ቀጥታ, እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ድብደባ 31 ሰዎች ሲገደሉ ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች

እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት 31 ሰዎች ሲገደሉ 149 ደግሞ ጉዳት እንደ ደረሰባቸው የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። ኢራን በበርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ዛሬም ቀጥላለች። በባህሬን እና ዱባይ እንዲሁም በኩዌት የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በኩዌት ሉዓላዊ ግዛት ላይ የተፈጸመውን ጥቃት አወገዙ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እሁድ ዕለት ኢራን በኩዌት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ከኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ ጋር በስልክ መወያየታቸው ተገለፀ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከኩዌቱ ልዑል አልጋ ወራሽ ጋር ባደረጉት ውይይት በአገሪቱ ሉዓላዊ ግዛት እና የአየር ክልል ላይ የሚፈጸም ጥቃትን በጽኑ ማውገዛቸውን የኩዌት የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዐቢይ፤ ድርጊቱ የዓለም አቀፍ ሕግ እና የተባበሩት መንግሥታት ቻርተር ጥሰት ነው ማለታቸውን ዘገባው ያመለክታል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከልዑል አልጋ ወራሹ ጋር በነበራቸው የስልክ ንግግር ወቅት የኩዌት ዜጎች እና ተቋማት ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ማውገዛቸው ተገልጿል።

    ዘገባው እንደሚያመለክተው ዐቢይ፤ በኩዌት የሲቪል ተቋማት ላይ የሚፈጸም ጥቃት ተቀባይነት እንደሌለውም ተናግረዋል።

    ዐቢይ ኢትዮጵያ፣ የኩዌት መንግሥት እና አመራር የአገሪቱን ሉዓላዊነት፣ መረጋጋት እና ደኅንነት ለመጠበቅ በሚወስደው ማንኛውም እርምጃ ድጋፋቸውን ገልጸዋል።

    ኢራን በትናንትናው ዕለት በመካከለኛው ምሥራቅ በፈጸመችው ጥቃት በኩዌት የአንድ ሰው ሕይወት ማለፉ ተገልጿል።

    ኢራን በበርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ዛሬም ጥቃት የፈጸመች ሲሆን በባህሬን፣ ዱባይ እንዲሁም በኩዌት የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ስላሳዩት ድጋፍ እንዳመሰገኑም የዜና ወኪሉ ዘግቧል። የዓለም መንግሥታት በኢራን ላይ ስለደረሰው ጥቃት ምን አሉ?

  2. ትራምፕ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ሊተኩ የሚችሉ በርካታ ዕጩዎች በመጀመሪያው ዙር ጥቃት ተገድለዋል አሉ

    ዶናልድ ትራምፕ ከአሜሪካው የቴሌቪዥን ጣቢያ ኤቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ይተካሉ ተብለው ተስፋ የሚጣልባቸው አብዛኞቹ ዕጩዎች በመጀመርያው ዙር ጥቃት ተገድለዋል አሉ።

    የኤቢሲ ጋዜጠኛ የሆነው ጆናታን ካርል በማኅበራዊ ሚዲያ ገፁ ላይ ከአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጋር በስልክ በነበረው ቃለ ምልልስ ላይ “አብዛኞቹን እጩዎች በማስወገድ ረገድ ውጤታማ ነበርን” እንዳሉት ጽፏል።

    የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በአሜሪካ እና በእስራኤል የአየር ጥቃት ቅዳሜ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ተገድለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዚህ ቀደም ኢራንን ለመምራት ሦስት ጥሩ አማራጮች መኖራቸውን ተናግረው የነበሩ ቢሆንም ስማቸውን ከመዘርዘር ግን ተቆጥበዋል።

    እሁድ ዕለት የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በኢራን በተፈጸመ ጥቃት ሦስት አሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን እና አምስት ደግሞ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ካረጋገጠ በኋላ "ተጨማሪ" አሜሪካውያን ላይ ጉዳት ሊደርስ እንደሚችል ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል።

  3. ሳይፕረስ ውስጥ የሚገኝ የብሪታኒያ የጦር ሰፈር በኢራን ድሮን ተመታ

    ትናንት ምሽት ሳይፕረስ ውስጥ በሚገኘው የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈር ላይ የድሮን የጥቃት መፈጸሙን የብሪታኒያ መከላከያ ሚኒስቴር ገልጿል።

