''አባቴ የቼልሲ ደጋፊ ነበር'' የሜጄር ጄኔራል ገዛዒ አበራ ልጅ

የፎቶው ባለመብት, Dimtsi Woyane
ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ. ም. ኢትዮጵያ ሁለት ትልልቅ የጦር አዛዦቿን፤ የአገሪቱ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ሰዓረ መኮንን እና በጡረታ የተገለሉትን ሜጄር ጄኔራል ገዛዒ አበራን ያጣችበት ቀን ነው።
ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖቹ የተገደሉት በጄኔራል ሰዓረ መኮንን ጠባቂ ሲሆን ጥቃቱ የተፈጸመውም በጄኔራሉ ቤት መሆኑ ተገልጿል።
በወቅቱም በአማራ ክልል ከሸፈ ከተባለው "መፈንቅለ መንግሥት" ጋር የተገናኘ መሆኑም የተነገረ ሲሆን፤ ጥቃቱም የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አምባቸው መኮንንና አማካሪያቸው አቶ እዘዝ ዋሴንና የክልሉ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አቶ ምግባሩ ከበደን ህይወት የቀጠፈ ሆኗል።
በአደባባይ ከሚታወቁበት ሕይወታቸው ጀርባ እነዚህ ሰዎች በግል ሕይወታቸው ምን ዓይነት ሰዎች ነበሩ? ህልማቸውስ? ምንስ ይወዱ ነበር? የሚለው ላይ በማተኮር ቢቢሲ አማርኛ ዘክሯቸዋል።
ሰበሮም ገዛዒ- የመጀመሪያ ልጅ
ወደ ውትድርናው ባይገቡ አባትህ በምን ሙያ ይሰማሩ ነበር ብለህ ታስባለህ?
ሰበሮም፡ አስቤው አላውቅም፤ ግን ምናልባት ወደ ንግዱ ዓለም ሊገባ የሚችል ይመስለኛል። ንግድ ነክ ነገሮች ላይ ጥሩ ነበር። ሁለተኛ ዲግሪውንም የሰራው 'በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን' ነው።
ምን አይነት አባት ነበሩ?
ሰበሮም፡ ገዛዒ ማለት አባት ብቻ አልነበረም። ከአባትም በላይ ነበር። ሁሉም ነገራችን ነበር። ቤተሰቡንና ልጆቹን በጣም ነበር የሚወደው፤ ሁሌም ቢሆን መሳቅና መጫወት ነበር የሚያስደስተው። ይሄ ነው ብዬ መግለጽ ቢከብደኝም አባት ማድረግ ከሚገባው በላይ ነው ያደረገልን። ሁሌም ቢሆን ከሥራ መልስ ቀጥታ ወደቤት ነበር የሚመጣው። ሌላው ቢቀር አንድም ቀን ልደታችን አምልጦት አያውቅም።
ቅዳሜና እሁድም መጽሃፉን የማያነብ ከሆነ ከእኛ ጋር ነው ጊዜውን የሚያሳልፈው።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የሚወዱት በዓል ምንድነው?
ሰበሮም፡ በተለየ መልኩ የሚወደው በዓል አለ ብዬ አላስብም። ሁሉም በዓላት ከቤተሰብ ጋር መሰብሰቢያ ሰበብ ስለሆኑ ሁሉንም የሚወድ ይመስለኛል። ለእሱ ዋናው ቤተሰቡ ሰብሰብ ብሎ መዋሉ ስለሆነ፤ ዋናው ትኩረቱ እሱ ነው።
የሚወዱት ምግብ ነበር?
ሰበሮም፡ ምግቡ ምንም ይሁን ጣፍጦ ከተሠራ ሁሉንም ሳይመርጥ ይበላል። በተለይ ደግሞ እናቴ የምትሠራውን ምግብ በጣም ነበር የሚወደው። አትክልት ነክ ነገሮች እና ሽሮም ይወዳል። ስጋ ላይ እሰከዚህም ነው።
ምን ያዝናናቸው ነበር?
