በፍቅር ስም የሚያጭበረብሩ ሊለዩ ነው

ዘመን አመጣሽ የፍቅር ጓደኛ አፋላጊ መተግበሪያዎች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል። ውሀ አጣጫቸውን በነዚህ መተግበሪያች ለማግኘት የሚሞክሩ እንዳሉ ሁሉ፤ መተግበሪያውን የሚበዘብዙም አልታጡም።

አንዳንዶች እውነተኛ ማንነታቸውን ይደብቃሉ። በመተግበሪያው የሚያገኟቸውን ሰዎች ገንዘብ ለማጭበርበር የሚሞክሩ ጥቂት አይደሉም። እነዚህን አጭበርባሪዎች በ 'አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ' የሚለይ አዲስ ቴክኖሎጂ መፈጠሩም ተሰምቷል።

መተግበሪያውን የሚጠቀሙ ሰዎች ምስል፣ የግል መረጃና የሚልኳቸው መልዕክቶች ተሰብስበው ይጣራሉ። ስለአንድ ሰው ትክክለኛ ማንነት ለማጣራት ጾታ፣ ዘርና ቋንቋም ከግምት ይገባሉ።

ጥናት እንደሚያሳየው፤ ቴክኖሎጂው አጭበርባሪዎችን በመለየት ረገድ 93 በመቶ ትክክል ነው።

ባለፈው ዓመት ብቻ እንግሊዛውያን 50 ሚሊየን ዩሮ ተጭበርብረዋል። ከእነዚህ መካከል 63 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች እንደሆኑም ጥናት ያሳያል። የፍቅር ጓደኞች የሚያገናኙ መተግበሪያዎች ላይ ስለማንነታቸው ከሚዋሹ መካከል 60 በመቶው እድሜያቸው በአማካይ 50 የሞላ ወንዶች ናቸው።

በመተግበሪያቹ ላይ ሀሰተኛ ማንነት የሚያሰፍሩ ሰዎች በርካታ ፎቶዎች በመለጠፍ ይታወቃሉ። 'አፍቃሪ ነኝ'፣ 'ተንከባካቢ ነኝ' ሲሉም ራሳቸውን ይገልጻሉ።

አዲሱ የ'አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ' ቴክኖሎጂ የተሠራው በእንግሊዝ፣ በአሜሪካና በአውስትራሊያ ባለሙያዎች ጥምረት ነው።

ከመተግበሪያ ተጠቃሚዎች መካከል የትኞቹ እውነተኛ፣ የትኞቹ ሀሰተኛ እንደሆኑ በመለየት ሌሎች ተጠቃሚዎች እንዲጠነቀቁ ለማድረግ ታስቧል። አዲሱ ቴክኖሎጂ ተመሳሳይ አገልግሎት ከሚሰጡ ቴክኖሎጂዎች ጋር ሲነጻጸር ጠንካራ እንደሆነም ባለሙያዎች ተናግረዋል።