በታላቁ ሩጫ ላይ ተሳትፈው ለሚያሸንፉ ተወዳዳሪዎች ላይ የአበረታች መድኃኒት ምርመራ ሊካሄድ ነው

እሁድ ሕዳር 9 2011 ዓ.ም በሚካሄደው የታላቁ ሩጫ ውድድር አሸናፊ የሚሆኑ አትሌቶች የአበረታች መድሀኒት ምርመራ ሊካሄድባቸው መሆኑን የሩጫው አዘጋጆች ዛሬ በሰጡት መግለጫ ላይ አስታወቁ።
በሩጫው ላይ 44 ሺህ ተወዳዳሪዎች ይሳተፋሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን 400 የሚሆኑት ከሌሎች ሀገራት የመጡ ሲሆን 5 አትሌቶች ደግሞ ኤርትራን በመወከል ይሳተፋሉ።
በ10 ሺህ ሜትርና በግማሽ ማራቶን ዝነኛ የሆነው አትሌት ዘረሰናይ ታደሰ ውድድሩ ላይ ለመሳተፍ አዲስ አበባ ተገኝቷል።
"ኢትዮጵያ በመምጣቴ በጣም ደስ ብሎኛል። የውድድሩ አዘጋጆችንም ስለጋበዙኝም አመሰግናለሁ" ብሏል።
እኤአ የ2012 ኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳሊያ አሸናፊ የሆነው ዩጋንዳዊው ስቴፈን ኪፕሮቲች ውድድሩ ላይ ከሚሳተፉ አትሌቶች መካከል አንዱ ነው።
የኬኒያ፣ኡጋንዳ፣ ቦትስዋና ሀገራት የመጡ አትሌቶች በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ።
የውድድሩ መነሻና መድረሻውን ያደረገው ስድስት ኪሎ መሆኑን በመግለጫው ላይ ተጠቅሷል።
የታላቁ ሩጫ የቦርድ ሰብሳቢ የሆነው አትሌት ኃይሌ ገብረ ስላሴ ውድድሩ በሰላማዊ መንገድ ተጀምሮ እንዲጠናቀቅ ጥሪ አቅርቧል።