    በኢራን ድሮን ጥቃት የደረሰበት ‘አርኤኤፍ’ የተባለው የጦር ሰፈር በሳይፕረስ የሚገኝ የብሪታኒያ ሉዓላዊ ግዛት ነው።

    የሳይፕረስ ፕሬዝዳንት ኒኮስ ክርስቶዶውሊደስ፤ በደቡባዊ አገሪቱ ክፍል በሚገኘው የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈር ላይ የደረሰውን የድሮን ጥቃት በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎች ሰጥተዋል።

    እኩለ ሌሊት እንዳለፈ፤ “ሻሄድ ሰው አልባ በራሪ” አክሮቲሪ ውስጥ ከሚገኙ የዩናይትድ ኪንግደም ወታደራዊ ተቋማት ላይ መውደቁን ተናግረዋል። ፕሬዝዳንቱ የጠቀሱት ሻሄድ የኢራን ድሮኖች ናቸው።

    በዚህ ጥቃት “መጠነኛ ቁሳዊ ጉዳት” እንደደረሰ ፕሬዝዳንቱ በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል። ከአውሮፓውያን እና ሌሎች መሪዎች ጋር “በቋሚነት ግንኙነት” እያደረጉ እንደሆነ ገልጸዋል።

    አክለውም ግን ሳይፕረስ “ምንም ዓይነት ወታደራዊ ዘመቻ ውስጥ የመሳተፍ ዕቅድ እንደሌላት” ተናግረዋል።

    የብሪታኒያ መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ “የሠራተኞቻችን እና የቤተሰቦቻቸው ደኅንነት ፍጹም ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው” ብሏል።

    ለጥንቃቄ እርምጃ ሲባልም በጦር ሰፈሩ የሚገኙ የቤተሰብ አባላት ወደ “ከሳይፕረስ ደሴት አቅራቢያ ወደሚገኝ” ስፍራ መዘዋወራቸውን አስታውቋል።

  4. እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ድብደባ 31 ሰዎች ተገደሉ

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት 31 ሰዎች ሲገደሉ 149 ደግሞ ጉዳት እንደ ደረሰባቸው የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የእስራኤል መከላከያ በሄዝቦላህ ላይ “የማጥቃት ዘመቻ” መክፈቱን የገለፀ ሲሆን ይህም ለበርካታ ቀናት ሊቆይ ይችላል ብሏል።

    የእስራኤል መከላከያ አዛዡ ኢያል ዛሚር "በሄዝቦላህ ላይ የማጥቃት ዘመቻ መጀመራችን ነው። በመከላከል ላይ አይደለም ያለነው፤ እያጠቃን ነው” ብለዋል።

    አክለውም “ለበርካታ ቀናት ለሚቀጥል ውጊያ መዘጋጀት አለብን፤ ለብዙ ቀናት። ጠንካራ የመከላከል ዝግጁነት ያስፈልገናል። እንዲሁም ቀጣይነት ላለው ማጥቃት ዝግጁ መሆን አለበን” ብለዋል።

    ኢራን በበርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ዛሬም ቀጥላለች። በባህሬን እና ዱባይ እንዲሁም በኩዌት የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ሠራዊቱ ከሔዝቦላህ ጋር ዳግም ውጊያ መግጠሙን ተከትሎ ወደ ሊባኖስ የእግርኛ ሠራዊት ይሰማራ እንደሆን ተጠይቀው "ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛ ላይ ናቸው" ሲሉ መልሰዋል።

    ሔዝቦላህ እስራኤልን ላይ ጥቃት በመሰንዘሩ "ከባድ ዋጋ ይከፍላል" ሲሉ ተናግረው “ዝግጁ ነን፤በሚገባ ተዘጋጅተናል። ወደ 100,000 የሚጠጉ ተጠባባቂ ወታደሮችን አሰባስበናል፤ በደርዘን የሚቆጠሩ ሻለቃዎችን፣ ብርጌዶችን፣ ዕዞችን፣ የሰሜን ድንበርን ለመከላከል አሰማርተናል፣ እና ለመከላከልም ሆነ ለማጥቃት ለሚደረጉ ሁሉም አማራጮች ተዘጋጅተናል" ብለዋል።

