የዩኬ እና ኖርዌይ ፖለቲከኞችን ያናወጠው የወሲብ ወንጀለኛው ኤፕስቲን ሰነድ

የፎቶው ባለመብት, Visionhaus/Getty Images
የወሲብ ወንጀለኛው ጄፍሪ ኤፕስቲን ተጨማሪ ሰነዶች ይፋ መሆናቸውን ተከትሎ የዩናይትድ ኪንግደም የሕዝብ እንደራሴ ሎርድ ፒተር ማንደልሰን ከሌበር ፓርቲ ለቅቀዋል።
ከኤፕስቲን ጋር ግንኙነት እንደነበራቸው ሰነዶቹ መጠቆማቸውን ተከትሎ "ተጨማሪ ሀፍረት ላለመፍጠር" በሚል ከፓርቲው ራሳቸውን እዳገለሉ ገልጸዋል።
በሌላ በኩል የኖርዌይ ልዕልት አልጋ ወራሽ ሜቴ-ማሪት ስማቸው ከመቶ ጊዜ በላይ በኤፕስቲን ሰነዶች ውስጥ መጠቀሱን ተከትሎ ድርጊታቸው "የተሳተ አካሄድ ነበር" ብለዋል።
የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆንስ ጋር ስቶሬም ከልዕልት አልጋ ወራሿ ጋር እንደሚስማሙ ገልጸዋል።
ልዕልት አልጋ ወራሽ ሜቴ-ማሪት እአአ ከ2011-2014 ባሉት ዓመታት ውስጥ ከኤፕስቲን ጋር በተያያዘ ከመቶ ጊዜ በላይ ስማቸው መነሳቱን የአሜሪካ የፍትሕ መሥሪያ ቤት ይፋ ያደረጋቸው ሰነዶች ይጠቁማሉ።
የልዕልት አልጋ ወራሿ የ38 ዓመት ልጅ ማሪየስ ቦርግ ሆይቢ፤ በመድፈር እና ጥቃት በማድረስ ወንጀሎች በተከሰሰበት ወቅት የኤፕስቲን ሰነዶች ይፋ መሆን ንጉሣዊ ቤተሰቡን የበለጠ ማጋለጡ ተገልጿል።

የፎቶው ባለመብት, PA Media
ይፋ በተደረጉት ሰነዶች ውስጥ ስማቸው የተጠቀሰው የዩኬ የሕዝብ እንደራሴ ሎርድ ፒተር ማንደልሰን አምና ከአሜሪካ አምባሳደርነታቸው የተነሱትም ከኤፕስቲን ጋር በነበራቸው ትስስር ነው።
ኤፕስቲን እአአ ከ2003 እስከ 2004 በሦስት የተለያዩ አጋጣሚዎች ለሎርድ ማንደልሰን 75,000 ዶላር መስጠቱ ተገልጿል።
ሎርድ ማንደልሰን ለሌበር ፓርቲ ዋና ጸሐፊ በላኩት ደብዳቤ "ከኤፕስቲን ጋር የሚያገናኙኝ ተጨማሪ ሰነዶች ይፋ ወጥተዋል። አዝናለሁ፤ ይጸጽተኛልም። ከ20 ዓመት በፊት ገንዘብ እንደሰጠኝ ተገልጿል። ይሄንን አላስታውስም፤ እውነተኛ ነው ብዬም አላምንም" ብለዋል።
"ሆኖም ተጨማሪ ሀፍረት ላለመፍጠር ከሌበር ፓርቲ አባልነቴ ለቅቄያለሁ። በዚህ አጋጣሚ ድምጻቸው ከዓመታት በፊት መሰማት ለነበረበት ሴቶች ያለኝን ሐዘኔታ እገልጻለሁ" ሲሉም አክለዋል።
የኤፕስቲን ሰነዶች ትክክለኛ መሆናቸውን እርግጠኛ እንዳልሆኑ ከዚህ ቀደም የተናገሩት ሎርድ ማንደልሰን ከኤፕስቲን ጋር እንደሚተዋወቁም አላመኑም ነበር።
የሌበር ፓርቲ አባል ጎርደን ሜኬት ለቢቢሲ እንደተናገሩት፤ ሎርድ ማንደልሰን ከፓርቲው መልቀቃቸው "ትክክለኛ ውሳኔ" ነው።
በሌላ በኩል የኖርዌይ ልዕልት አልጋ ወራሽ ሜቴ-ማሪት ከኤፕስቲን ጋር የተለዋወጧቸው ኢሜሎች ይፋ መውጣታቸውን ተከትሎ በኖርዌይ ፖለቲከኞች ዘንድ ዋነኛ መነጋገሪያ ሆኗል።
"ድርጊቴ የተሳሳተ ነበር። ከኤፕስቲን ጋር ማንኛውንም ግንኙነት በማድረጌ ተጸጽቻለሁ፤ አሳፋሪ ነው" ብለዋል።
ኤፕስቲን ብዝበዛ ላደረሰባቸው ተጎጂዎች "ጥልቅ ሐዘኔን እገልጻለሁ፤ ከጎናቸውም እቆማለሁ" ሲሉም ተናግረዋል።
የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ልዕልት አልጋ ወራሿ መሳሳታቸውን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የንጉሣዊ ቤተሰቡ ላይ ትችት መሰንዘራቸው የተለመደ አይደለም።
የቀድሞው የኖርዌይ ጠቅላይ ሚኒስር ቶርቦጃን ጃግላንድ በኤፕስቲን የግል ደሴት የቤተሰብ ጉብኝት ለማድረግ አቅደው እንደነበር አዲስ የወጡት ሰነዶች ጠቁመዋል።
ከጠቅላይ ሚኒስትር ጆንስ ጋር በተያያዘም አስተያየት የሰጡት የአሁኑ መሪ ስቶሬ፤ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር "ተሳስተው ነበር" ብለዋል።















