ጀርመን እና ፈረንሳይ ትራምፕ ግሪንላንድን 'ለመጠቅለል' ማስፈራራታቸውን እንዲያቆሙ አስጠነቀቁ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ተመራጩ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የዴንማርክን የራስ ገዝ ግዛት ለመጠቅለል ወታደራዊ ሃይል ጭምር ሊጠቀሙ እንደሚችሉ መግለጻቸውን ተከትሎ ግሪንላንድን ማስፈራራታቸውን እንዲያቆሙ ጀርመን እና ፈረንሳይ አስጠነቀቁ።
የጀርመኑ ቻንስለር ኦላፍ ሾልዝ "ድንበር ያለመጣስ መርህ... ለሁሉም አገር ይተገበራል" ብለዋል።
የፈረንሳዩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዣን ኖኤል ባሮ በበኩላቸው "የአውሮፓ ህብረት ሌሎች የዓለም አገራት ሉዓላዊ ድንበሩን እንዲያጠቁ እንደማይፈቅድ ምንም ጥርጥር የለውም" ብለዋል።
ትራምፕ የአርክቲክ ደሴቷ ለአገር እና ለኢኮኖሚ ደህንነት "ወሳኝ" እንደሆነች በመግለጽ ግሪንላንድን የመጠቅለል ፍላጎታቸውን በድጋሚ ማክሰኞ ዕለትም ገልጸዋል።
በመጀመሪያው የፕሬዚዳንትነት የስልጣን ዘመናቸው ሃሳቡን ካነሱ በኋላ ግሪንላንድን የመግዛት ፍላጎታቸውን ደጋግመው አሳውቀዋል።
የረዥም ጊዜ የአሜሪካ አጋር የሆነችው ዴንማርክ በበኩሏ ግሪንላንድ ለሽያጭ እንደማትቀርብ እና የነዋሪዎቿ እንደሆነ በግልጽ ተናግራለች።
የግሪንላንድ ጠቅላይ ሚንስትር ሙቴ ኤጌዴ ከዴንማርክ ነፃ ለመሆን እየሠሩ ቢሆንም እርሳቸውም ግዛቲቱ እንደማትሸት ግልጽ አድርገዋል። ረቡዕ ዕለት ኮፐንሃገንን እየጎበኙ ነበር።
ቻንስለር ሾልዝ ከቀጣዩ የአሜሪካ አስተዳደር የሚሰሙ መግለጫዎች "የተወሰነ ያለመረዳት ነገር" አለ ብለዋል።
"በምስራቅም ሆነ በምዕራብ የማይጣስ የድንበር መርህ በሁሉም አገራት ላይ ይተገበራል።"
ዴንማርክ፣ ጀርመን እና ፈረንሳይ በዩናይትድ ስቴትስ የሚመራው የኔቶ ጥምረት አባላት ናቸው።
"ኔቶ ለመከላከያችን በጣም አስፈላጊው ተቋም ሲሆን ግንኙነታችን ማዕከልም ነው" ሲሉ ሾልዝ አጽንኦት ሰጥተዋል።
ዣን ኖኤል ባሮ ለፈረንሣዩ ኢንተር ሬድዮ "ዩናይትድ ስቴትስ ግሪንላንድን ትወርራለች ብዬ እንደማስብ ከጠየከኝ መልሴ አታደርገውም የሚል ነው" ሲሉ ረቡዕ ዕለት ተናግረዋል።
"አቅም ያለው ህልውናውን የሚያስጠብቅበት ዘመን ውስጥ ገብተናል ወይ ከተባለ ደግሞ መልሱ አዎ ነው" ብለዋል።
"ስለዚህ ራሳችንን እንድንሸማቀቅ እና በጭንቀት እንድንሸነፍ መፍቀድ ግን የለብንም። መንቃት አለብን፤ ጥንካሬያችንን ማጎልበት አለብን" ሲሉ የፈረንሳዩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አክለዋል።
ጀርመን እና ፈረንሳይ ሁለቱ የአውሮፓ ህብረት መሪ አባላት ሲሆኑ ብዙ ጊዜም እንደህብረቱ ዋና አንቀሳቃሽ ኃይል ተደርገው ይገለጻሉ።
የአውሮፓ ህብረት ማንኛውንም ጥቃት ሊከላከል የሚችለው እንዴት እንደሆነ መገመት ግን አስቸጋሪ ነው። የራሱ የሆነ የመከላከል አቅም የሌለው ሲሆን ከ27ቱ አብዛኛዎቹ አባል አገራት የኔቶ አካል ናቸው።
ትራምፕ ይህንን የተናገሩት በፍሎሪዳ በሚገኘው ማር አ ላጎ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ነው። ጥር 20 ደግሞ ለሁለተኛ የፕሬዚዳንትነት ዘመናቸው ቃለ መሃላ ይፈጽማሉ።
ግሪንላንድን ወይም የፓናማ ሰርጥን ለመቆጣጠር ወታደራዊ ወይም ኢኮኖሚያዊ ኃይልን ይጠቀሙ እንደሆን ተጠይቀው "ከሁለቱ አንዱ ነው ብዬ ላረጋግጥ አልችልም" ሲሉ መልሰዋል።
