ከኢራን ጋር ግንኙነት ያላቸው አራት መርከቦች ከአሜሪካ እገዳ በኋላ በሆርሙዝ ወሽመጥ አለፉ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካ በሆርሙዝ ላይ የጣለችው እገዳ ተግባራዊ መሆን እንደጀመረ ቢነገረም ከኢራን ጋር ግንኙነተ ያላቸው አራት መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፋቸውን ቢቢሲ ቬሪፋይ የተነተነው የመርከቦች ጉዞ የትክክል መረጃ አሳየ።
‘ማሪን ትራፊክ’ የተሰኘው መርከቦች ጉዞ መከታተያ ድረ ገጽ መረጃ እንደሚመለክተው ከአራቱ ውስጥ ሁለቱ መርከቦች የኢራን ወደቦችን ጎብኝተው ነበር።
'ክርስቲያና' የተሰኘችው የጭነት መርከብ ወደ ኢራን ባንዳር ኢማን ኮሜኒ ወደብ ተጉዛ የነበረ ሲሆን ሰኞ ዕለት አሜሪካ እገዳ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ በኋላ ደግሞ በወሽመጡ በኩል ማለፏን መረጃው ያሳያል።
ከኢራን ጋር በሚያደርገው የንግድ እንቅስቃሴ ምክንያት በአሜሪካ ማዕቀብ የተጣለበት ‘ሪች ስቴሪ’ የተባለ ሌላ መርከብ ደግሞ ትናንት ሌሊት በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሻርጃ በመነሳት በሆርሙዝ በኩል ተጉዟል። መርከቡ መዳረሻው ቻይና እንደሆነ ሮይተርስ ዘግቧል።
በወሽመጡ በኩል ያለፈው ሌላኛው ነዳጅ ጫኝ መርከብ ‘ሙርሊኪሻን’ የሚል ስያሜ የተሰጠው ነው። ይህም መርከብ ከኢራን ጋር ባለው ንግድ ምክንያት አሜሪካ ማዕቀብ ጥላበታለች።
መርከቡ ከቻይና ላንሻን እንደተነሳ እና ሌሊቱን በሆርሙዝ በኩል እንዳለፈ መረጃው አሳይቷል። እንደ ማሪን ትራፊክ ከሆነ፤ መርከቡ የታየበት የመጨረሻው ስፍራ ከኢራን ቃሽም ደሴት በስተምስራቅ ያለ አካባቢ ነው።
‘ኤልፒስ’ የተባለ ሌላ ነዳጅ ጫኝ መርከብም ማክሰኞ ዕለት ከኢራኑ ቡሼህር ወደብ ተነስቶ በወሽመጡ በኩል ማለፉን የጉዞ መከታተያው ድረ ገጽ መረጃ ይጠቁማል። መዳረሻው ያልታወቀው ይህ መርከብም በአሜሪካ ማዕቀብ ተጥሎበታል።
እነዚህ መርከቦች አድራሻቸውን ለመደበቅ ሲሉ የሚገኙበትን ቦታ በተመለከተ የተሳሳተ መረጃ አሰራጭተው ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።
የአሜሪካ ጦር ከትናንት ሰኞ 11 ሰዓት ጀምሮ “ወደ ኢራን ወደቦች ለመግባት እና ለመውጣት የሚደረጉ የባሕር ጉዞዎችን በሙሉ” እንደሚያግድ አስታውቆ ነበር።
"እገዳው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ወደ ኢራን ወይም ከ[ኢራን] ወዳልሆኑ መዳረሻዎች የሚደረጉ ገለልተኛ የትራንዚት ጉዞዎችን" ግን እንደማያስቆም ገልጾ ነበር።



















