አሳይተዋል።

    ኢያንፔትቼኒክ የተባሉት እና ፍላይት ራዳር 24 የሚሰሩ ባለሙያ ለሮይተርስ እንደተናገሩት አውሮፕላኗ “በድንገት ወደ ቁልቁል መጓዝ እንደጀመረች” ተናግረዋል።

    ከዚያ በ30 ሰከንድ ውስጥ አውሮፕላኗ ከ 28 ሺህ ጫማ ከፍታ ወደ 8 ሺህ ቁልቁል መምዘግዘግ እንደጀመረች ጠቁመዋቀል።

    “የተከሰተው ምንም ይሁን ምን የሆነው ግን በፍጥነት ነው” ያሉት ባለሙያው አደጋው ከመከሰቱ በፊት አውሮፕላኗ ላይ ችግር ስለመኖሩ አመላካች ነገር አልነበረም ነበር ሲሉ አክለዋል።

    በማህበራዊ ትስስር ገጾች የተሰራጨ ቪዲዮ አውሮፕላኗ ከሰማይ ቁልቁል ከጭስ ጋር ተምዘግዝጋ ስትወርድ አሳይቷል።

  17. በተከሰከሰው አውሮፕላን ውስጥ የነበሩ ተሳፋሪዎችን አስከሬን አግኝተናል- የሩሲያ ባለስልጣናት

    አውሮፕላኑ የተከሰከሰበት ስፍራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በተከሰከሰው ኤምብራየር ሌጋሲ በተሰኘው የግል ጄት ተሳፋሪ የነበሩ አስር ግለሰቦች አስከሬን መገኘቱን የሩሲያ የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት አስታወቀ።

    ከተሳፋሪዎቹም መካከል የሩሲያው ቅጥረኛ ተዋጊ ቡድን (ቫግነር) መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢን እና የቅርብ አጋራቸው እና ምክትል አዛዣቸው ዲሚትሪ ኡትኪን እንደሚገኙበትም ተናግረዋል።

    በአሁኑ ወቅት በዋነኝነት መነጋገሪያ የሆነው ለአውሮፕላኑ መከስከስ መንስዔው ምንድን ነው? የሚለው ነው።

    ፖሊስ የአውሮፕላን አደጋ የተከሰተበትን አካባቢ የዘጋ ሲሆን የሩሲያ አቪዬሽን ባለስልጣንም አደጋውን የሚመረምር ልዩ ኮሚሽን አቋቁሟል።

    የፕሪጎዥን መሞት በትናንትናው ዕለት ሲዘገብ በርካታ ሩሲያውያንን አላስገረመም።

    ከሁለት ወራት በፊት በሩሲያ ጦር ላይ ያልተሳካ ዓመጽ የመራው ፕሪጎዢን የፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንንም ስልጣን ተገዳድሯል።

    ይህንንም ሁኔታ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ፑቲን በቀላሉ የማይረሱት ጉዳይ ነው።

  18. ሩሲያን አሸብሮ የነበረው የቫግነር ቡድን ማን ነው? መሪውስ?

    የቫግነር መስራች እና መሪ የቭጌኒ ፕሪጎዢን (መሃል) ከሩሲያ መከላከያ ሚንስትር ጋር ሲነጋገሩ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሩሲያ ከጥቂት ወራት በፊት ውጥረት አይሎባት ነበር።

    ቫግነር የተባለው ቅጥረኛ ተዋጊ ቡድን በፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን አስተዳደር ላይ አምጾ በሞስኮ ውጥረትም ነግሶ፤ ሽብርም ተነዝቶ ነበር።

    በአሁኑ ወቅት ህይወቱ አልፏል የተባለው የቡድኑ መስራች የቭጌኒ ፕሪጎዢን የሩሲያን መከላከያ ከፍተኛ አመራሮች “ልክ አስገባለሁ” ብሎ ዝቶ ወደ ሞስኮ መገስገስ ጀምሮ ነበር።

    ይሁን እንጂ በፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን አስተዳደር ላይ አመጽ አስነስተው ወደ ሞስኮ ሲገሰግሱ የነበሩት የቅጥረኛው ቫግነር ቡድን መሪ የጦር እንቅስቃሴያቸውን ለማቆም ተስማምተው ከአገር ወጥተዋል።

    ሩሲያ ከቫግነር ቅጥረኛ ተዋጊዎች ቡድን ጋር ግንኙነት የለኝም ስትል ታስተባብል እንጂ፣ የቡድኑ መሥራች ከሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ቅርብ ግንኙነት ነበራቸው።

    የቭጌኒ ከዚህ ቀደም በወንጀል ድርጊቶች ጥፋተኛ ተብሎም ተፈርዶበታል። የቭጌኒ “የፑቲን ሼፍ” በመባል የሚታወቅ ከበርቴ ነው። 'የፑቲን ሼፍ' የሚለውን ስያሜ ያገኘው የክሬምሊን ምግብ አዘጋጅ እና የሬስቶራንት ባለቤት ስለነበር ነው።