የአል-ሻባብ ቁልፍ ሰው ሶማሊያ ውስጥ በአየር ድብደባ ተገደለ

የፎቶው ባለመብት, AFP
የአል-ሻባብ ከፍተኛ አመራር ባሽር ቆርጋብ፤ ሶማሊያ ውስጥ በደረሰበት የአየር ድብደባ መገደሉን የሶማሊያ ብሔራዊ ራድዮ ጣብያ ዘግቧል።
በግሪጎሪ አቆጣጠር 2008 ላይ አሜሪካ ባሽር ሞሐመድ ቆርጋብ ያለበትን ለጠቆመ 5 ሚሊዮን ዶላር እሸልማለሁ ብላ መግለጫ ማውጣቷ አይዘነጋም።
ዩናይትድ ስቴትስ ሶማሊያ ውስጥ የአል-ሻባብ አባላትን ዒላማ ያደረገ ጥቃት በየጊዜው ትሰነዝራለች። ምንም እንኳ አሜሪካ በሰውየው ግድያ ዙሪያ አስተያየት ባትሰጥም የግለሰቡ ቤተሰቦች ሞቱን አረጋግጠዋል።
በወታደራዊ ካምፖች ላይ ጥቃት በማድረስ የሚፈለገው ባሽር ኬንያ ውስጥ አል-ሻባብ ባደረሳቸው ጥቃቶችም ላይ እጁ እንዳለበት ይነገራል።
የሶማሊያ ብሔራዊ ራድዮ ጣብያ እንደዘገበው ባሽር የካቲት 14/2012 አሜሪካና ኬንያ በጋር ባደረሱት የአየር ድብደባ ነው የተገደለው። ራድዮ ጣብያው ዜናው ዘግይቶ ለምን እንደወጣ ያለው ነገር የለም።
ባለፈው ወር የሶማሊያ መገናኛ ብዙሃን ባሽር ቆርጋብ ከአል-ሻባብ መሪዎች ጋር ባለመስማማቱ ሳይገነጠል አይቀርም ሲሉ ዘግበው ነበር።
ከአል-ቃይዳ ጋር ትሥሥር እንዳለው የሚነገርለት አል-ሻባብ በደቡብ እና መአከላዊ ሶማሊያ ጥቃቶችን በማድረስ ይታወቃል። አልፎም የሶማሊያ ጎረቤት በሆነችው ኬንያ ውስጥ በርካታ ጥቃቶች ያደርሳል።
ባለፈው ወር የአል-ሻባብ ታጣቂዎች ኬንያ ውስጥ የኬንያና አሜሪካ ወታደሮች የሚገለገሉበትን ካምፕ አጥቅተው ሶስት አሜሪካውያንን መግደላቸው አይዘነጋም።














