የሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የቀብር ሥነ ሥርዓት ታላላቅ የዓለም መሪዎች በተገኙበት ተፈጸመ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ የቀብር ሥነ ሥርዓት ከዓለም ዙሪያ የመጡ እንግዶች እና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሐዘንተኞች በተገኙበት ቫቲካን ውስጥ ተፈጸመ።
የበርካታ የዓለም አገራት መሪ ፖለቲከኞች፣ ንጉሣውያን፣ ታዋቂ ሰዎች እና 400 ሺህ የሚደርሱ ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ እና በቫቲካን ጎዳናዎች ላይ በመውጣት በጳጳሱ የመጨረሻ ስንብት ላይ ተሳትፈዋል።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ደማቁ እና በካቶሊክ ዕምነት ባሕል እንዲሁም የፀሎት ሥርዓት የታጀበውን የጳጳሱን የቀብር ሥነ ሥርዓት የመሩት ካርዲናል ቻምበርሌይን ኬቪን ፋረል ናቸው።
በዓለም ዙሪያ ከ1 ነጥብ አራት ቢሊዮን በላይ ተከታይ ያላት የካቶሊክ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊ መሪ ሆነው ከ10 ዓመታት በላይ በመንበራቸው ላይ የቆዩት ፖፕ ፍራንሲስ ለስደተኞች፣ ለተጨቆኑ እና ለተፈጥሮ አካባቢ ያላቸው ተቆርቋሪነት በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ወቅት ጎልቶ ተሰምቷል።

የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE/REX/Shutterstock
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ አገራት ለስደተኞች መጠጊያ በመሆን እንክብካቤ እንዲያደርጉ ከመወትወታቸው ባሻገር ድጋፍ እንዲያገኙ እና እንዲጽናኑ በግላቸው በርካታ ነገሮች ማድረጋቸው ይነገራል።
በተጨማሪም በዓለም ዙሪያ ሰላም እንዲሰፍን ጦርነቶችን ለማስቆም ለድርድር ጥሪ በማድረግ እንዲሁም የዓለም የአየር ሁኔታ ለውጥ ትኩረት እንዲሰጠው ሲጥሩ ቆይተዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ጣሊያናዊው ካርዲናል ጂዮቫኒ ባቲስታ በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ወቅት ባደረጉት ንግግር "ለሰው ካላቸው ፍቅር እና በዘመናችን ለገጠሙን ፈተናዎች ካላቸው ጥልቅ ግንዛቤ የተነሳ ፖፕ ፍራንሲስ በዚህ ሰዓት ጭንቀታችንን፣ ሰቆቃዎችን እና ተስፋችንን ይጋራሉ" በማለት ተናግረዋል።
ፖፕ ፍራንሲስ በሕይወት ሳሉ የቀብር ቦታቸው ቀለል ባለ ሁኔታ የተዘጋጀ እንዲሆን እና በስፍራው "ፍራንሲስ" የሚለው የጵጵስና ስማቸው ብቻ እንዲሰፍር ጠይቀው ነበር።

የፎቶው ባለመብት, EPA/Vatican
ቅዳሜ ሚያዝያ 18/2017 ዓ.ም. ከምሳ ሰዓት በኋላ የተጠናቀቀውን የቀብር ሥነ ሥርዓት ተከትሎ የውጭ አገራት መሪዎች ከሮም በመውጣት ወደ የመጡበት ሲመለሱ፣ ሐዘንተኞች እና ለሐይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት የመጡ ሰዎች ባቫቲካን ይቆያሉ።
ከጳጳሱ ሕልፈት በኋላ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ዋነኛ ሥራ የነበረው ለርዕሳነ ሊቀ ጳጳሱ የቀብር ሥነ ሥርዓት ዝግጅት ማድረግ እና ቀብሩን መፈጸም የነበረ ሲሆን፣ ከዚህ በኋላ ደግሞ ለዘጠኝ ቀናት የሚቆይ የሐዘን ሥነ ሥርዓት ይኖራል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ከቀብር ዕለት ጀምሮ የሚካሄደው እና ለዘጠኝ ቀናት የሚቆየው የሐዘን ሥርዓት 'ኒቬምዲያሌስ' የሚባል ሲሆን፣ በየዕለቱም ጳጳሱ የሚዘከሩበት በርካታ ሕዝብ የሚሳተፍበት የፀሎት ሥነ ሥርዓት ይኖራል።
የጳጳሱ ሥርዓተ ቀብር ከተፈጸመ በኋላ በቀጣይ የካቶሊኩ ዓለም ዋነኛ ትኩረት የሚሆነው የፖፕ ፍራንሲስን ቦታ ተረክበው ታላቋን ቤተክርስቲያን የሚመሩ ተተኪን የመሰየም ሂደት ነው።

የፎቶው ባለመብት, AFP
ለዚህም ከዓለም ዙሪያ በቫቲካን ሲቲ የሚሰባሰቡት ካርዲናሎች ተለይተው የሚያካሂዱት ሥነ ሥርዓት በእያንዳንዱ ካቶሊክ ተጠባቂ ነው።
ነገር ግን የጳጳሱን ምርጫ በምሥጢር የሚያካሂዱት ካርዲናሎች ለምርጫው የሚቀመጡበትን ቀን እስካሁን አላሳወቁም። በተለምዶው ግን ይህ ስብሰባ ጳጳሱ ካረፉበት ቀን በኋላ ከ15 እስከ 20 ቀናት ባሉት ጊዜያት ሊካሄድ ይችላል።