"ለኢኮኖሚያዊ ደህንነት ስንል ግን ሁለቱንም እንፈልጋቸዋለን ማለት እችላለሁ።"
ግሪንላንድ ከቀዝቃዛው ጦርነት ጀምሮ የዩናይትድ ስቴትስ ራዳር ማዕከል ሆና የቆየች ሲሆን ለዋሽንግተንም ወሳኝ ስትራቴጅያዊ ጠቀሜታ አላት።
"በየቦታው የሚገኙትን" የቻይና እና የሩሲያ መርከቦችን ለመከታተል ለሚደረገው ወታደራዊ ጥረት ደሴቲቱ ወሳኝ እንደሆነች ትራምፕ ጠቁመዋል።
"ነጻውን ዓለም ስለመጠበቅ ነው የማወራው" ሲሉም ለጋዜጠኞቹ ተናግረዋል።
የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜት ፍሬደሪክሰን ማክሰኞ ዕለት ለዴንማርክ ቲቪ እንደተናገሩት "ግሪንላንድ የነዋሪዎቿ ናት"፤ የወደፊት ዕጣ ፈንታዋ የሚወስነውም በህዝቦቿ ብቻ ነው።
ዴንማርክ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር የቅርብ ትብብር እንደሚያስፈልጋት ግን አልሸሸጉም።
የግሪንላንድ የፓርላማ አባል ኩኖ ፌንከር ለቢቢሲ እንደተናገሩት ከሆነ ህዝቡ ከትራምፕ "አንዳንድ ድፍረት የተሞላባቸውን ውሳኔዎች" እንደሚሰማ ሲዘጋጅ እንደነበር ጠቅሰው፤ የደሴቲቱ "ሉዓላዊነት እና የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ጉዳይ ግን ለድርድር የማይቀርብ ነው" ብለዋል።
የግሪንላንድ አስተዳደር ጥምረት አካል የሆነው የሲዩሙት ፓርቲ አባሉ ፌንከር እንደገለጹት ከሆነ የአካባቢው ባለስልጣናት "ከዩናይትድ ስቴትስ እና ከሌሎች አገራት ጋር ገንቢ ውይይት እና የጋራ ተጠቃሚነት" ይቀበላሉ።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ግሪንላንድ 57 ሺህ ህዝብ ያላት እና ሰፊ ነጻነት ያለው የራስ ገዝ አስተዳደር ቢኖራትም ኢኮኖሚዋ በአብዛኛው ከኮፐንሃገን በሚደረግ ድጎማ ላይ የተመሰረተ ሲሆን የዴንማርክ ግዛት አካል ናት።
ባትሪዎችን እና ከፍተኛ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎችን በማምረት ረገድ ወሳኝ የሆኑ ብርቅዬ የሆኑ የአንዳንድ ማዕድናት ክምችት አሏት።
በግሪንላንድ ዋና ከተማ ኑክ ሲዘግብ የነበረው የዴንማርክ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋዜጠኛው ስቴፈን ክሬትስ እንደተናገረው ከሆነ አብዛኛዎቹ ያናገራቸው ሰዎች ትራምፕ ግዛቲቱን ለመቆጣጠር ወታደራዊ ኃይል አንጠቀምም ማለታቸው አስደንግጧቸዋል።
በግሪንላንድ የሚኖሩ አብዛኛዎቹ ሰዎች ነጻ አገር የመመስረት ተስፋ ቢኖራቸውም፤ አሁን ዴንማርክ እንደምታደርገው ህዝባዊ አገልግሎትን፣ መከላከያን እና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍን የሚሰጥ አጋር እንደሚያስፈልጋት ያምናሉ።
"ደሴቲቱ እንደ ዩናይትድ ስቴት ላሉ የውጭ ሃይሎች ቅኝ ግዛት እንድትሆን እያለመ የሚገኝ የግሪንላንድ ሰው ገና አላገኘሁም።"
የዴንማርክ መንግስት ከትራምፕ ጋር የሚነሱትን ማንኛውንም ግጭቶች "ለማቃለል" ቢሞክርም "ከጀርባ ግን ይህ ግጭት በዘመናዊው ታሪክ ለዴንማርክ ትልቁ ዓለም አቀፍ ቀውስ ሊሆን እንደሚችል ግንዛቤ አለኝ" ሲል ክሬትስ ለቢቢሲ ተናግሯል።
የተመራጩ የፕሬዚዳንት ልጅ ዶናልድ ትራምፕ ጁኒየር ማክሰኞ ዕለት ወደ ግሪንላንድ በመጓዝ ለአጭር ጊዜ የቆየ ጉብኝት ያደረገ ሲሆን ከሰዎች ጋር ለመነጋገር ያደረገው "የግል ጉዞ" መሆኑን ገልጿል።
በግሪንላንድ ትራምፕን የሚደገፍ ኮፍያ ካጠለቁ ሰዎች ጋር ባር ውስጥ ፎቶ ተነስቶ ለጥፏል።