    "የሁኔታ ግምገማዎችን እያካሄድን ነው፣ እና ሁሉም አማራጮች በጠረጴዛ ላይ ናቸው።"

  5. ኢራን በኩዌት እና ኢራቅ ላይ ጥቃት መፈጸሟ ተገለጸ

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ለሦስተኛ ቀን በቀጠሉበት በዛሬው ዕለት ኢራንም በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ባሉ አገራት ላይ ሚሳዔሎችን አስወንጭፋለች።

    ዛሬ ማለዳ በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ጥቃት መፈጸሙ ተገልጿል።

    ኤምባሲው በኩዌት የሚገኙ የአሜሪካ ዜጎች ወደ ኤምባሲው እንዳይመጡ እና በቤታቸው እንዲቆዩ መልዕክት አስተላልፏል።

    በኤምባሲው ድረገጽ ላይ የሰፈረው መልዕክት “ወደ ኤምባሲው እንዳትመጡ” ካለ በኋላ ቤታቸው ውስጥ ደህንነቱ በተጠበቀ ሥፍራ እንዲሆኑ መመሪያ አስተላልፏል።

    አክሎም “መስኮት አካባቢ አትቅረቡ፤ ወደ ውጭ አትውጡ” ሲል በአገሪቱ ለሚኖሩ አሜሪካውያን የደህንነት መልዕክቶችን አስፍሯል።

    ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ትናንት በፈጸመችው ጥቃት በኩዌት አንድ ሰው መገደሉ ተገልጿል። የአሜሪካ አጋር የሆነችው ኩዌት ከኢራን የተተኮሰባትን ሚሳዔል ማክሸፏን አስታውቃለች።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል በበኩሉ በኢራቅ የሚገኙ የደኅንነት ባለሥልጣናትን በመጥቀስ በሰሜናዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኘው በኢርቢል አውሮፕላን ማረፊያ ሦስት የታጠቁ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    በአውሮፕላን ማረፊያው የአሜሪካ ወታደሮች ይገኛሉ ተብሏል።

    ሮይተርስ ሰው አልባ አውሮፕላኖቹ ተመትተው መውደቃቸውን የገለፀው በጦር ሠፈሩ ከፍተኛ ፍንዳታ መሰማቱን የኤኤፍፒ ጋዜጠኛ ከዘገበ በኋላ ነው።

    በሳምንቱ መጨረሻ አሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ማክሸፏን አስታውቃለች።

  6. ሰበር, የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላኖች በኩዌት ተከሰከሱ

    "ዛሬ ጠዋት በርካታ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች ተከስክሰዋል" ሲል የኩዌት የመከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የበረራ አባላቱ "ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸው በሕይወት ተርፈዋል" በማለት ወደ ሆስፒታሎች መወሰዳቸውን መግለጫው አክሎ ገልጿል።

    የኩዌት መከላከያ ሚኒስቴር መግለጫ የበረራ አባላቱ ሁኔታ "የተረጋጋ" መሆኑን አስታውቋል።

    የመከላከያ ሚኒስቴር አክሎም ከአሜሪካ ጋር ስለ "ክስተቱ" እየተነጋገረ መሆኑን እና "የክስተቱን መንስዔዎች" በተመለከተ ምርመራውን እየተካሄደ መሆኑን አስታውቋል።

  7. ዩኬ፣ ፈረንሳይ እና ጀርመን በቀጣናው “ጥቅሞቻችን ለማስጠበቅ እርምጃ ለመውሰድ” ዝግጁ ነን አሉ

    ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ እና ጀርመን በጋራ ባወጡት መግለጫ ኢራን በጎረቤቶቿ ላይ የፈጸመችውን "ያልተመጣጠነ እና የዘፈቀደ የሚሳዔል" ጥቃት አውግዘዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም በበኩሏ አሜሪካ የብሪታኒያን የጦር ሰፈሮች ተጠቅማ የመከላከያ እርምጃ እንድትወስድ ልትፈቅድ መሆኑን አስታውቃለች።

    የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር፣ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እና የጀርመኑ ቻንስለር ፍሪድሪሽ ሜርዝ ኢራን ጥቃት መፈጸሟን እንድታቆም ጠይቀዋል። አገራቱ በመካከለኛው ምሥራቅ ያላቸውን ጥቅሞች ለማስጠበቅ አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

    "የራሳችንን እና በቀጠናው ያሉ አጋሮቻችንን ፍላጎቶች ለመከላከል እርምጃዎችን እንወስዳለን። ይህም የኢራንን ሚሳዔሎች እና ድሮኖች የመተኮስ አቅሟ ከምንጩ የሚያጠፋ አስፈላጊ እና ተመጣጣኝ የመከላከያ እርምጃ ሊሆን ይችላል" ብለዋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ አሜሪካ የአገሪቱን የጦር ሰፈሮች እንድትጠቀም እንደሚፈቅዱ ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ አጋሮቻችን እነርሱን ለመከላከል ተጨማሪ ተግባር እንድናከናውን ጠይቀውናል… በተቀናጀው የመከላከያ ዘመቻ አካል የሆኑ የብሪታኒያ ጄቶች አየር ላይ አሉን…አስቀድሞም በተሳካ ሁኔታም የኢራንን ጥቃቶች አክሽፈዋል” ብለዋል።

    “ነገር ግን ስጋቶቹን ለማስቆም ብቸኛው መንገድ ሚሳዔሎቹን ከምንጫቸው ማጥፋት፤ እዚያው ከማከማቻ ዴፗቸው ወይም ሚሳኤል ለመተኮስ ጥቅም ላይ ከሚውሉት ማስወነጨፊያዎች” ሲሉም ተናግረዋል።

    "ኢራን በመላ ቀጣናው ሚሳዔል እየተኮሰች ንጹሃንን እንዳትገድል፣ የብሪታኒያውያንን ሕይወት አደጋ ላይ እንዳትጥል እና ተሳትፎ የሌላቸውን አገራት እንዳትመታ ለመከላከል የቀረበልንን ጥያቄ ለመቀበል ወስነናል” ሲሉ የአገራቸው አቋም ገልጸዋል።

  8. አሜሪካ በ24 ሰዓታት ውስጥ ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎችን መምታቷን አስታወቀች

    በኢራን ላይ የጥቃት ዘመቻ ከተጀመረ በኋላ ባሉት በመጀመሪያዎቹ 24 ሰዓታት ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎች ኢራን ውስጥ መመታታቸውን የዩናይትድ ስቴትስ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) አስታወቀ።

    ዕዙ ካወጣው የጥቃት ዝርዝር ውስጥ ነጥሎ መቺ ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖች፣ ድሮኖች፣ ተዋጊ ጄቶች እና ፀረ ሚሳዔል ሥርዓቶችን ጨምሮ የአሜሪካ ሠራዊት ጥቅም ላይ ያዋላቸው ጦር መሳሪያዎችንም አካትቷል።

    ማዕከላዊ ዕዙ ዒላማ ከተደረጉት ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎች መካከል የኢራን የማዘዣ እና መቆጣጠሪያ ማዕከላት፣ የባለስቲክ ሚሳዔል ማስወንጨፊያ ቦታዎች እና የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዋና ጽህፈት ቤት ይገኙበታል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ የተፈጸመው ጥቃት “በከፍተኛ ሁኔታ ወሳኝ ውጤትን” አስገኝቷል በማለት የእስራኤል መከላከያ ኃይል የሰጠውን አስተያየት ደግሞታል።

  9. የባሕረ ሰላጤው አገራት በኅብረት ኢራንን አስጠነቀቁ

    የባህረ ሰላጤው ትብብር ምክር ቤት (Gulf Cooperation Council) አባላት እሁድ ዕለት ባደረጉት ስብሰባ፤ ኢራንን በአባል አገራቱ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ምክንያት ስለደረሰው ከፍተኛ ጉዳት መክረዋል። የባሕረ ስላጤው አገራት፤ የኢራን ጥቃት የሲቪሊያን ተቋማትን እና መኖሪያ አካባቢዎችን ጭምር ዒላማ ያደረገ ነው ብለዋል።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ ባህሬን፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ኦማን፣ ኳታር እና ኩዌትን በአባልነት የያዘው ምክር ቤቱ፤ ጥቃቶቹን አውግዟል። ኢራን የአባል አገራቱን ሉዓላዊነት እና ዓለም አቀፍ ሕግን ጥሳለች ሲልም ከስሷል።

