የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ከትናንት ጀምሮ በሆርሙዝ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ እንቅስቃሴን ካገደ በኋላ በአሜሪካ ማዕቀብ የተጣለበት አንድ የቻይና ነዳጅ ጫኝ መርከብ
በወሽመጡ በኩል ማለፉን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።
መዳረሻው
ቻይና የሆነው ይህ መርከብ ለመጨረሻ ጊዜ ቆሞ የበረው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ወደብ ላይ እንደነበረ ቢቢሲ የተመለከታቸው መረጃዎች
አሳይተዋል።
“ሪች
ስቴሪ” የተሰኘው ይህ ነዳጅ ጫኝ የአሜሪካ እገዳ ትናንት 11 ሰዓት ላይ ከተጀመረ በኋላ በወሽመጡ በኩል በማለፍ የፋርስ ባሕረ
ሰላጤን ቀዝፎ የሄደ መርከብ መሆኑን የባሕር ጉዞ መከታተያ ድረ ገጾች አሳይተዋል ተብሏል።
እንደ
ሮይተርስ ዘገባ የመርከቡ ባለቤት “ሻንዳይ ዡአንረን ሺፒንግ” የተባለ እና ከኢራን ጋር በሚፈጽመው ንግድ ምክንያት በአሜሪካ ማዕቀብ
የተጣለበት ኩባንያ ነው።
ፕሬዝዳንት
ዶናልድ ትራምፕ እሁድ ዕለት ባስተላለፉት መልዕክት “ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ለመግባት ወይም ከዚያ ለመውጣት የሚሞክር ማንኛውም እና
ሁሉም መርከቦች” በአሜሪካ ባሕር ኃይል እንደሚታገዱ ገልጸው ነበር።
ሰኞ
ዕለት ደግሞ እገዳው የሚተገበረው “ወደ ኢራን ወደቦች በሚገቡ እና በሚወጡ” መርከቦች ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
የአሜሪካ
ማዕከላዊ ዕዝም በተመሳሳይ “ወደ ኢራን ወደቦች ለመግባት እና ለመውጣት የሚደረጉ ሁሉም የባሕር ላይ ጉዞዎች” እንደሚታገዱ አስታውቋል።
ይሁን
እንጂ "እገዳው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ወደ ኢራን ወይም ከ[ኢራን] ወዳልሆኑ መዳረሻዎች የሚደረጉ ገለልተኛ የትራንዚት
ጉዞዎችን አያስቆምም" ብሏል።
ቢቢሲ
ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ እገዳው ሰኞ 11 ሰዓት ላይ ተግባራዊ መሆን ከመጀመሩ አስቀድሞ ባሉት ሰዓታት አራት መርከቦች
በወሽመጡ በኩል አልፈዋል።
‘ማሪን ትራፊክ’ የተሰኘው የባሕር ጉዞ መከታተያ ድረ ገጽ መረጃ እንደሚያሳየው አራቱም የጭነት መርከቦች
ናቸው። ምናልባትም ነዳጅ፣ ጋዝ ወይም ኬሚካል ጭነው እንደሚሆን ተገምቷል።
ማክሰኞ
ዕለት ጉዞ ያደረገው ብቸኛ መርከብ ‘ሪች ስቴሪ’ ነው። ይህ መርከብ ለመጨረሻ ጊዜ ቆሞ የነበረው በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ወደብ እንደሆነ እና መዳረሻውን ቻይና እንዳደረገ የ‘ማሪን ትራፊክ’ መረጃ ያሳያል።
እንደ
ሮይተርስ ዘገባ በዚህ መርከብ ላይ ያሉት የቻይና የባሕር ሠራተኞች ናቸው።
በአሜሪካ
ማዕቀብ የተጣለበት ሌላ መርከብም ወደ ወሽመጡ ማምራቱን የዜና ወኪሉ ‘ኤልኤስኢጂ’ ከተሰኘው የባሕር ጉዞ መከታተያ ድረ ገጽ መመልከቱን
ጠቅሷል።
ከዚህ
ቀደም የሩሲያ እና የኢራን ነዳጅን በማጓጓዝ የሚታወቀው ይህ ሁለተኛ መርከብ፤ ሐሙስ ዕለት ኢራቅ ደርሶ ነዳጅ እንደሚጭን ይጠበቃል ተብሏል።