ሙዚቃ ማዳመጥ ይወዳል። ብዙ ጊዜ ሙዚቃ የማዳመጫ ሰአት አይኖረውም ግን አጋጣሚውን ሲያገኝ ሙዚቃ ደስ ብሎት ይሰማ ነበር። መጻሕፍት ማንበብ ደግሞ በጣም ነበር የሚወደው። ያለምንም ማጋነን ሁሌም ቢሆን ሲያነብ ነው የምታገኘው። ወደቤት ሲመጣ ምሳውን ከበላ በኋላ ትንሽ ከእኛ ጋር ተጫውቶ ወደ መጽሐፎቹ ነበር የሚመለሰው። በተለይ ደግሞ ምሽት ላይ ቁጭ ብሎ ረዥም ሰአት መጽሐፍ ያነባል፤ ይጽፋልም። አንዳንዴ ደግሞ በስልኩ ሳይቀር አንዳንድ ነገሮችን ሲያነብ ያመሻል።
የሚወዱት ስፖርት አይነት ምንድነው?
እግር ኳስ ማየት ይወድ ነበር። በእንግሊዝ ፕሪምር ሊግ የቼልሲ ደጋፊ ነው። አንዳንዴ ጊዜ ሥራ ሳይኖረውና ቤት ውስጥ እሱ ሲኖር አብረን ኳስ እንመለከት ነበር። ቤት ውስጥ ኖሮም ብዙ ጊዜ መጽሐፍ ማንበብ ወይም አንዳንድ ጽሁፎችን መጻፍ ነው የሚያዘወትረው።
ማኅበራዊ ሕይወታቸው ምን ይመስላል?
ማኅበራዊ ሕይወቱ በሚያስገርም ሁኔታ በጣም ጥሩ ነበር። ዓመት በዓል እንኳን ሳይቀር ጠዋት ከቤተሰቡ ጋር አሳልፎ ከሰአቱን ዘመድ ጥየቃ ነው የሚወጣው። ለበአል የሚያዘውን ይዞ ቤተዘመድ ሲጠይቅ ነበር የሚውለው። ሁሌም ቢሆን በተረጋጋ መንፈስ ከሁሉም ሰው ጋር ያለውን ግንኙነት ጥሩ ለማድረግ ነው የሚጥረው፤ ለጋስም ነበር።
የተቸገረ ሰው ሲረዳ ለበአል አንዳንድ ነገሮችን ሲያደርግላቸው እያየሁ ነው ያደግኩት። ደግሞ ሰዎች ስለሚያደርገው ጥሩ ነገር እንዲያውቁ አይፈልግም።
የማይረሳ ትዝታ አለህ?
እኔ የማልረሳው ልጆች ሆነን በበዓላት ወቅት ከእንቅልፋችን ስንነሳ ልብስ ተገዝቶ አልጋችን ላይ ተቀምጦ የሚጠብቀንን ነው። ሁሌም ቢሆን ባልጠበቅነው ሁኔታ ያልጠበቅነው ነገር አድርጎ ያስደስተን ነበር።

የፎቶው ባለመብት, Anadolu Agency
የቀድሞ የኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ኤታማዦር ሹም ሌተናንት ጄኔራል ፃድቃን ገብረትንሳዔ- ጓደኛ
ከሜጄር ጄኔራል ገዛዒ አበራ ጋር የተዋወቃችሁት እንዴት ነው?
ጄኔራል ፃድቃን፡ ሜጀር ጄኔራል ገዛዒ ለትግል ወደ በረሃ ሲመጣ እድሜው ትንሽ ነበር። ያን ጊዜ እኔ ቀደም ብዬ ነው ወደ ትግሉ ዓለም የተቀላቀልኩት። ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኘነው 'ኃይል ሰላሳ' በምትባል ቡድን ውስጥ እያለ ነው። ወደ ሎጂስቲክስ ከተመደበ በኋላ ደግሞ እድሜ ልክ በሚባል ደረጃ አብረን ሰርተናል።
የትግል ሕይወታቸውን እንዴት ይገልፁታል?
