ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በትግራይ የታሰሩ ሰላማዊ ሰልፈኞች እንዲፈቱ አምነስቲ ጠየቀ
በትግራይ ጥያቄያቸውን በአደባባይ ያሰሙ ሰላማዊ ሰልፈኞች መታሰር እና ድብደባ ደርሶባቸዋል የሚሉ ሪፖርቶች እንዳሳሰቡት ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ አስታወቀ።
ለሁለት ዓመት ከዘለቀው ደም አፋሳሽ ጦርነት ጋር ተያይዞ የተፈጸሙ ጥሰቶች ፍትህ እና ተጠያቂነትን ጨምሮ 38 ጥያቄዎችን ይዘው ለሰላማዊ ሰልፍ የወጡ ነዋሪዎች እስር፣ ድብደባ እና ማስፈራራት እንደደረሰባቸው አምነስቲ ትናንት ጳጉሜ 3/ 2015 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ አስፍሯል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ ባለስልጣናት ከማክሰኞ ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኙ ሰላማዊ ሰልፈኞችንም በአስቸኳይ እንዲፈቱ አምነስቲ ጠይቋል።
ከክልሉ ባለስልጣናት ፍቃድ ያላገኘው የአደባባይ ሰልፍ መካሄድን ተከትሎ የጸጥታ ኃይሎች ሰልፉን በኃይል ለመበተን እንደሞከሩና በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎችም እንደታሰሩ ቢቢሲ ከነዋሪዎች ሰምቷል።
ከሰልፈኞቹ በተጨማሪም የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች፣ የመቀለ ዩኒቨርስቲ መምህራን እና ሌሎች ማኅበረሰብ አንቂዎች እና አባላትም ለእስር መዳረጋቸውም ተዘግቧል።
አምነስቲ በትናንትናው መግለጫው በሰልፈኞቹ ላይ ጥሰት የፈጸሙ የጸጥታ አካላት ላይ ምርመራ እንዲከፈትም ለባለስልጣናቱ ጥያቄ አቅርቧል።
“የትግራይ ክልል ጊዜያዊ ባለስልጣናት የክልሉ ነዋሪዎች ሃሳባቸውን በነጻነት የመግለጽ እና የመደራጀት መብታቸውን ሊያከብሩ ይገባል። ይህ በተለይም ከአውዳሚ ግጭት እየወጣ ላለ ክልል መሰረታዊ ነው” ሲልም በመግለጫው አስፍሯል።
በትግራይ ስር ነቀል ለውጥ እንዲመጣ በተቃዋሚ ፓርቲዎቹ ሳልሳይ ወያነ፣ ባይቶና እና የትግራይ ነጻነት ፓርቲዎች ሰልፍ ለማድረግ ያቀረቡት ጥያቄ በጊዜያዊ አስተዳደሩ ውድቅ ተደርጎ ነበር።
ጊዜያዊ አስተዳዳሩ የጸጥታ እና ደህንነት ጥያቄዎችን ጨምሮ የአደባባይ ሰልፍ የማድረጊያ “ትክክለኛ ጊዜ” አይደለም ብሎ ነበር።
ሰላማዊ ሰልፉ ከባለስልጣናቱ ፍቃድ ባያገኝም በተያዘለት ቀን መደረጉን ተከትሎም ነው የጸጥታ ኃይሎች ድብደባን ጨምሮ ኃይልን በመጠቀም ለመበተን የሞከሩት።
በተቃዋሚ ፓርቲዎች ለሶስት ቀናት የተጠራውን የአደባባይ ተቃውሞም ተከትሎ በመቀለ የንግድ እንቅስቃሴ ቆሞ ነበር።
የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ረዳ ከሰሞኑ በሰጡት መግለጫ፤ “ሰላማዊ ሰልፍ መፍቀድ ወይም መከልከል የሚባል ነገር እንደሌለ ከፓርቲዎቹ አመራሮች ጋር ተስማምተናል። ሆኖም የሰልፉን ቦታ መወሰን የፓርቲዎች ኃላፊነት አይደለም” ብለዋል።
“ሕጋዊ መሠረታቸውን በተመለከተ ሙግት ውስጥ ላለመግባት ተውነው እንጂ፣ እነዚህ ፓርቲዎች እኮ አሁን ባለው ምርጫ ቦርድ ሕግ መሠረት የቤት ውስጥ ስብሰባ ከመጥራት በስተቀር በአደባባይ ሰልፍ የመጥራት መብትም የላቸውም" ብለዋል።