    ኢራን ጥቃቷን እንድታቆም በመግለጫው ያሳሰበው ምክር ቤቱ፤ ለንግግር እና ዲፕሎማሲ ቅድሚያ መሰጠት እንዳለበት በአጽንኦት አሳስቧል። ነገር ግን አገራቱ ደኅንነታቸውን ለማስጠበቅ “ሁሉንም አስፈላጊ እርምጃዎች” እንደሚወስዱ ምክር ቤቱ አስጠንቅቋል።

  10. በእስራኤል ጥቃት ቀኑን የጀመሩት የቤይሩት ነዋሪዎች ከተማውን ለቅቀው መውጣት ጀምረዋል

    የሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ነዋሪዎች ሌሊት ዘጠኝ ሰዓት (በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከሌሊቱ 10 ሰዓት) አካባቢ ላይ በመላው ከተማ በተሰማው የእስራኤል ተከታታይ ጥቃቶች በፈጠሩት የፍንዳታ ድምጽ ከተኙበት ነቅተዋል።

    እነዚህ ድምጾች የተሰሙት በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ የሮኬት ጥቃት የተፈጸመባት እስራኤል፤ የቡድኑ ይዞታዎችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት መፈጸም በመጀመሯ ነው።

    ሄዝቦላህ ባወጣው መግለጫ ጥቃቱን የፈጸመው፤ በኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ላይ የተፈጸመው ግድያ የአጸፋ ምላሽ ለመስጠት እንደሆነ አስታውቋል። እርምጃውንም “ሕጋዊ ራስን የመከላከል እርምጃ” ሲል ገልጾታል።

    ሄዝቦላህ፤ “ትክክለኛ ዒላማቸውን የሚመቱ ሮኬቶችን እና በብዛት ተጉዘው ጥቃት የሚያደርሱ ድሮኖችን” በሰሜናዊ እስራኤል በሚገኝ የሚሳዔል መከላከያ ስፍራ ላይ ማስወንጨፉን ገልጿል። ለሄዝቦላህ ጥቃት ምላሽ መስጠት መጀመሩን ያረጋገጠው የእስራኤል ጦርም፤ ጥቃቱ “ሄዝቦላህ በዘመቻው ለመሳተፍ ያሳለፈው ውሳኔ ላይ” የሚፈጸም እንደሆነ አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ፤ “ለእስራኤል መንግሥት ስጋት እንዲጋርጥ እና በሰሜን እስራኤል በሚገኙ ንጹኃን ላይ ጉዳት እንዲያደርስ” እንደማይፈቅድ ጠቅሷል። የእስራኤል ጦር ሊባኖስ ውስጥ ባሉ ከ50 በላይ መንደሮች ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች አካባቢያቸውን ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

    ይህንንም ተከትሎ አገሪቱ ዜጎች መኖሪያቸውን ለቅቀው እየወጡ ነው። ቤይሩት እና ሲዶን ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው በሚወጡበት ወቅት ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ መከሰቱን የሚያሳዩ ምሥሎች ወጥተዋል።

    ከአንድ ዓመት በላይ ቆየው እና እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ ከፍተኛ ጥቃት የፈጸመችበት ውጊያን ለማስቆም በአውሮፓውያኑ 2024 በአሜሪካ አሸማጋይነት በተደረሰ ስምምነት እስራኤል እና ሊባኖስ፤የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማምተው ነበር። ኋላ ላይ ግን ተኩስ አቁሙ ለመጣሱ አንዳቸው ሌላኛቸውን ተጠያቂ አድርገዋል።

    እስራኤል ስምምነቱ ከተፈጸመም በኋላ፤ ከሄዝቦላህ ጋር ግንኙነት አላቸው ባለቻቸው የሊባኖስ ግዛቶች ላይ በየቀኑ በሚባል ደረጃ ጥቃት ስትፈጸም ቆይታለች።

  11. ሰበር, እስራኤል ከ50 በላይ በሚሆኑ መንደሮች የሚኖሩ ሊባኖሳውያን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች

    እስራኤል ጥቃት እንደምትፈጽም በመግለጽ ከ50 በላይ በሆኑ አነስተኛ ከተሞች እና መንደሮች የሚኖሩ ሊባኖሳውያን አካባቢያቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች።

    የእስራኤል ጦር ከለያቸው ከእነዚህ አከባቢዎች ነዋሪዎች ቢያንስ አንድ ኪሎ ሜትር እንዲርቁ አስጠንቅቋል።

    የእስራኤል ጦር ያስተላለፈው ማስጠንቀቂያ “ለራሳችሁ ደህንነት ሲባል ቤታችሁን በአስቸኳይ ለቅቃችሁ፣ ቢያንስ ከመንደራችሁ 1000 ሜትሮች ወደ ግልጽ ስፍራ እንድትሄዱ ይሁን" ይላል።

    “ማንኛውም የሄዝቦላህ አባላት፣ ተቋማት ወይንም ወታደራዊ ቁሳቁሶች ቅርብ የሆነ ሰው ሕይወቱን ለአደጋ ያጋልጣል” በማለት መንደሮቹን በዝርዝር አስፍሯል።

    የእስራኤል ጦርን ማስጠንቀቂያ የሰሙ ሊባኖሳውያን ከተጠቀሱት አካባቢዎች ለቅቀው እየወጡ ነው።

  12. የአሜሪካ፣ እስራኤል እና ኢራን ጦርነት የሦስተኛ ቀን ዋና ዋና ክስተቶች

    አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የጀመሩት ጦርነት ሦስተኛ ቀኑን አስቆጥሯል፤ ሁሉም ወገኖች ከፍተኛ የአየር ድብደባ መፈጸም ቀጥለዋል። በጦርነቱ ሦስተኛ ቀን ምን ተከሰተ?

    • ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ የተከፈተው “የማጥቃት ዘመቻ” “ሁሉም ግቦቻችን እስኪሳኩ ድረስ” ይቀጥላሉ ሲሉ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት ገልጸዋል።
    • የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በኢራን በተፈጸመ ጥቃት ሦስት አሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን እና አምስት ደግሞ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ካረጋገጠ በኋላ "ተጨማሪ" አሜሪካውያን ላይ ጉዳት ሊደርስ እንደሚችል ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል።
    • ሰኞ ማለዳ ላይ ሄዝቦላህ ወደ እስራኤል ሮኬቶችን መተኮሱን ተከትሎ፤ ቴል አቪቭ የቡድኑ ዒላማዎች ናቸው ባለቻቸው በሊባኖስ የሚገኙ አካባቢዎች ላይ ላይ ጥቃት መሰንዘር ጀመራለች።
    • አሜሪካ እና እስራኤል፤ በኢራን በሚገኝ የሴቶች ትምህርት ቤት ላይ በፈጸሙት ጥቃት ቢያንስ 153 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ መንግሥት ገልጿል። የኢራን ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን ድርጊቱን "አረመኔያዊ " ሲሉ ጠርተውታል።
    • እስራኤል ከኢራን የተተኮሱ ሚሳዔሎች ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎችን መግደላቸውን አሳውቃለች። ይህ ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በእስራኤል ላይ የደረሰው ከፍተኛ የሟቾች ቁጥር ነው።
    • የተባበሩት አረብ ኤምሬትቶች ቅዳሜ ዕለት ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ሰዎች መሞታቸውን አስታውቃለች ፤ በባህሬን ፣ በኢራቅ ኤርቢል እና በዮርዳኖስ ከፍተኛ ፍንዳታዎችም መከሰታቸው ተገልጿል።
    • ሰኞ ጠዋት በእስያ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል።
    • የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር አሜሪካ የዩኬ ወታደራዊ ሰፈሮች በመጠቀም ጥቃቶችን እንድትፈጽም መፍቀዳቸውን አስታውቀዋል። ነገር ግን "አሁን የማጠቃት እርምጃውን አልተቀላቀልንም" ሲሉ ለሕዝባቸው ተናግረዋል።
    • በሳይፕረስ የሚገኘው የዩኬ የጦር ሠፈር በቆጵሮስ በሚገኝ አንድ የጦር ሰፈር ላይ ለተፈጸመ የድሮን ጥቃት ምላሽ መስጠቱን አረጋግጧል።