ጄኔራል ፃድቃን፡ እኔ እስከማስታውሰው ድረስ ገዛዒ በጣም ጠንቃቃና ሥራውን በከፍተኛ ኃላፊነት የሚቀበል ታጋይ ነበር። የሎጂስቲክስ ክፍል ኃላፊ በነበረበት ወቅት በትንሹ ከገበሬ እህል በምንሰበስብበት ወቅት እሱን አደረጃጅቶ ለሠራዊት ቀለብ በመስጠት ላይ የነበረው ብቃት ሁሌም የማልረሳው ነው።
ከፍ ሲል ደግሞ በጣም በተደራጀ መልኩ ሜካናይዝድ ኃይል ይዘን የብዙ የወታደሮቹን ፍላጎት ለማሟላት ስንጥር እንዲሁም በተለያዩ ግንባሮች የተበተኑ ወታደሮችን እና ንብረቶችን በአግባቡ ሰብስቦ በተደራጀ መልኩ መስመር ማስያዝ ላይ እጅግ የተዋጣለት ሥራ ነበር ያከናወነው።
በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት በጣም ትልቅ ኃይል ነው ያሠማራነው፤ ወደ መጨረሻ ላይ እንደውም እስከ 350 ሺ ደርሶ ነበር የሠራዊቱ ቁጥር። ይሄ ሁሉ ኃይል የሚያስፈልገውን የሎጂስቲክስ አቅርቦት በተሟላ መንገድ አሳክቶ ሠራዊቱ ለድል እንዲበቃ አድርጓል።

የፎቶው ባለመብት, MICHAEL TEWELDE
የሚመርጡት ምግብ ይኖር ይሆን?
ጄኔራል ፃድቃን፡ በረሃ ላይ እያለን የምንመርጠው ምንም አይነት ምግብ አልነበረም። ያገኘነውን ነበር የምንበላው። ነገር ግን ደርግን ጥለን ወደ ሥልጣን ከመጣን በኋላ በተለይ ደግሞ ባህላዊ ምግቦችን ያዘወትር ነበር። አንድ የማልረሳው ግን በተለይ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት እሱ ወደነበረበት ግንባር በምመላለስበት ወቅት ሰብሰብ ብለን ጥብስ እንበላ ነበር።
በትግል ወቅት የማይረሱት አጋጣሚ አለ?
ጄኔራል ፃድቃን፡ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት በዘመቻ ፀሃይ ግባት ማለት ነው፤ ድንገተኛ ብልጫ አግኝተን እንድናሸንፍ የተጫወተውን ቁልፍ ሚና ሁሌም የማልረሳው ነው።
ያኔ በጦርነቱ ምክንያት ሳይታዩ እንቅስቃሴ ማድረግ እጅግ ከባድ ነበር። በተጨማሪም መንገዶቹ እጅግ ጠባብና አስቸጋሪ ነበሩ። እሱ ግን ከ750 በላይ የሚሆኑ ትልልቅ ተሽከርካሪዎችን በአንድ ሌሊት ከማዕከላዊ ጾረና ግንባር አስነስቶ በቀጣዩ ጠዋት ባድመ እንዲደርሱ ያደረገበት መንገድ አስገራሚ ነበር።
በዚህ ምክንያት ለአጭር ጊዜም ቢሆን ከፍተኛ የኃይል የበላይነት አግኝተን በቦታው የነበረውን የጠላት ኃይል እንድንመታ አስችሎናል።
ይህ ሥራው በወቅቱ ሁኔታው ከነበረው ክብደት አንጻር፣ ባስገኘው ውጤት እና ሊያስከትል ይችል የነበረውን ጉዳት ከግምት ውስጥ በማስገባት እጅግ አስገራሚ ሥራ ነው ማለት ይቻላል። በእውነት እሱ የሎጂስቲክስ ጥበበኛ ነው።












